Wednesday, February 17, 2016

ንሕነሰ ንሰብክ ክርስቶስሃ ዘተሰቅለ (1ቆሮ 1: 22)

                   

                     ንሕነሰ ንሰብክ ክርስቶስሃ ዘተሰቅለ (1ቆሮ 1: 22)
                     -------------------------------------------
ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ምእመናን በላከው መልእክት ውስጥ የእርሱና የሌሎች ቅዱሳን ሐዋርያት ተልእኮ ምን እንደ ሆነ ያስረዳበት ቃል ነው እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን የሚለው።
ሐዋርያት ወንጌልን ለማስተማር ወደ ዓለም በወጡበት ወቅት ከአይሁድ፣ ከሮማውያንና ከግሪካያውን የተለያዩ ፈተናዎች ገጥሟቸው ነበር። አይሁድ ወልደ አምላክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የሰቀሉ ምእመናን ከኢየሩሳሌም ወደ ተለያዩ የአሕዛብ መንደሮችና ከተሞች እንዲበተኑ ያደረጉ ሐዋርያት በዋሉበት እንዳያድሩ ባደሩበት እንዳይዉሉ ሲያሳድዱ የነበሩ በእግዚአብሔር ለማመን ተአምራትን ይናፍቁ የነበሩ ናቸው። ሮማውያን በአምልኮ ጣዖት ዓይነ ልቡናቸው የታወረ ከመሆናቸው ባሻገር ነገሥታቶቻቸው ራሳቸውን እንደ ፈጣሪ ቆጥረው ምሥል አቁመው ሕዝቡ እነርሱን እንዲያመልክ የሚያስደርጉ ሲሆኑ ግሪካውያን ደግሞ በእነ ሶቆራጥስ፣ ፕሌቶና አሪስጣጣሊስ ፍልስፍና ተይዘው በነገር ሁሉ መጠበብን (መፈላሰፍን) ዋና ነገራቸው ያደረጉ ሕዝቦች ነበሩ።

Monday, February 1, 2016

የእመቤታችን ክብር

                                                      
                                                                           የእመቤታችን  ክብር
በቀሲስ ደረጀ ሥዩም

“ማርያም ንጽሕት፣ ድንግል፣ ወላዲተ አምላክ፣ ማእምንት፣ ሰኣሊተ ምሕረት፣ ለውሉደ ሰብእ” ትርጉም “ንጽሕት፣ ድንግል ማርያም የታመነች፣ የአምላክን የወለደች ናት፡፡ ለሰዎች ልጆችም ምሕረትን ትለምናለች፡፡” (ውዳሴ ማርያም ዘዓርብ አንቀጽ 6 ቁ. 15)

የቀደሙት አባቶቻችን የቤተክርስቲያን ሊቃውንት የቤተክርስቲያኒቱን የቅዳሴና የውዳሴ መጻሕፍት ሲያዘጋጁ አብዛኛዎቹ ከጸሎት መጽሐፍትነታቸው ባሻገር ሃይማኖታዊ ትምህርታቸውም እንዲጎላና ክርስቲያኑ በየዕለቱ በጸሎት መልኩ ሲያዘወትራቸው ሃይማኖቱንም እንዲያጠና በጥበብ አዘጋጅተውታል። እንደምሳሌ የሃይማኖት ጸሎትንና ውዳሴ ማርያምን መጥቀስ ይቻላል።
በተለይ ውዳሴ ማርያምን የደረሰው ቅዱሱ አባታችን ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ አካላዊው ቃል ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋን ተዋሕዶ እንደሚወለድ የተነገሩትን የብሉይ ኪዳንን የትንቢት ቃሎችና ምሳሌዎች እያመሳጠረ በአዲስ ኪዳን የወንጌል ቃል እየፈታና የእመቤታችንን ክብር እያብራራ ውዳሴ ማርያምን ከጸሎትነቱ ባሻገር ምስጢረ ሥጋዌን የምናጠናበት እንዲሆን አድርጎ አዘጋጅቶታል።