Monday, December 19, 2016

የእመቤታችን ዘላለማዊ ድንግልና

Image result for ethiopian mary
የእመቤታችን ዘላለማዊ ድንግልና በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
(John Chrysostom. C.349-407) Archbishop of Constantinople
=====================================
ቅዱስ ዮሐንስ በዘመኑ ለተነሱት መናፍቃን የድንግል ማርያምን ዘላለማዊ ድንግልና እውነታውን አስረግጦ አስተምሮአል። መናፍቃን "ዮሴፍ የበኩር ልጇን እስከ ምትወልድ አላወቃትም የሚለውን "ማቴ1፣25። ተብሎ ስለተጻፈ ድንግል ማርያም ጌታን ከወለደች በኋላ ከዮሴፍ ጋር በትዳር ኖራለች ብለው ለተነሱበት የተሳሳተ ሃሳብ ሲመልስ፣እስከ የሚለው ሃረግ ወይም ቃል " ዮሴፍ የበኩር ልጇን እስከምትወልድ አላወቃትም ማለት አንድም ወንድ እንደማታውቅ አንድም እስከ የሚለው ፍጻሜ የሌለው እስከ ነው ፤ በመሆኑም ጌታን እስከምትወልድ የምትወልደው መድኃኔዓለምን እንደሆነ አላወቀም፣ የድኅነት ምክንያት ሆና እንደተመረጠች አያውቅም ነበር፣ በሉቃስ ወንጌል ላይም ማርያም ነገርን ሁሉ በልቧ ትጠብቀው ስለነበር ከቅዱሳን የከበረች ከመላዕክትም የበለጠች እንደነበር አያውቅም ነበር ። በሌላው ጌታን በፀነሰች ጊዜ ገጽዋ ይለዋወጥ ነበር ይህንንም ሲያይ ዮሴፍ ጻድቅም ስለነበር ሳይገልጣት ተዋት።

የድንግል ማርያም ክብር

Image result for mary ethiopia

የድንግል ማርያም ክብርና ነገረ ክርስቶስ በቅዱስ አትናቴዎስ ሊቀጳጳስ ዘአሌክሳንድርያ  ( d.373)
======================================================
የድንግል ማርያምን አስተምህሮ (Mariology) ንጽህና ቅድስና ዘላለማዊ ድንግልና እንዲሁም በነገረ ድኅነት ውስጥ ያላትን ሱታፌ አብራርተው ከጻፉትና ካስተማሩት አበው ሊቃውንት መካከል 20ኛው የአሌክሳንድርያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ አትናቴዎስ አንዱ ነው። ቅዱስ አትናቴዎስ ከመንፈሳዊ መልዕክቶቹ ጠጣርነት በተለይም በነገረ መለኮትና በነገረ ማርያም ትምህርቱ የተነሳ ታላቁ አትናቴዎስ ሐዋርያው አትናቴዎስ እየተባለ ይጠራል። ትክክለኛውን የተዋሕዶ ምስጢር በተለይም የጌታችንን የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን የባህርይ አምላክነት ለአርዮስና ለተከታዮቹ አስረግጦ በማስተማሩ የእንዚናዙ ቅዱስ ጎርጎርዮስ "የቤተክርስቲያን አምድ" የሚል ስያሜ ሰጥቶታል።
ቅዱስ አትናቴዎስ በአሌክሳንድርያ በ295 ዓ.ም. ተወለደ፣ ዕድሜው ከፍ ሲልም በ24 ዓመቱ (319 ዓ.ም) ከሊቀ ጳጳሱ ከብፁዕ አቡነ አሌክሳንደር ዲቁናን ተቀበለ፣ የሊቀጳጳሱም ጸሐፊ ሆኖ ተሾመ። ይህ አጋጣሚ ነበረ አትናቴዎስን ከሊቀጳጳሱ ጋር በ325 በተደረገው የኒቂያ ጉባኤ ላይ እንዲገኝ የረዳው።

