Thursday, November 12, 2020

ዳግሚት ሔዋን (አዲሲቱዋ ሔዋን )




ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር << በአንተና በሴቲቱ በዘርህና በዘርዋ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ : እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል አንተም ሰኮናውን ትነክሳለህ :: >> ( ዘፍ ፫፥፲፭ ) ሲል የተናገረው ይህ ተስፋ ትንቢት መፍቀሬ ስብእ የሆነው አምላክ ለሰው ልጆች ያለውን አምላካዊ የአድኅኖት ዕቅድና በጎ ፈቃድ የሚገልጥ መሪ የተስፋ ቃል ነው :: #በመሆኑም ይህ አምላካዊ ተስፋ ትንቢት በምክረ ከይሲ ተታለው በኃጢአት ተሰናክለው በመንጸፈ ደይን ወድቀው በእግረ አጋንንት ይጠቀጠቁ ለነበሩት ለአባታችን አዳምና ለእናታችን ሔዋን እንዲሁም ለልጆቻቸው ሁሉ የተሰጠ የመጀመሪያ አምላካዊ የድህነት ተስፋ ነው :: ስለሆነም መጽሐፍ <<ተፈጸመ ተስፋ አበው በማርያም ድንግል ወበቀራዮ ተተክለ መድኃኒት መስቀል ፤ የቅዱሳን አበው ተስፋ ድኅነት በቅድስት ድንግል ማርያም ተፈጸመ : የድኅነተ ዓለም ሥራ የተፈጸመበት መድኃኒት መስቀልም በቀራንዮ ተተከለ >> እንዳለው ወላዲተ አምላክ የዚህ ቃለ ትንቢት ፍጻሜ መሠረት መሆኑዋን የመለክቱዋል :: ከላይ የተጠቀሰው ምስጢረ ድኅነተ አለም ፣ቃለ ትንቢት ለጊዜው በቀዳሚነት ሔዋንና በጥንተ ጠላታችን በዲያቢሎስ መካከል ያለውን ጸብና ክርክር የሚያሳይ ሲሆን ፍጻሜ ምሥጢሩ ግን በዳግሚተ ሔዋን (አዲሲቱዋ ሔዋን ) በወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያምና ምክንያተ ስህተት በሆነው በሰይጣን መካከል የሚኖረውን ጠላትነት የሚገልጥ ነው :: (ራእ፲፪፥፩-፲፯) ከዚህም ሌላ የሴቲቱ (የድንግል ማርያም ) ዘር በሆነው በአምላካችን በመድኃኒታችን በፈጣሪያችን በኢየሱስ ክርስቶስና በሠራዊተ አጋንንት መካከል የሚኖረውን ጠላትነትም ያስረዳል :: ይህም ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት <<አንተም የዘንዶውን ራሶች ቀጠቀጥህ >> (መዝ ፸፫፥፲፬) ባለው መሠረት የድንግል ማርያም ልጅ መድኅነ ዓለም ክርስቶስ ጥንተ ጠላታችን የሆነውን የዲያቢሎስን ራስ በመስቀል ላይ ቀጥቅጧል :: በአንጻሩ ደግሞ << እጆቼንና እግሮቼን ቸነከሩኝ >>(መዝ ፳፩፥፲፮)ተብሎ እንደተጻፈ ጠላት ዲያቢሎስ በአይሁድ ልቡና አድሮ የአምላካችን የመድኃኒታችን የፈጣሪያችንን ቅዱሳት እግሮች በቀኖት አስቸንክሯል (ዮሐ ፲፱፥፳፫):: ታላቁ ሐዋርያ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስም ይህንን ድንቅ ምስጢረ ድኅነት አስመልክቶ ሲናገር <<ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ እግዚአብሔር ልጁን ላከ ከሴትም ተወለደ :: እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ ከሕግ በታች ያሉትን ይዋጅ ዘንድ >> (ገላ፬፥፬-፭) በማለት መስክሯል :: በዚህም ሐዋርያዊ ቃል መሠረት ከላይ የገለጽነው የድኅነተ ዓለም ተስፋ በቅድስት ድንግል ማርያም እንደተፈጸመ ልብ ይሏል :: ዳግመኛም በቅዱስ ወንጌል እንደተጻፈው አምላካችን ጌታችን መድኃኒታችን ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያምን