Sunday, November 4, 2012

ተመየጢ ተመየጢ ሱላማጢስ




ይህንን ቃል የተናገረዉ ንጉስ ሰሎሞን ነዉ፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን ከመዝሙር ሁሉ ሚበልጥ መዝሙር ተብሎ በሚጠራዉ መጽሃፉ በመሐልይ መሓልይ ላይ ደጋግሞ ተመለሺ ተመለሺ እያለ ሲዘምር እናያለን፡፡ሰሎሞን ማለት የቃሉ ትርጉም መስተሳልም የሰላም ሰዉ ሰላማዊ ማለት ነዉ፡፡(፪ኛ ሳሙ12፤24) ይህም የሆነበት ዘመኑ እርቀ ሰላም የተደረገበት ስለሆነ ነዉ፤ አባቱ ዳዊት ግዚአብሔር ጋር: እግዚአብሔርም ከዳዊት ጋር በታረቁበት ዘመን ስለተወለደ መስተሳልም ሰላማዊ  እንዲሁም ይዲዲያ ወይም በእግዚአብሔር የተወደደ ተብሏል፡

ሶሎሞን ይህንን ቃል ስለብዙ ተናግሮታል ፡
፩. አንድም ወዳጄ ዉበቴ ሱላማጢስ ሆይ ተምልሺ ያለዉ ቤተ እስራዔልን  ከግብጽ ተነስተሽ ወደ ከነአን ተመለሺ ፤” የሕዝቤን ግፍ አየሁ መቃተታቸዉንም ሰምቼ ላድናቼዉ ወረድኩ” እንዲል ስደቱ ባርነቱ ይበቃል ከግዞት ወደ እረፍት ተመለሺ ሲል ነዉ፡፡
አንድም እግዚአብሔር በቂሮስ በዳሪዮስ አድሮ በዮሴእ በዘሩባቤል አድሮ ቤተ እስራዔልን ከባቢሎን ተመለሺ ሲል ነዉ፡፡እስራዔል ፍርድ በማጓደላቸዉ ደሃ በመበደላቸዉ የ አባቶቻቸዉን አምላክ እግዚአብሔርን ረስተዉ ሃጢያትን በመስራታቸዉ በቃለ እግዚአብሔር በማፌዛቸዉ እገዚአብሔርን አስቆጡት “’ ትዉልድ ሁሉ ወደ አባቶቻቸዉ ተከማቹ ከዚያም በሐላ እግዚአብሄር ለ እስራዔል ያደረገዉን ስራ ያላወቀ ሌላ ትዉልድ ተነሳ””(መሳ 2፤10) ተብሎ እንደተጻፈ፡፡  ያለ እግዚአብሔር ግን ምንም ማድረግ አይቻልም። ዮሐ 15፤5  ይህንን በማድረጋቸዉ እግዚአብሔር  አረመኔዎችን ጨካኞችን አሕዛብ ከለዳዉያንን አስንስቶ  ብዙዎችን በሰይፍ አጠፋቸዉ ፤ ከሰይፍ የተረፉትን ደግሞ በነቢዩ በኤርሚያስ የተነገረዉ ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ለ70 ዘመን ያህል ወደ ባቢሎን በምርኮ ፤ በግዞት እነዲሰደዱ አደረጋቸዉ፡፡ (2ኛ ዜና 36፤14-21)  አምላካችን እግዚአብሔር ወደ ተጨነቁት ወደ ተገፉት  ወደ ሃጥአን መሔድ ግብሩ ነዉና ደግሞም እስራዔል የበኩር ልጆቹ ናቸዉና ይሳሳላችዋል ፤ በ ኤርሚያስ የተነገረዉ ትንቢት ሲፈጸም ከ70 ዘመን የባቢሎን ስደት ተነስተሽ ወደ ኢየሩሳሌም ሃገርሽ ማርና ወተት ወደ ምታፈሰዉ ምድር ተመለሲ፡፡
፪. ወዳጄ ሱላማጢስ ሆይ ተመለሺ ተመለሺ  ያለዉ ስለ አዳምና ስለ ልጆቹ ነፍስ ተገብቶ ነዉ  ፤ አዳምና ሔዋን እጸ በለስን ቀጥፈዉ በመብላታቸዉ ምክንያት በሞተ ስጋ ላይ ሞተ ነፍስ ፤በርደተ መቃብር ላይ ርደተ ሲኦል ተፈርዶባቸዉ እሰከነ ልጅ ልጆቻቸዉ ለ5500 ዘመን በሲኦል በደይን ተሰደዉ ይኖሩ ከነበረበት ፤ እነሆ አምላካችን ክርስቶስ በተራራዉ በኮረብታዉ እያስተማረ መጥቷልና ሱላማጢስ ሆይ ተመለሺ ፤ በተራራዉ በኮረብታዉ አለ በትዕ ቢተኞቹ በፈሪሳዉያን መካከል እንደ ባለስልጣን እያስተማረ መጣ ፤ አንድም በተራራ በሐዋርያት ፤ በኮረብታ በ72 ቱ አርድእት አድሮ እያስተማረ  መጥቷልና ሱላማጢስ ሆይ ተመለሺ፡፡ ለ5500 ዘመን በሲዖል ስትሰቃይ ስትባዝኝ የነበርሽ ነፍስ ተነሺ ወደ ቀደመ ቦታሽ ወደ ገነት ተመለሺ፡፡