Sunday, December 11, 2016

መቅደስ እንተ ውስቴታ መቅደስ

በዓታ ለማርያም

ኦ መቅደስ ዘኮነ ለሊሁ እግዚአብሔር ሊቀ ካህናት ማኅየዊ ፤ ጌታ በማኅፀን ያደረብሽ አማናዊት መቅደስ አንቺ ነሽ።
ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ 
ኢያቄምና ሐና ከዘመናት በኋላ በስተርጅና እንደ ፀሐይ የምታበራ ልጅ በመውለዳቸው " ነያ ሠናይት እንተ ኅቤየ ነያ ሠናይት አዕይንትኪ ዘርግብ ሥዕርትኪ ከመ መርኤተ አጣሊ ፤ወዳጄ ሆይ እነሆ ውብ ነሽ እነሆ መልከ መልካም ነሽ ዓይኖችሽ እንደ ርግቦች ናቸው " (መኃ 4፣1) በማለት ሰሎሞን እንደ ዘመረላት ፤ በውስጥ በአፍአ ደም ግባቷ ያማረ 
"ኲለንታኪ ሠናይት እንተ ኅቤየ አልብኪ ነውር ወኢምንትኒ ላዕሌኪ" ተብሎ የተተነበየላትን ፣ፈጣሪዋን የምትመስል ንጽህት ቅድስት ልጅ ስለ ወለዱ አምላክን አመሰገኑ። ኢያቄምና ሐና ደስታቸው ያለምክንያት አልነበረም ፤ አንድም ለረጅም ዘመናት ልጅ ሳይወልዱ ሲያዝኑ ቆይተው" ጸኒሐ ጸናሕክዎ ለእግዚአብሔር ሰምዐኒ ወተመይጠኒ ወሰምዐኒ ቃለ ስእለትየ" እንዲል ነቢዩ ዳዊት፤ እግዚአብሔር ስዕለታቸውን መሻታቸውን አይቶ በእርግናቸው ይህችን ብላቴና በማግኘታቸው እንጅ ቀድሞ ሐና በጎረቤቶቿ ጽርፈት ነበረባት፣ የበቅሎ ዘመድ ኅፁተ- ማኅፀን፤ ማኅፀኗ የተዘጋ እየያተባለች ትሰደብ ነበር ኋላ ይህን ዘለፋ የምታስወግድ ልጅ ወለደች፤ ድንግል ማርያም እንባቸውን አበሰችላቸው ፤ ስድባቸውን አራቀችላቸው ፤በእመቤታችን ነቃፊዎቿን አሳፈረች። 

Wednesday, September 14, 2016

በዚች ዓለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሰራለሁ የሲዖል ደጆችም አያናውጡአትም። ማቴ ፲፮፣ ፲፰



ሰኔ ፳ ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊሊጶስ ቂሳሪያ ከሦስት አዕባን (ዓለቶች ) ለእመቤታችን መታሰቢያ ይሆን ዘንድ በስሟ ቤተ ክርስቲያንን ካነጸ በኋላ ሰኔ ፳፩ ቀን ቅዳሴ ቤቷ የከበረበት ዕለት ነው። በማቴዎስ ወንጌል ፲፮ ፣፲፫ ኢየሱስም ወደ ፊሊጶስ ቂሳሪያ አገር በደረሰ ጊዜ ደቀመዛሙርቱን ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል ? ጌታችን ስለራሱ ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል አለ? ከእመቤታችን በነሳው ሥጋ፣ ከእኛ ከአዳም ልጆች በነሳው ሥጋ ራሱን የሰው ልጅ እያለ ይጠራልና። እምነ ፅዮን ይብል ኩሉ ሰብዕ፣ ወብእሲ ተወልደ በውስቴታ።(መዝ፹፮፣፭) 

የኢትዮጵያውያን እንቆቅልሽ መፍትሔ






ብዙዎቻችን በመንፈሳዊ ድርቀት ተይዘናል። ደስታና እረፍት ጥለው ከሸሹ ቀናት ተቆጥረዋል። ሁሉም ሰው ውስጡ ይቆዝማል። ለወዳጁ ቢያማክር እሱም የባሰ ውስጡ የኃዘን ትርምስምስ አለ። ባለን ገንዘብ ደስታ ይሰጡኛል ብለን ወደ ምናስባቸው አቅጣጫም ብናዘግም ዓለም የኛን ደስታ ሙሉ ለማድረግ አቅም የላትም። እናም ትርፍ አልባ ኪሳራ ሆነን ወደ መጣንበት እንመለሳለን። የሁሉንም ቤት እንደፈረኦን ዘመን የግብፃውያን ጓዳ ኃዘን አንኳኩቶታል።
ችግሮቻችን ደግሞ ህብረ ቀለማቸው መብዛቱ አንዱን ሳንወጣው ሌላው ይደረባል። ያለነው በሦስተኛው ዓለም ውስጥ ብቻ ሳይሆን በጨለማው የነፋስ ሌሊት ውስጥ ነው።
በውስጣችን ያለውን የኃዘን ጭጋግ የሚገፍ እስካሁን በምድር ላይ አልተገኘም። የብዙዎቻችን ጸሎት እንኳን ከጣራ ጋር እየተላተመ ይመለሳል እንጅ ብዙም አልፈይድ ብሏል። ዛሬ እግዚአብሔር ለምን ዝም አለ?የሚያስጨንቁንንስ ለምን ዝም ይላቸዋል? የሚለው አንደበት ኢትዮጵያ ውስጥ እልፍ ነው። እውነት እንቆቅልሹስ ምን ይሆን? መቼስ ነው የእንቆቅልሻችን መፍትሔ የሚገኘው?

Saturday, April 23, 2016

ሆሳዕና





እስራኤላውያን ጌታ የተቀመጠባት አህያ አከበሩ፡ ይህ ትውልድ ግን ጌታ የተቀመጠባት እመቤታችን ማክበር ተሳነው፡፡(ማቴ ፳፩፤ ፩፣ ፱)
============================================================================
• ጌታችን የታሰሩ አህዮች ለምን መረጠ?
•ሐዋርያት ለምን ልብሳቸው አነጠፉለት ?
• ጌታ ለምን በፈረስ ላይ አልተቀመጠም?
•ዘንባባ የምን ምሳሌ ነው?
• በሆሣዕና በእጃችን እደ ቀለበት ማሰራችን የምን ምሳሌ ነው?
---------------------------------------------------------------------