የመጀመሪያውን ተአምር ባደረገበት በገሊላ ቃና ሠርግ ቤት በ(ዮሐ፪፥፬ 4) እንዲሁም የድኅነተ ዓለም ሥራን በፈጸመበት በቀራንዮ መስቀል ላይ (ዮሐ፲፱፥፳፮) "" አንቺ ሴት "" ሲል መጥራቱ አስቀድሞ ለሰው ልጆች የሰጠው የድህነት ተስፋ በእርዋ በኩል መፈጸሙን በምሥጢር ያጠይቃል :: በቀዳሚት ሔዋንና በዳግሚት ሔዋን በእመቤታችን መካከል ያለውን ምሥጢራዊ ንጽጽር በየዘመኑ የተነሡ የተለያዩ አበው ሊቃውንት መተርጉማን አምልተውና አስፍተው ገልጸዋል :: ይህውም ቀዳሚት ሔዋን ለፈቃደ እግዚአብሔር ባለመታዘዙዋ ምክንያት በመላው የሰው ዘር ላይ መርገምንና ሞትን አምጥታለች :: በአንጻሩ ደግሞ ዳግሚት ሔዋን የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለፈጣሪዋ ፈቃድ በመታመኑዋና በመታዘዙዋ ምክንያት በመርገምና በሞት ጥላ ሥር ወድቆ ለነበረው ዓለም በረከትንና ሕይወትን አስገኝታለች :: ይህንን አስመልክቶ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ሲናገር "" በእንተ ሔዋን ተዐጽወ ኖኅተ ገነት ወበእንተ ማርያም ድንግል ተርኅወ ለነ ዳግመ : በቀዳሚት ሔዋን ምክንያት የገነት ደጃፍ ተዘጋብን ዳግመኛም ስለ ዳግሚት ሔዋን ስለ ድንግል ማርያም ተከፈተልን "" በማለት አስገንባል :: ከዚህም ሌላ ሰፊና ጥልቅ በሆነው የነገረ ማርያም አስተምህሮው የዜና አበው ሊቃውንት "" የነገረ ማርያም አባት "" እያሉ የሚጠሩት ታላቁ የቤተክርስቲያን ሊቅ ቅዱስ ሔኔሬዎስ ከላይ የገለጥነውን ኃይለ ቃል መሠረት በማድረግ እመቤታችን "" የሔዋን ጠበቃ አለኝታ "" ብሏታል :: በዜና አበው ክፍለ ትምህርት እንደሚታወቀው ይህ አባት የነበረበት ዘመን "" የነገረ ማርያም ዘመነ ልደት "" በመባል ይታወቃል ::
#እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለነገር ድኅነት መሠረት መሆኗን በመግለጥ የተአምሯ መጽሐፍ "" እግዝእትነ ማርያም ነበረት እምቅድመ ዓለም በኅሊና አምላክ "" ይላል :: ከዚህም ኃይለ ቃል ድኅነተ ሰብእ የሆነው እግዚአብሔር አምላክ አስቀድሞ የፈቀደውና ያሰበው የቸርነቱና የመግቦቱ ሥራ መሆኑን እንረዳለን : እንገነዘባለን :: ከዚህም ጋር ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ "" ወበእንተ ዝንቱ አስተርእየ ወልደ እግዚአብሔር ከመ ይስዐር ግብሮ ለጋኔን : ስለዚህ የዲያቢሎስን ሥራ እንዲያፈርስ የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ "" (፩ኛ ዮሐ ፫፥፰) እንደመሰከረው ጥንተ ጠላታችን የሆነው ዳያቢሎስ በሥጋ ከይሲ ተሠውሮ አዳምንና ሔዋንን እንዳሳተ (ዘፍ ፫፥ ፩-፲፬) አካላዊ ቃል አምላካችን ፈጣሪያችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ ብእሲ ተሠውሮ ወደ ቀደመው ጸግና ክብር መልሷቸዋል :: ይህንን ምስጢር ሊቃውንተ ቤተክርስቲና አሞንዮስና አውሳብዮስ በመቅደመ ወንጌል ሲገልጡ "" ወበከመ ተኃብእ ሰይጣን በጉሕሎቱ ውስተ ሥጋ ከይሲ ከማሁ ኮነ ድኅነትነ በሠውሮተ ቃለ እግዚአብሔር በዘመድነ :ሰይጣን በሥጋ ከይሲ ተሰውሮ አዳምን እንዳሳተው ጌታችን መድኃኒታችን ፈጣሪያችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም በስጋ ብእሲ ተሰውሮ መጥቶ ዓለምን አዳነ "" በማለት ተናግረዋል :: በዚህም ትርጉዋሜ ምስጢር መሠረት የሰው ልጅ በምክረ ከይሲ ተታሎ ሕገ እግዚአብሔርን አፈረሰ በሀጢያቱም ምክንያት ከፈጣሪው አንድነት ተለየ ሲባል በአካለ ተደልሎ በልሳነ ከይሲ ተታሎ መሳቱን መናገር ነው :: ስለሆነም ጥንተ ጠላታችን ዲያቢሎስ አካለ ከይሲን መሰወሪያ ልሳነ ከይሲን መናገሪያ አድርጎ በማሳቱ በማኅደሩ ኃዳሪውን መናገሩ እንጂ ለሰው ልጅ ስሕተት ምንጩና መሠረቱ ራሱ ዲያቢሎስ መሆኑን መረዳት ያሻል ::