፫ .ወዳጄ ሆይ ተነሺ  ሱላማጢስ ሆይ ተመለሺ እያለ ደጋግሞ ጥሪዉን የሚያተስተላልፈዉ  ለእመቤታችን ነዉ፡፡ የፊቱ ሚሰጥር ተገልጾለት በመንፈስ ቅዱስ መነጽርነት ስደቷን አይቶ የግብጽ ሀገር  ስደቱ ይብቃሽ አሁን ጊዜዉ ደርሷልና ወደ ሃገርሽ ወደ ናዝሬት ተመለሺ ይላታል፡፡ እመቤታችን ከሃላ “የሄሮድስ ወታደሮች ይደርሱብኝና ልጄን ይገሉብኝ ይሆን እያለች “ በስጋት ከፊት የምትደርስበትን ስፍራ ሀገር፤ ሕዝብ ፤ሁኔታ ስለማታዉቅ በጭንቅ አስቸጋሪዉን በረሃ  በእግር አቋረጠች፡፡በረሀብና ጥም እየተቸገረችም ጭምር በሰዉ ሃገር ተንከራተተች፡፡  ፍጥረት ሁሉ አንተን ተስፋ ያደርጋል አንተም በየጊዜዉ ምግባቸዉን ትሰጣቸዋለህ “ ተብሎ መጋቤ አለም እንደሆነ የተነገረለት አምላክ ወልድ አምላክን ታቅፋ ፡ መራቧ በየሰዉ ደጃፍ ቆማ ቁራሽ መለመኗ ፡ ከዐለት ዉሃ አፍልቆ የሚያጠጣዉን ይዛ መጠማቷ ፡ እንደ እሳት የሚጋረፈዉን የሰዉ አይን በትዕግስት ማሳለፏ: ልብ ስርስሮ የሚገባዉን የክፉዎችን ስድብ  ነቀፋ ስምታ መቻሏ ባጠቃላይ ገና ብላቴና ሳለች መሰደዷና ያን ሁሉ መከራ መቀበሏ አለሙን ሲያሲደንቅ ይኖራል፡፡ ምክንአቱም ሌላዉ ፍጥረት ቢሰደድ በሀጢያቱ ነዉ ፤ እመቤታችን ግን ጥፋት ሳይኖርባት ተሰዳለችና ይህ ስድቷን የተለየ ያደርገዋል፡፡











No comments:

Post a Comment