Saturday, April 16, 2016

አማን አማን ዕብለከ ዘኢተወልደ ዳግመ ኢይሬእያ ለመንግስተ እግዚአብሔር(ዮሐ ፫፣ ፫)


ኒቆዲሞስ :
የአብይ ጾም ሰባተኛ ሳምንት
------------------------------------------
ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ መንግስተ ሰማይን አይወርስም::(ዮሐ ፫፣ ፫)
=======================================
ወሀሎ አሐዱ ብእሲ እምፈሪሳውያን ዘስሙ ኒቆድሞስ ። ብዙኃን አምኑ ቦቱ ብሎ ነበርና ብዙኃን ካላቸው ከፈሪሳውያን ወገን የሚሆን ኒቆዲሞስ የሚባል አንድ ሰው ነበር ። መጽሐፍ ይህን ሰው መልአኮሙ ለአይሁድ ይለዋል። መልአክ ማለት አለቃ ማለት ሲሆን ፤ ኒቆዲሞስ የአይሁድ አለቃ የተባለበት ምክንያት አንድም በትምህርቱ በዳኝነት ወንበር ላይ ተቀምጦ ይፈርድ ስለነበር፣ አንድም በሹመቱ የአይሁድ አለቃ ስለነበር፣
አንድም በሃብቱ በንብረቱ ባለጸጋ ስለነበር ነው።

Sunday, April 10, 2016

ሰሙነ ሕማማት --(ክፍል-ሁለት)


ነስአ ደዌነ ወፆረ ሕማመነ
-------------------------
እናት የወለደችው ልጇን እንደምታዝል አምላካችን እኛን ፍጥረቶቹን በተለይም በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረንን ልጆቹን ከልጅነት እስከ እውቀት ከነኃጢያታችን በማይዝል ትከሻው ተሸክሞ የሚያኖረንን መጋቢና ኤልሻዳይ አምላክ አይሁድ በእለተ አርብ መከራ አጸኑበት ተዘባበቱበት ። የአዳም ዘር ክብር ጎድሎት ጸጋው ተገፎ ከሰውነት ተራ ቢወጣ እሱ ሥግው ሆኖ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተገለጠ እንደሰው እየተመላለሰ እንደ እግዚአብሔር ሰራ የሰውን ስብዕና ይመልስ ዘንድ ድውያኖቻቸውን ቢፈውስ እውራኖቻቸውን ቢያበራ እነሱ ግን ሰንበትን ሻረ ብለው ክስ መሰረቱበት ፣ ችግራቸውን ይፈታ ዘንድ መናን አበርክቶ በመገባቸው ግፈኞች አይሁድ ግን የበሉበትን ወጪት ሰበሩ በጠላትነት ተነስተው ንጹህ ደም አፈሰሱ( መዝ ፵ ፣፱) ። ስለ በደላችንና ስለ ኃጢያታችን አስራ ሦስት ሕማማተ መስቀልን ተቀበለ። መከራ መቀበሉስ እንዴት ነው ቢሉ በአባቱ ፈቃድ በራሱ ፈቃድ በባሕሪ ሕይወቱ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ፍቅር አገብሮት የፍጥረቱ የአዳም ነገር ግድ ስለሆነበት እንጅ እሱ የልዑላን ልዑል የማይገሰስ የማይደፈር ነው ።

Saturday, April 9, 2016

በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ፤ማቴ ፳፭ ፣፳፩

ገብርኄር 


የአብይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት
 ገብርር ማለት ታማኝ አገልጋይ ማለት ነው።
ከመ እንግር ፈቃደከ መከርኩ አምላኪየ  
ወሕግከኒ በማዕከለ ከርስዬ 
 ዜኖኩ ጽድቀከ በማኅበረ ዐቢይ።
(መዝ፴፱፣ ፰)




 ወምዕመን ዘበኅዳጥ፣ ዘበውኁድ ምዕመነ ኮንከ ዲበ ብዙኅ እሰይመከ። ማቴ ፳፭ ፣፳፩
===============================================
ወደ ሩቅ ሀገር የሚሄድ ባለጸጋ ሰው አገልጋዮቹን ወደ እርሱ ጠርቶ ያለውን ገንዘብ ነግደው እንዲያተርፋበት ሰጣቸው ፣ ቦ ለዘወሀቦ ሃምስተ መክሊተ  አምስት መክሊት የሰጠው ሰው አለ፣ወቦ ለዘወሀቦ ክልኤተ መክሊተ ፡ሁለት መክሊት የሰጠው ሰው አለ፣ወቦ ለዘወሀቦ አሐደ መክሊተ ፡አንድ መክሊት የሰጠው ሰው አለ፤ ለእያንዳንዳቸው እንደአቅማቸው ሰጥቷቸው ሄደ፡ወነገደ በጊዜሃ።
፩) አምስት መክሊት የተቀበለው ወጥቶ ወርዶ አተረፈ ፣ወረብኃ ካልዓተ ኀምስተ መካልየ፤ አምስት አትርፎ አስር አድረገ።
፪) ወከማሁ ዘሂ ክልኤተ መካልየ ረብኃ ካልአተ መካልየ፣እንደዚሁ ሁሉ ሁለት መክሊት የተቀበለውም ወጥቶ ወርዶ አትርፎ አራት አደረገ።
፫) ወዘ አሐደሰ መክሊተ ነስአ ሖረ ወኃለፈ ወከረየ ምድረ ወኃብ ወርቀ እግዚኡ፣ አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ሌባ ቢሰርቀኝ ወንበዴ ቢቀማኝ ቀጣፊ ቢያታልለኝ ብሎ ፈርቶ ሄዶ ምድር ቆፍሮ የጌታውን ወርቅ ቀበረ።
ወእምድኅረ ብዙኅ መዋዕል አተወ እግዚኦሙ ለእሉ አግብርት፣ ከብዙ ዓመት በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታቸው መጣ
ወአኅዘ ይትሐሰቦሙ ፡ ተቆጣጠራቸውም።