#ቤዛዊት ዓለም ድንግል ማርያም በዘመነ ብሉይ በተለአየ ኅብረ አምሳል መገለጧና በብዙ ዓይነት ኅብረ ትንቢት መነገሯም በነገረ ድኅነት ውስጥ ያላትን ሰፊ ድርሻ በጥልቀት ያስረዳል :: በዚህም መሠረት የነገረ ማርያም ትምህርት ከነገረ ድኅነት ትምህርት ጋር የተያያዘ ጥልቅ ምሥጢር እንዳለው ልብ ይሏል :: የመጋቤ ሐዲስ የቅዱስ ገብርኤል ዜና ብሥራትና የእመቤታችን ተአምኖና ተአዛዚተ እግዚአብሔር መሆን የመሲሕ ክርስቶስን ወደዚህ ዓለም መምጣትና የአዲስ ኪዳንን መጀመር ያበሥራል :: በአጠቃላይ ይህንን ታላቅና ድንቅ ምስጢር በተመለከት አራቱ ወንጌላውያን ይልቁንም ደግሞ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ የእመቤታችንን ሁለንተናዊ ሕይወት በመግለጥ በልዑል እግዚአብሕሄር ፊት ያላትን ክብርና የባለሟልነት ሞገስ እንዲሁም ከመልአከ ብሥራቷ ከቅዱስ ገብርኤል ጋር ያደረገችውን ቃለ ምልልስ በሰፊው ተናግሮላታል ::
#በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የነገረ ማርያም አስተምህሮ አምላካዊ የድኅነት ዓለም ጉዞ በማህጸነ ድንግል እንዲጀምር ምክያትና መሠረት የሆነው የመልአከ ሰላም የቅዱስ ገብርኤል ዜና ብሥራት አስቀድሞ የሰው ልጆች በኃጢያት የወደቁበትን መርገምና ሞት ወደ ዓለም የገባበትን የመልአክ ጽልመት የዲያቢሎስን ተንኮል የሻረና ክፉ ምክሩንም ያፈረሰ የበረከትና የሕይወት መንገድ ነው :: በመሆኑም በእመቤታችን በድንግል ማርያም አማካይነት የተፈጸመው የሥጋዌ ምሥጢር መፍቀሬ ሰብእ የሆነው ቸሩ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያለውን ጥልቅ ፍቅር የገለጠበት ታላቅ የድኅነት ምሥጢር ነው :: በቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጸው የመጀመሪያዪቱ ሔዋን በምክረ ከይሲ ተታልላ የጠላት ዲያቢሎስን ክፉ ምክር ሰምታ በመቀበሏ ምክንያት ለሰው ልጆች ድቀት (ውድቀት ) እንዲሁም የሞት ፍርድ ምክያት ሆናለች ( ዘፍ ፫ ፥፬-፮) :: በአንጻሩ ደግሞ ዳግሚት ሔዋን የተባለችው ቅድስት ድንግል እመቤታችን በልዑል እግዚአብሔር ፊት በባለሟልነት የሚቆመውን መልአከ ሰላም ቅዱስ ገብርኤልን ቃለ ብስራት ሰምታ "" ይኩነኒ በከመ ትቤለኒ : እንደቃልህ ይሁንልኝ ይደረግልኝ "" ብላ በእምነት በመቀበሏ ምክንያት ድኅነት ሆነችን :: ይህን ቃሏን ምክንያት አድርጎም አካላዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድ ከሥጋዋ ሥጋ :ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ በማኅጸኗ አደረ :: በመሆኑም ቀዳሚት ሔዋንን ምክንያተ ስሕተት : ምክንያተ ሞት በመሆኗ ሲወቅሳትና ሲከሳት የነበረው የሰው ዘር በሙሉ ምክንያተ "" ድኅነት ምክንያተ በረከት ወሕይወት የሆነች ዳግሚት ሔዋን እመቤታችንን << ብፅዕት አንቲ እንተ ተአምኒ ከመ ይከውን ቃል ዘነገሩኪ እምኅበ እግዚአብሔር ፤ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልከው ከእግዚአብሔር ዘንድ አግኝተው የነገሩሽ ቃል እንዲፈጸም የምታምኚ አንቺ በእውነት ብጸዕት ነሽ ንዕድ ክብርት ነሽ >>(ሉቃ ፩፥ ፳፰-፴፰) እያለ የሚያመሰግናት ሆኗል :: ከላይ እንደተገለጠው ወላዲተ አምላክ የቅዱስ ገብርኤልን ዜና ብሥራት ሰምታ በማመኗ ምክንያት መድኅነ ዓለም ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም ስለመጣ ብሥራተ መልአክ የብሉይ ኪዳን አምሳልና ትንቢት ፍጻሜ ወይም መደምደሚያ ሆነ :: ይህንን ታላቅና ድንቅ ሚስጢር አስመልክቶ የቤተክርስቲያናችን የነገረ ማርያም መጽሐፍ ሲናገር "" ወቅዱስ ገብርኤል በቃለ ብሥራቱ ኅተመ ትንቢትዮሙ ለነቢያት :: ገብርኤል ውእቱ ዘአፈልፈለ ስቴ ፍሥሐ ለኩሉ ዓለም ወአብጠለ እማልባበ ሰብእ ኩሉ ስቴ ኃዘን መሪር ዘየአኪ እምሕምዘ አፍሀት ዘይቀትል "" ይላል :: ይህም ማለት "" ቅዱስ ገብርኤልም በምሥራቹ ቃል የቅዱሳን ነቢያትን ትንቢት አተመ :አጸና : ፈጸመ : ዘጋ : አረጋገጠ :: ለዓለም ሁሉ የደስታ መጠጥና ምንጭን ያፈለቀ : ያስገኘ : ያመነጨ : ገዳይ ከሆነ የእባብ (የአውሬ ) መርዝም የሚከፋ መራራ የኃዘን ውኃን (መጠጥን :ምንጭን ) ከሰው ሁሉ ልቡና ያስወገደ ያራቀ ይህ ቅዱስ ገብርኤል ነው "" ማለት ነው :: በዚህም መሠረት ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ የጻፈው የነገረ ብሥራት ምሥጢር ለኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን የንገረ ሥጋዌ ትምህርት ምንጭ ለሆነው የነገረ ማርያም ትምህርት ዐቢይ መሠረት ጥሏል :: ከዚህ በተጨማሪም ብሥራተ መልአክ የሰው ልጆችን አስከፊ የኃጢያትና የመርገም ታሪክ የቀየረ ታላቅ ክስተት በመሆኑ ለቤተክርስቲያናችን ጥልቅ የነገረ ድኅነት አስተምህሮ በቂ ማስረጃና ምስክር ነው :: እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለመልአኩ ዜና ብስራት በሰጠችው ቃለ ተአምንሮ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር ከጥንት ያሰበውና የፈቀደው ያድህነተ ዓለም ሥራ እንዲፈጸምና አማናዊ እንዲሆን አድርጋለች :: ይህም ወላዲተ አምላክ በነገረ ድኅነት ውስጥ ያላትን ታላቅ ሱታፌ በጉልህ ያሳያል :: ይህንን ምሥጢር በተመለከተ ኢትዮጵያዊው ሊቅ በድርሰቱ "" ዘበቃለ ጉሕሎቱ ለሰይጣን መልአክ ስሕተት ተሰፍሐ ግላ ጽልመት ውስተ ኩሉ ዓለም :ወበቃለ ብሥራቱ ለገብርኤል መልአክ ጽድቅ ተሰፍሐ ብርሀነ ሕይወት ውስተ ኩሉ ዓለም : የስሕተት አለቃ በሆነው በሰይጣን የክፋትና የጥፋት ቃል ምክንያት የጨለማ መጋረጃ በዓለም ሁሉ እንደተዘረጋ : የእውነት መልአክ በሆነው በቅዱስ ገብርኤል የምሥራች ቃል ደግሞ የሕይወት ብርሀን በዓለም ሁሉ ተዘረጋ በማለት መስክሯል :: ኢትዮጵያዊው የዜማ ሊቅ ቅዱስ ያሬድም እመቤታችን በነገረ ድህነት ውስጥ ያላትን ልዩ ሥፍራ ሲናገር "" በእንተ ተሠግዎቱ ለወልደ አምላክ እምኔኪ ቀሩባነ ኮነ እምድር ውስተ አርያም :ብኪ ወበከመ ወልድኪ "" ብሏል :: የዚህ ኃይለ ቃል ትርጉዋሜ ምሥጢርም ቃለ እግዚአብሔር ወልድ ከሥጋሽ ሥጋ :ከነፍሥሽ ነፍስን ነሥቶ ካንቺ ሰው በመሆኑ ከምድር ወደ ሰማይ :ከሞት ወደ ሕይወት : ከመርገም ወደ በረከት : ከኃሳር ወደ ክብር : ከሲኦል ወደ ገነት የተሸጋገርንብሽ ማለት ነው :: ከላይ የተጠቀሰውን በቃዲምት ሔዋንና በዳግሚተ ሔዋን መካከል ያለውን ምሥጢራዊ ንጽጽር አስመልክቶ
'' ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ ""በመባል የሚታወቀው ሊቁ ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ሲገልጽ "" ለእመ ኃሠሥላ ለሔዋን ትረክባ በህየ እንዘ ትትፌሣሕ በወለታ ዘእምጽአት ፈውሰ ለቁስሊሀ : ለእመ ኃሠሦኮ ለአዳም ረክቦ በህየ እንዘ ይትፌሣሕ ወይገብር በዓለ ምስለ ዳግማዊ አዳም "" በማለት በንጽጽሩ ውስጥ ያለውን ጥልቅና ረቂቅ ምሥጢረ ድህነት አስተምሯል :: እንደ ሊቁ አገላለጽ ዳግሚት ሔዋን የተባለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ፍሬ ሕይወት ወመድኃኒት የሆነው ጌታ የተገኘባት አማናዊት ዕጸ ሕይወት በመሆኗ የዕጸ በለስን ፍሬ በልታ ሞትን ላመጣችብን ለቀዳሚቷ ሔዋን ካሣ ናት :: ምክንያቱም ከዳግሚት ሔዋን ከድንግል ማርያም የተወለደው የማኅጸኗ ፍሬ ጌታችን መድኃኒታችን አምላካችን ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሚያርቅ :በረከተ ሥጋ :በረከተ ነፍስን የሚያድል ሕይወተ ሥጋን ሕይወተ ነፍስን የሚሰጥ : ቀዳሴ ሥጋ ወነፍስ ወመንፈስ የሆነ ቡሩክ አምላክ ነውና ::
ወስብሀት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን ::


ሐኪሙ ወንጌላዊ(ቅዱስ ሉቃስ)

================
ሐኪሙ ወንጌላዊ በማለት ሊቃውንት የሚጠሩት ቅዱስ ሉቃስ ነው። ቅዱስ ሉቃስ ሀገሩ አንጾኪያ ነው፡፡ አስቀድሞ ከ፸፪/72ቱ አርድእት ወገን የተቆጠረ ሲሆን ከበዓለ ሃምሳ በኋላ ወደ አንጾኪያ ወርዶ ወንጌልን ሰብኳል ከሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎሰ ጋር የተገናኘውም በዚሁ ነው፡፡ ቅዱስ ሉቃስ የሕክምና ሙያ የነበረው ሲሆን ያጠናውም ከአቴናና እስክንድርያ ሊቃውንት መሆኑ ታውቋል፡፡ ከዚህ ሙያው በተጨማሪ የሥነ-ሥዕል ችሎታም እንደነበረው ይነገራል፡፡ይህንን ችሎታውንም በወንጌሉና በሐዋርያት ሥራ መጽሐፉ ላይ ባለው ሥዕላዊ አገላለጥ ከማንጸባረቁም ሌላ በእጁ የተሳሉ ሥዕሎች በተለያዩ ሀገሮች ይገኛሉ፡፡
የቅዱስ ሉቃስ ስዕሎች እመቤታችን ልጇን አቅፋ ( ምስለ ፍቁር ወልዳ) የሳላቸው ሲሆኑ በኢትዮጵያ በተድባ በማርያም ፤ በደብረ ዘመዶ ፤ በዋሸራ ፤በጅበላ ሲገኙ ተመሳሳዩም በስፔን ቅድስት ማርያም ካቴድራል እንደሚገኝ ይነገራል ፡፡
ቅዱስ ሉቃሰ የድንግልና ሕይወት የነበረው ወንጌላዊ ነው፡፡ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በሰማዕትነት እስካረፈበት ጊዜ ድረስ ደቀ መዝሙር በመሆን አገልግሎታል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በ67 ዓ.ም. በሮማ በሰማዕትነት ሲያርፍ ሉቃስ ወደ ድልማጥያ መጣ፡፡ በዚያም በሽምግልና ዘመኑ ወንጌልን በመስበክ ላይ እያለ አይሁድና ካህናተ ጣዖት ተባብረው ትምህርቱን በመቃወም ተነሡበት፡፡ መስከረም 20 ቀን 68 ዓ.ም. አይሁድና አረማውያን ጉባዔ አድርገው ነገር በመሥራት ለሮም ንጉሥ ከሰሱት፡፡ በዚያን ዘመን ኔሮን እብደቱ ያየለበት ጊዜ በመሆኑ የቅዱስ ሉቃስን ከሮሜ ማምለጥና ወደ ድልማጥያ መምጣት ሲሰማ 200 ወታደሮችን ላከበት ቅዱስ ሉቃስም የሰዎችን መምጣት በመንፈስ ቅዱስ ተረድቶ ያሰተምራቸው የነበሩትን ምእመናን ወደየቤታቸው ላከና በድልማጥያ አጠገብ
ወደሚገኘው ባሕር ተጠጋ፡፡
በባሕሩ አጠገብ አንድ ዓሣ አስጋሪ ቆሟል፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ወደ ዓሣ አስጋሪው ቀረበና ጨዋታ ጀመሩ፡፡ ቀስ በቀስም ወንጌል ይሰብክለት ጀመር፡፡ ዓሣ አስጋሪውም ቅዱስ ሉቃሰ የሚነግረውን ሁሉ ሥራውን አቁሞ በደስታ ያዳምጠው ነበር፡፡ በመጨረሻ እንካ እነዚህ የሕወትን መገንድ ይመሩሃል አለና የያዛቸውን መጻሕፍት ሁሉ ሰጠው፡፡ ያም ዓሣ አስጋሪ እጅግ ተደስቶ ዕቃ በሚያስቀምጥበት ቦታ በክብር አኖራቸው፡፡
ቅዱስ ሉቃሰ መጽሐፉን ሰጥቶት ዘወር ሲል የኔሮን ወታደሮች ተረባረቡና ያዙት፡፡ ከዚያም ወደሮም ተወሰደና የኔሮን ፍርድ ቤት ቀረበ፡፡ ጥቅምት 22 ቀን አንገቱን ተሠይፎ በአሸዋ በተሞላ ከረጢት አስገብተው በተወለደ በ84 ዓመቱ ወደ ባሕር ወረወሩት፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍቱን ግን ያ ዓሣ አስጋሪ ለዚህ ትውልድ አትርፏቸዋል፡፡
የቅዱስ ሉቃስ ወንጌል ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃሰ በዓይኑ የተመለከተውን ከሐዋርያትም የሰማውን ጠንቅቆ በማሰብ 24 ምዕራፍ፣1149 ቁጥሮች የያዘ ወንጌል አበርክቶልናል፡፡ ወንጌሉን የጻፈው ከ58-60 ዓ.ም. ባው ጊዜ ውስጥ ቅዱስ ጳውሎስ በእሥር ላይ ባገኘው ዕረፍት መሆኑ ይነገራል፡፡ ወንጌሉ የተጻፈው በግሪክ ቋንቋ ነው።
የሐዋርያት ሥራ የሐዋርያት ሥራን የጻፈው ቅዱስ ሉቃስ ነው፡፡ ቅዱስ ሉቃስ በወንጌሉ ከ1-34 ዓ.ም. ያለውን የክርስትና ታሪክ ካሰፈረ በኋላ ቀጣዩንና ከ34-58 ዓ.ም. ያለውን ደግሞ
በሐዋርያት ሥራ መጽሐፉ ላይ ጽፏል፡፡
ከምዕራፍ 1-8 ያለው የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ በኢየሩሳሌም የሚያሳይ ሲሆን ከምዕራፍ 9-12 ያለው ታሪክ ደግሞ በእስጢፋኖስ ሰማኝትነት በተነሣው ስደት የተበተኑት የኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን ልጆች በአካባቢው ያደረጉትን ሐዋርያዊ ጉዞ የሚያሳይ ነው፡፡ ከምዕራፍ 13
ጀምሮ እስከ ፍጻሜው ደግሞ የቅዱስ ጳውሎስን ጉዞዎች ተከትሎ የጻፈውና ክርስተና በታናሿ እኪያር በአውሮፓ እንዴት እንደተሰበከ የሚያሳየው ክፍል ነው፡፡ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በመጀመሪያው የሮም እሥራቱ በቁም እሥር ላይ ሆኖ ወንጌልን እንዲሰብክ ተፈቅዶለት በነበረ ሰዓት በሮም ከሚኖሩ አይሁድ ጋር በ58 ዓ.ም ስለሃይማኖት ያደረገውን ውይይት ተርኮ ያጠናቅቃል፡፡ ወንጌላዊው ሉቃስ የሐዋርያት ሥራን የጻፈው በ58/በ59 ዓ.ም/ ነው፡፡
ጥቅምት ፳፪ ቀን የበዓሉ መታሰቢያ ነው።
የቅዱሱ በረከት በእጥፍ ይደርብን።


 አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን

አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን በ330 ዓ.ም በሐዋርያው ቅዱስ አትናቴዎስ እጅ ጵጵስና የተሾሙበት ዕለት ነው፡፡ ይኸውም ቅዱስ ጌታችን ‹‹ኢትዮጵያን ከጨለማ አውጥተህ በሃይማኖት ስለ አበራሃት ከፍ ያሉ ክብራትንና ማዕረጋትን ፈጽሜ ሰጠሁህ›› በማለት ታላቅ ቃልኪዳን የሰጣቸው እጅግ የከበሩ ነገር ግን ቤተ ክርስቲያናችን እንደሚገባቸው መጠን ያላከበረቻቸው የመጀመሪያው አባታችን ናቸው፡፡

አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን፡- ቅዱስ አባታችን አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በኋላ በ245 ዓ.ም በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ህዳር 26 ቀን ሲወለዱ ታላቅ ብርሃን ከሰማይ ወርዶ ለ7 ቀናት አብርቷል፡፡ ቅዱሳን መላእክትም ወደ ምድር ወርደው በመወለዳቸው ታላቅ ደስታን አድርገዋል፡፡ በተወለዱም ጊዜ ‹‹ለአብ ስግለት ለወልድ ስግደት ለመንፈስ ቅዱስ ስግደት ይገባል፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን ለአወጡኝ ቅድመ ዓለም ለነበሩ ዛሬም ላሉ ዓለምን አሳልፈው ለሚኖሩ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል ብለው ዳግመኛም አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ›› ብለው ፈጣሪያቸውን በአንድነት በሦስትነት አመስግነዋል፡፡
ቅዱስ አባታችን በሌላኛው ስማቸው ፍሬምናጦስ እየተባሉ ይጠራሉ፡፡ በ40 ቀናቸው ጌታ በተጠመቀበት በዮርዳኖስ ያጠመቋቸውና ስመ ክርስትና የሰጧቸው ሊቀ ጳጳስ ‹‹ይህ ሕፃን ለኢትዮጵያውን ሁሉ ብርሃን ይሆንላቸዋል›› በማለት ትንቢት ተናግረዋል፡፡ በሊቀ ጳጳሱ በቅዱስ አትናቴዎስ በሚገባ ተምረው ካደጉ በኋላ በ257 ዓ.ም ከኢየሩሳሌም ወደ ኢትዮጵያ ስሙ ሜርጵዮስ ከሚባል ከአንድ ነጋዴ ጋር መጡ፡፡ ከእነሱም ጋር አድስዮስ የሚባል ልጅ ነበር፡፡ ወደ ሀገራችንም ሊመጡ የቻሉት እንዴት ነው? ቢሉ መጀመሪያ ለሰባት ወር በአንድ ሌላ አገር ኖረው ወደ ኢየሩሳሌም ሊመለሱ ሲሉ የበረሃ ሽፍቶች ሜርጵዮስንና ሌሎች መንገደኞችን ገደሏቸውና ሁለቱን ልጆች ማርከው ወስደው ስሙ አልአሜዳ ለሚባል ለአክሱም ንጉሥ ሰጡት፡፡ እርሱም አድስዮስን የቤተክርስቲያን የአልባሳትና የዕቃ ቤት ጠባቂ አድርጎ ሲሾመው ፍሬምናጦስን ደግሞ የቤተክርስቲያንና የሕግ ጠባቂ አደረገው የቤተክርስቲያንን ሥርዓቷንና አገልግሎቷን ጠንቅቆ ያውቅ ነበርና፡፡
በአክሱምም በተጋድሎና በትጋት ኖረ፡፡ ቅዳሜና እሁድ የዛፍ ቅጠሎችን ከመመገብ በቀር ሌላ ምግብ አይቀምስም ነበር፡፡ በየቀኑም አምስት ሺህ ስግደትን ይሰግድ ነበር፡፡ በእርሱም የተጋድሎ ዘመን ደጋግ የሆኑ ነገሥታት አብርሃና አጽብሓ ነገሡ፡፡ እነርሱም ሆኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍሬምናጦስን በጣም ይወዱት ነበር፡፡ አንድ ቀን ፍሬምናጦስ የአክሱሙን ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ሚናስን ‹‹ግዝረትና እምነት በእናንተ ዘንድ አለ ነገር ግን ጥምቀትና ሥጋ ወደሙ መቀበል በእናንተ ዘንድ የለም›› አለው፡፡ ቅዱስ ሚናስም ‹‹ግዝረትንስ አባቶቻችን ሌዋውያን አመጡ፣ በክርስቶስ ማመንን ሕንኬ የተባለች የኢትዮጵያ ንግሥት ጃንደረባ አመጣልን፡፡ ስለ ጥምቀትና ሥጋ ወደሙ ሐዋርያ ወደ እኛ አልተላከም ነገር ግን ያልከውን ሁሉ የሚያደርግልን የሚባርከንና የሚቀድሰን ጳጳስን ታመጣልን ዘንድ ሊቀ ጳጳሱ ወዳለበት ወደ እስክንድሪያ አገር አንተ ሂድ›› አለው፡፡ ጥምቀትስ በጃንደረባው በኩል አገራችን ገብቶ ነበር ነገር ግን ገና ስላልተጠናከና ብዙ ሕዝብም አልተጠመቀም ነበርና አባታችን ፍሬምናጦስ አጠናክሮ ያልተጠመቀውን ሁሉ አጥምቆአል፡፡