ተዘጋጅታችሁ ኑሩ ፣(ማቴ ፳፬ ፣፵፪)

ደብረ ዘይት 


የዓብይ ጾም ፭ኛ ሳምንት

ትግሁ እንከ እስመ ኢተአምሩ በዓይ ሰዓት ይመጽእ እግዚእክሙ።(ማቴ ፳፬ ፣፵፪)
===============================================
ወእንዘ ይነብር እግዚእነ ውስተ ደብረ ዘይት ቀርቡ ኅቤሁ አርዳኢሁ ፤ ጌታችንና መድኃኒታችን በደብረዘይት ተቀምጦ ሳለ ደቀመዛሙርቱ ወደሱ ቀርበው ፤ ወይቤልዎ እንተ ባሕቲቶሙ ፤ለብቻቸው ጠየቁት ፡ ንገረነ ማዕዜ ይከውን ፡ -
1)ዝንቱ ወናሁ ይትኃደግ ለክሙ ቤትክሙ በድወ ብሎ ነበርና፤ህንፃ በህንፃ ላይ ሳይፈርስ አይቀርም
2) ወምንትኑ ተአምሪሁ ለምጽአትከ ፣ አማን እብለክሙ ኢትሬእዩኒ፣ የሰውን ልጅ በክብሩ ሲመጣ ታዩታላችሁ ብሎ ነበርና
3) የመምጫህስ ወለኀልፈተ ዓለም ፣ የኀልፈተ ዓለምስ ምልክቱ ምንድን ነው? አሉት።
ጌታችንም የዓለምን መጨረሻና የመምጣቱን ምልክት በዝርዝር አስተማራቸው ፣ ወአውሥአ ወይቤሎሙ 

Thursday, April 7, 2016

ሰሙነ ሕማማት --(ክፍል አንድ)


ነስአ ደዌነ ወፆረ ሕማመነ 
===============
የጌታችንን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራ በትንቢት መነጽር እያየ ነቢዩ ኢሳይያስ መርገማችን ሊሽር ነውራችን ሊያንከባልል ፣ ስለ እኛ የከፈለውን ውለታ ሲዘክር ሕመማችን ታመመ መቅሰፍታችን ተሸከመ ስድባችንን ያስወግድ ዘንድ እሱ ተሰደበ አለ፤ ትውልዱ ግን አላስተዋለም፣ ከትውልዱ ማን አስተዋለ ፣ እርሱ ግን ያከብረን ዘንድ ተዋረደ ፣ ያነሳን ዘንድ ወደቀ
ከእስራታችን ይፈታን ዘንድ በገመድ ታሰረ
በአይሁድ ቀያፋ በስምንቱ ቤተ ጭፍራ ተዘለፈ ፣አስራ ሦስቱን ሕማማተ መስቀል ተቀበለ፡-

Tuesday, April 5, 2016

ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ? (ሆሴ ፲፫፣፲፬)





ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ? (ሆሴ ፲፫፣፲፬)
===================================
ይህንን ቃል ነቢዩ ሆሴዕ የጌታችንን የመድኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ በትንቢት መነጸር እያየ በእምነት ሐሴት እያደረገ ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ? ሲዖል ሆይ ድል መንሳትህስ ወዴት ነው?በማለት ተናግሮታል፡፡
መጽሐፍ እግዚአብሔር ሞትን እንዳልፈጠረም ነገር ግን የሰው ልጆች ትዕዛዝን በመሻር ሕግን በመተላለፍ በአመጽ ምክንያት በሥራቸው ሞትን ወደ ሕይወታቸው እንዳስገቡ ይነግረናል፡፡ ይህንን ሲያጸና ሐዋርያው ጳውሎስም ኀጢዓት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ ካለ በኋላ በኀጢዓትም ሞት ገባ ይለናል፡(ሮሜ ፳፫) የኀጢዓት ደሞወዝ ሞት ነውና ከዚያን ጊዜ ጀምሮ  ሺህ  መቶ ዓመታት ሞት ገዥ ሆኖ : አሳዳጃችን በአንገታችን ላይ ነው ተብሎ እንደተጻፈ በሰው ልጆች ላይ ሁሉ ንጉሥ ሆኖ ኖረ  የአዳም ልጆችም ከሞት እርግማን የተነሣ አልቃሾች ሆነው ኖሩ ደስታ ከእነሱ ራቀ፣ ሞት ሁሉን እያሸነፈ ሁሉን እየማረከ ከተወደደችው ዓመት ደረሰ (ኢሳ ፷፩ )  በዚች ዓመት ግን ነገር ተገለበጠ የተቆጠረው ባዔ የተነገረው ትንቢት ጊዜ በደረሰ ጊዜ ሞት በእባብ ተሰውሮ ገዥ ሆኖ እንደኖረ ከሦስቱ ቅዱስ አንዱ ቅዱስ እግዚአብሔር ወልድ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከዙፋኑ ዝቅ ብሎ ከድንግል ማርያም ተወልዶ ሁለተኛው አዳም ሆነ እንደ እግዚአብሔርነቱ እየሰራ ሞትን በሞት ያጠፋ ዘንድ ሰው ሆነ ከሙላቱ ሳይጎድል በተለየ አካሉ ሰው ሆነ፤ ሰው ሆነው ተፈጥረው ሰው መሆን ያቃታቸውን፣ የሰው ልጆችን ሰው ያደረግ ዘንድ ሰው ሆነ ችግራችንን ይፈታ ዘንድ መርገማችን ይሽር ዘንድ ስድባችን ያስወግድ ዘንድ ሰው ሆነ በግዕዘ ሕፃናትም በሞገስና በጥበብ ቀስ በቀስ አደገ በ፴ዘመኑም በዮርዳኖስ ተጠመቀ ሳይውል ሳያድር ዳመ ቆሮንጦስ ጾመ ጸለየ ከዲያብሎስም ተፈተነ ከዚህም በኋላ ነበረ አሳሪውን ያስር ዘንድ ኀይለኛውን ያንበረክክ ዘንድ ከምድር ከፍ ከፍ አለ (ዮሐ፲፪፴፪) በመስቀል ላይም ተሰቀለ፣ ሁሉን ወደእርሱ ይስብ ዘንድ ሕዝቡን ይቤዣቸዋል ተብሎ በነቢያት ተነግሮ ነበረና ቃሉ ይፈጸም ዘንድ በመስቀል ላይ ተሰቀለ፣ በኃጢዓታችን ሙታን ነበርንና በክርስቶስ ሕይወትን ይሰጠን ዘንድ እስከ መስቀል ሞት ድረስ አከበረን መቃብራችንን ከፍቶ ከሞት ያወጣን ዘንድ ወደ መቃብር ወረደ፣ ሙታንን ሕያዋን ያደርግ ዘንድ ሞተ፣ ሁሉን ሕያው ያደርግ ዘንድ አንዱ ስለሁሉ ሞተ፣ የትንሣኤያችን በኩር ይሆን ዘንድ አንዱ ስለ ሁሉ ሞተ (፪ቆሮ )::

እግዚአብሔር በቅዱሳኑ አድሮ የሚሰራው ስራ እጹብ ድንቅ ነው:

 እግዚአብሔር በቅዱሳኑ አድሮ የሚሰራው ስራ እጹብ ድንቅ ነው:
====================================


የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሯችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ የኑሯቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በሃይማኖት ምሰሏቸው::እብ 13:7
እግዚአብሔር የጸጋ ሁሉ ባለቤት ነው ስለዚህ ለፍጥረቱ የሚሰጠው የጸጋ አይነት ውስን ስፍር ቁጥር ልናበጅለት አንችልም:: የምናውቅበት መንገድ ግን አለን ይህውም በየጊዜው ለሚነሱ ቅዱሳን የሚሰጠውን ጸጋ መመልከት ብቻ ነው:: እግዚአብሔር በቅዱሳኑ አድሮ የሚሰራው ስራ እጹብ ድንቅ ነው:: በመሆኑም በገድላቸውና በታምራቸው ለህሊና የሚያስደንቅ ነገሮችን እንመለከታለን:: በቅዱሳን ገድል ላይ ያሉት ቃል ኪዳኖች መረዳትና የነእርሱንም ስም በመጥራት እግዚአሔርን መማጸን በረከትን ያሰጣል::ለምሳሌ ነብየ እግዚአብሔር ኤልሳን ብንመለከት አምላከ ቅዱስ ኤልያስን በመጥራት በመጠምጠሚያው ባህር ተከፈሎለታል ከዚህ የምንረዳው የቅዱሳንን ስም በመጥራት አምላከ ቅዱሳንን ብንማጸነው የእነርሱን ዋጋ እንቀበላለን ማለት ነው::
በዚህም መሰረት የቅዱሳንን ገድል ጽፎ ማስቀመጥና ትውልድ ከእነርሱ ህይወት እንዲማር ማድረግ ከብሉይ ኪዳን ጀምሮ የነበረ በአዲስ ኪዳንም የነበሩ አበው ለኛ ያቆዩልን የቤተክርስቲያን መንፈሳዊ ሃብት እንጂ ልብ ወለድ ድርሰት አይደለም::

Thursday, March 17, 2016

‹‹ንጹም ጾመ ወናፍቅር ቢጸነ››

 


እንኳን ዓብይ ጾም አደረሳችሁ

ምን  እንጹም ባልንጀራችን እንውደድ

‹‹እስመ ጾም እማ ለጸሎት ወእኀታ ለአርምሞ ወነቅዓ ለአንብዕ ወጥንተ ኩሉ ገድል ሠናይት››
 ጾም የጸሎት እናት የአርምሞ እህት የዕንባ ምንጭና የመልካም ገድል ሁሉ ጥንተ መሠረት ናት

ባሕረ ጥበባትና ስንዱ እመቤት የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ልዩ ከሚያደርጓት ነገሮች መካከል አንዱ የሒሳብ ስሌት ሰርታ የዘመን መቁጠሪያ ሳይንስን (ባሕረ ሐሳብን) ቀምራ አበቅቴና መጥቅን ለይታ የአማትና የበዓላትን ዕለታት ወስና ለትውልድ ማስተለለፏ ነው፡፡ በመሆኑ ዘወትር በየዓመቱ ሰባቱን የአዋጅ አጽዋማት ታውጃለች፣ ከነዚህም መካከል አንዱና ርዕሰ አጽዋማት ሆነው የዓይ ጾም (የጌታ ጾም) ነው፡፡ በቤተከርስቲያናችን ቀኖና መሠረት እምነት ጾም ጸሎትና ምጽዋት የማይለያዩ አንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ከመሆናቸውም ባሻገር ጾም ጸሎትና ምጽዋት እንደ ጣራና ግርግዳ የመልካም ሥራ አበጋዞች ናቸው፡፡ እምነት በመሠረትነቱ እንዲጸና እንዲያድግና ሥራ እንዲሠራ ጾም ጸሎትና ምጽዋት ያስፈልጋሉ፡፡ ጾምም ከእምነትና ከጸሎት ጋር ሲሆን ድንቅ ሥራ ያሰራል ይህ ከሆነ ዘንድ ደግሞ በጎ ሥራን ሳይሰሩ ፍቅርን ሳይዙ ምህረትንና ይቅርታን ሳያደርጉ እጾማለሁ ማለት የረሃብ አድማ እንጂ ክርስቲያናዊ ጾም አይደለም፡፡

Wednesday, February 17, 2016

ንሕነሰ ንሰብክ ክርስቶስሃ ዘተሰቅለ (1ቆሮ 1: 22)

                   

                     ንሕነሰ ንሰብክ ክርስቶስሃ ዘተሰቅለ (1ቆሮ 1: 22)
                     -------------------------------------------
ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ምእመናን በላከው መልእክት ውስጥ የእርሱና የሌሎች ቅዱሳን ሐዋርያት ተልእኮ ምን እንደ ሆነ ያስረዳበት ቃል ነው እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን የሚለው።
ሐዋርያት ወንጌልን ለማስተማር ወደ ዓለም በወጡበት ወቅት ከአይሁድ፣ ከሮማውያንና ከግሪካያውን የተለያዩ ፈተናዎች ገጥሟቸው ነበር። አይሁድ ወልደ አምላክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የሰቀሉ ምእመናን ከኢየሩሳሌም ወደ ተለያዩ የአሕዛብ መንደሮችና ከተሞች እንዲበተኑ ያደረጉ ሐዋርያት በዋሉበት እንዳያድሩ ባደሩበት እንዳይዉሉ ሲያሳድዱ የነበሩ በእግዚአብሔር ለማመን ተአምራትን ይናፍቁ የነበሩ ናቸው። ሮማውያን በአምልኮ ጣዖት ዓይነ ልቡናቸው የታወረ ከመሆናቸው ባሻገር ነገሥታቶቻቸው ራሳቸውን እንደ ፈጣሪ ቆጥረው ምሥል አቁመው ሕዝቡ እነርሱን እንዲያመልክ የሚያስደርጉ ሲሆኑ ግሪካውያን ደግሞ በእነ ሶቆራጥስ፣ ፕሌቶና አሪስጣጣሊስ ፍልስፍና ተይዘው በነገር ሁሉ መጠበብን (መፈላሰፍን) ዋና ነገራቸው ያደረጉ ሕዝቦች ነበሩ።

Monday, February 1, 2016

የእመቤታችን ክብር

                                                      
                                                                           የእመቤታችን  ክብር
በቀሲስ ደረጀ ሥዩም

“ማርያም ንጽሕት፣ ድንግል፣ ወላዲተ አምላክ፣ ማእምንት፣ ሰኣሊተ ምሕረት፣ ለውሉደ ሰብእ” ትርጉም “ንጽሕት፣ ድንግል ማርያም የታመነች፣ የአምላክን የወለደች ናት፡፡ ለሰዎች ልጆችም ምሕረትን ትለምናለች፡፡” (ውዳሴ ማርያም ዘዓርብ አንቀጽ 6 ቁ. 15)

የቀደሙት አባቶቻችን የቤተክርስቲያን ሊቃውንት የቤተክርስቲያኒቱን የቅዳሴና የውዳሴ መጻሕፍት ሲያዘጋጁ አብዛኛዎቹ ከጸሎት መጽሐፍትነታቸው ባሻገር ሃይማኖታዊ ትምህርታቸውም እንዲጎላና ክርስቲያኑ በየዕለቱ በጸሎት መልኩ ሲያዘወትራቸው ሃይማኖቱንም እንዲያጠና በጥበብ አዘጋጅተውታል። እንደምሳሌ የሃይማኖት ጸሎትንና ውዳሴ ማርያምን መጥቀስ ይቻላል።
በተለይ ውዳሴ ማርያምን የደረሰው ቅዱሱ አባታችን ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ አካላዊው ቃል ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋን ተዋሕዶ እንደሚወለድ የተነገሩትን የብሉይ ኪዳንን የትንቢት ቃሎችና ምሳሌዎች እያመሳጠረ በአዲስ ኪዳን የወንጌል ቃል እየፈታና የእመቤታችንን ክብር እያብራራ ውዳሴ ማርያምን ከጸሎትነቱ ባሻገር ምስጢረ ሥጋዌን የምናጠናበት እንዲሆን አድርጎ አዘጋጅቶታል።

Saturday, January 30, 2016

ሞት የተሸነፈብሽ ሆይ ሞት እንዴት አገኘሽ


    ሞት የተሸነፈብሽ ሆይ ሞት እንዴት አገኘሽ
    =========================

                         " ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ
                            ሞታ ለማርያም የአጽብ ለኩሉ
    ትርጉም ፦ ሞትማ ለሚሞት ሰው ይገባዋል
    የማርያም ሞት ግን እጅግ ያስገርማል"

    የመላዕክት እህት ሆይ መውጊያው የተሰበረ ሞት እንዴት በአንቺ ላይ በረታ፤
    የአዳም ተስፋው የአብርሃም ርስቱ ክብርት ሆይ ፍላፃው የተቆረጠ ሞት እንዴት በአንቺ ላይ ኃይል አገኘ፤
    የአመፃ መዝገባችንን የገለበጠውን ብርቱ የወለድሽ ሆይ ደካማው እንዴት ወደ አንቺ መጣ፤...
    በብርሃን ላይ ስልጣን ያለውን ብርሃንን የወለድሽ ሆይ የጨለማው አበጋዝ እንዴት አንቺን ደፈረ፤
    የፍቅርና የትህትና መምህርት ሆይ የጥልና የትዕቢት አባት ሞት እንዴት አገኘሽ፤
    ርግበ-ኖህ የተባልሽ የድኅነታችን ምክንያት ሆይ ከሐዲው ቁራ ወደ አንቺ ለምን መጣ፤
    መዓዛሽ የተወደደ የናርዶስ ቀጺመታት ሽቱ ሆይ ክፋ ጠረንና መጥፎ ሽታ ያለው እንዴት አንቺን ቀረበ፤
    የነቢያትን ናፍቆት የወለድሽ የኢሳይያስ ድንግል የሕዝቅኤል የተዘጋ ምስራቅ በር ሆይ በምን በኩል የተናቀው አገኘሽ፤
    የዮሐንስ እናት ደግሞም የጥበቡ ምንጭ ሆይ የማትሞቺ እንዴት አንቺ ሞትሽ፤
    ሐዘናችንን ያራቅሽ ሙኃዘ ፍስሐ የተባልሽ የደስታችን መፍሰሻ ሆይ የሐዘናችን ምክንያት መላከ ሞት አንቺን ይቀርብ ዘንድ እንዴት እድል አገኘ፤
    ሞት የተሸነፈብሽ አንቺ ሆይ ከቶ ሞት እንዴት ወደ አንቺ መጣ፤


    ጥር ፳፩ ቀን፳፻፰ ዓ.ም

የሰሞኑ የሚዲያዎች ግርግር


ሰሞኑን የተለያዩ ድረ ገፆችን ካጨናነቁት አርእስተ ጉዳዮች መካከል አንዱ “አቡነ” መልከጼዴቅ በኦርጋንና በተመሳሳይ ዘመናዊ የሙዚቃ መሣርያዎች ስለ መዘመር የተናገሩት ንግግር ነው። ንግግራቸውን ተከትለው ለብዙ ዓመታት ደብቀውት የነበረውን አቋማቸውን በርካታ የኾኑ “የአቡኑ” ደቀ መዛሙርት ጉዳዩን ወደ ቤተ ክርስቲያን አሾልከው ለማስገባት ምእመናንም ሀሳባቸውን እንዲቀበሏቸው በብዙ በመጣር ላይ ይገኛሉ።“አቡነ” መልከጼዴቅ ሃሳባቸው ተቀባይነት እንዲያገኝ ርእሰ ጉዳዩን ከሁለት የቅርብ ጊዜ ታሪካዊ ሁኔታ ጋር ለማቆራኘት ሞክረዋል። አንደኛው በአፄ ቴዎድሮስ ዘመነ መንግሥት የተተረጎመው መጽሐፍ ቅዱስ ኦርጋን ወይም አርጋኖን የሚለውን ቃል መጠቀሙን፣ ሁለተኛም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ዘመነ ፕትርክና ዘመን ኦርጋን በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ መዋሉን በአጽንኦት ገልጠዋል። ሁለቱንም ሃሳበቸውን በማስተዋል ስንመለከተው ሚዛን የማይደፉ ሆነው እናገኛቸዋለን።

Friday, January 29, 2016

አስተርእዮ ማርያም (ጊዜ እረፍታ ለማርያም )





    ጥር 21 በዚህች ዕለት ስለሰው ልጅ አንድ ጊዜ አይደለም ሰባት ጊዜ ልሙት ያለች ለፍጥረት ሁሉ የምታዝን ከርህራዬዋ ብዛት የተጠማን ውሻ በወርቅ ጫማዋ ያጠጣች አባቶች ቢወዷት ሶልያና ያሏት ተወዳጅ እናታች...ን ድንግል ማርያም በ 64 ትአመቷ ዐረፈች። ነፍሷ ከስጋዋ የምትለይበት ጊዜ ሲደርስ ሐዋርያትና ድንግል ትባርካቸው ዘንድ እያለቀሱ ለመኗት፤ እጁዋን በላያቸው ዘርግታ ባረከቻቸው። በዚያን ጊዜ ጌታችን ንፅህይት ነፍሷን ከስጋዋ ለይቶ ወሰደ። እንደሌላው ፍጥረት ሁሉ የድንግልን ሞት ተናግረን ዝም የምንል አይደለም ይልቁንም ሞትን ድል እንዳረገው እንደ ልጇ እርሷም መነሳቷን እንመሰክራለን እንጂ ። "ማርያም ሞተኪ ይመስል ከብካበ" እውነት ነው የድንግል ማርያም ዕረፍት በመልአክት በብዙ ዝማሬ የታጀበ ሥለነበር ደስታ ሠርግ ነው የሚመሥለው። የሕይወት የድህነት አለኝታ የሆነች እርሷን እናቱን ለሰጠን እግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በጸሎቷም ከክፉ ነገር ይጠብቀን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።

Wednesday, January 27, 2016

ሊቀ ሰማዕታት ፀሐይ ዘልዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ፡-


                                 
    ሊቀ ሰማዕታት ፀሐይ ዘልዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ፡-
     ጊዮርጊስ ማለት ‹‹ኮከብ ብሩህ፣ ፀሐይ›› ማለት ነው፡፡ ሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ ሀገሩ ፍልስጤም ልዩ ስሟ ልዳ ሲሆን የተወለደው በ277 ዓ.ም ጥር 20 ቀን ነው፡፡ አባቱ ዞሮንቶስ ወይም አንስጣስዮስ የ...ልዳ መኳንንት ሆኖ ተሹሞ ይኖር ነበር፤ እናቱ ቴዎብስታ ወይም አቅሌስያ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ሌላ ማርታና እስያ የሚባሉ ሁለት ሴት ልጆችን ወልዳለች፡፡

Thursday, January 14, 2016

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ክብር


    የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ክብር
    ============================
     ስለ እመቤታችን ክብር በመጽሐፍ ቅዱስ የተፃፈውን የእመቤታችንን ንግግር መጥቀስ በቂ ነው እነሆ ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል። ሉቃ 1፥48
     በመጽሐፍ ቅዱስ እመቤታችንን ስለማክብር የተፃፉ ብዙ ጥቅሶች አሉ፣ ለምሳሌ በእመቤታችን እናት ዕድሜ የነበረችዋ ቅድት ኤልሳቤጥ እመቤታችንን “የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል? እነሆ፥ የሰላምታሽ ድምጽ በጆሮዬ በመጣ ጊዜ ፅንሱ በማኅፀኔ በደስታ ዘሎአልና።” ሉቃ 1፥ 43-44 አለቻት እዚህ ላይ የሚያስደንቀን ነገር ኤልሳቤጥ የእመቤታችንን ሰላምታ በሰማች ጊዜ “መንፈስ ቅዱስ ሞላባት” የሚለው ሐረግ ነው። የእመቤታችንን ድምፅ መስማት ብቻ ኤልሳቤጥን መንፈስ ቅዱስ እንዲሞላባት አደረጋት።

ሐራጥቃ ተሃድሶን ልብ የሰጡ ሦስቱ ጽንፎች


“መቀበል፣መደገፍ እና መከተል! ሐራጥቃ ተሃድሶን ልብ የሰጡ ሦስቱ ጽንፎች” ውድ አንባብያን በዕረፍት አልባ ቀንና እንቅልፋ የለሽ ሌሊት ልንታገለው ስለሚገባው ሐራጥቃ ተሃድሶ(ፕሮቴስታንታዊ ተሃድሶ) በአንክሮ መነጋገሩ ጊዜው የሚጠይቀው ጉዳይ ነው፡፡ ሐራጥቃ ተሃድሶ ሕልም አይደለም! ቅዠትም አይደለም! እንደ ምድር ወገብ የሃሳብ መሥመርም አይደለም! ምዕናብም አይደለም! ሰዎች አልያም ማኅበራት የፈጠሩት ስምም አይደለም! ይልቁንም በዓይን የሚታይ፣በጆሮ የሚሰማና እና በእጅ የሚዳሰስ የዐደባባይ እውነት እንጂ፡፡ ዛሬ ለዚህ እኩይ አካል እዚህ መድረስ ጉልህ አስተዋጽኦ ስላደረጉና ለሐራጥቃ ተሃድሶ ግብዓት ስለሆኑት ሦስት ነገሮች መጻፍ አስገደደኝ፡፡ እነዚህ ሦስት ኩነቶች መቀበል፣መደገፍ እና መከተል ናቸው፡፡