ፍሬምናጦስም ወደ እስክንድሪያ ለመሄድ አስቦ ሳለ እንደተኛ ድንግል ማርያም ተገልጣለት ‹‹ዲቁናና ቅስናን መቀበል ይገባሃል፣ ለጵጵስና ተዘጋጅ፣ እግዚአብሔር ይህችን ከፍ ያለችውን ማዕረግ ሰጥተሃልና የልጄ ወዳጅ ሆይ በጸሎትህና በልመናህ በስብከትህም የኢትዮጵያ ሰዎች ሁሉ ይድናሉ፣ በእጅህ ጥምቀትንና ሥጋ ወደሙን ይቀበላሉ›› አለችው፡፡ ጌታችንም እንዲሁ ተገልጦለት ‹‹ወደ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አትናቴዎስ ሄደህ ከፍ ያችውን ማዕረግ ተቀብለህ የኢትዮጵያን ሰዎች አጥምቅልኝ፣ ነቢዩ ዳዊት ስለ እነርሱ ‹ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች› ብሎ ተናግሯልና›› አለው፡፡ እርሱም ቅዱሳኑን ነገሥታት አብርሃንና አጽብሓን አግኝቶ ከእነርሱም ጋር ተማክሮ ወደ እስክንድሪያ ሄዶ በቅዱስ አትናቴዎስ እጅ በአገራችን ላይ ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ታኅሳስ 18 ቀን ተሾመ፡፡ ስሙንም ሰላማ ከሣቴ ብርሃን አለው፡፡ ሰላማ ማለት እግዚአብሔርንና ሰውን የሚያስታርቅ ማለት ነው፡፡ ከሣቴ ብርሃን ማለትም ሃይማኖትን ገልጦ የሚያስተምር ማለት ነው፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስም ከሾመው በኋላ ታቦትና በጣም ብዙ ንዋያተ ቅድሳትንና መገልገያ ዕቃዎችን ሰጥቶ መርቆ በሰላም ወደ ኢትዮጵያ ላከው፡፡
ቅዱሳን የሚሆኑ ሁለቱ ነገሥታትም መምጣቱን በሰሙ ጊዜ ‹‹ኢትዮጵያ ሰዎች ሁላችሁ እስከ 40 ቀን ተሰብሰቡ›› ብለው አዋጅ አስነገሩ፡፡ በደብረ ሲናም ሄደው ተገኛኙትና ከዚያች ቀን ጀምሮ ሕዝቡም ሁሉ እስከ 40 ቀን ድረስ ተጠመቁ፡፡ በዚያችም ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያች በደብረ ሲና አገር ላይ ወረደና ሕዝቡን ሁሉ ባረኮ ተመልሶ ሲያርግ ከአባ ሰላማ በቀር ያየው አልነበረም፡፡ ወደ አክሱምም ሄደው ነገሥታቱም የአድባራት ሁሉ የበላይ የምትሆን የቅድስት ጽዮንን ቤተክርስቲያን በወርቅና በዕንቊ ሠሩና አባ ሰላማ ባርኮ ቀደሳት፡፡ ታቦተ ጽዮንም ከድንኳን ወጥታ ማንም ካህን ሳይሸከማት አብርሃና አጽብሓ ወዳሠሩላት ቤተ መቅደስ ራሷ በመንፈስ ቅዱስ ገብታ ተገኘች፡፡ አባታችንም በእመቤታችንም በዓለ ዕረፍት ቀን ጥር 21 ቀን በውስጧ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲቀድስ ሚካኤልና ገብርኤል በግራ በቀኝ እየተራዱት እርሱም ከምድር ሦስት ክንድ ከፍ ብሎ ሥርዓተ ቅዳሴውን ፈጽሞ ለነገሥታቱና ለሕዝቡም ሁሉ አቆረባቸው፡፡ የዚያን ዕለትም እጅግ ታላቅ በዓልን አደረጉ፡፡
ከዚያም ሌሎችን እየሾመ ወደ ሌላ አገር ካሰማራ በኋላ እርሱም በየሀገሩ በአራቱም አቅጣጫ እየዞረ እያጠመቀና እያስተማረ አብያተ ክርስቲያናትንም እየሠራ ለኢትዮጵያ ሕዝቦች ታላቅ ብርሃን ሆነ፡፡ በየቀኑም እስከ ማታ ድረስ የሚጠመቀው ሕዝብ የሦስት ገበያ ሕዝብ ይሆናል፡፡ በመሸም ጊዜ እንደ ኢያሱ ፀሐይን እያቆመ ሕዝቡን ያጠምቅ ነበር፡፡ መድኃኔዓለምም በየጊዜው በአካል እየተገለጠለት አገልግሎቱን ያፋጥንለት ይባርከውና ቃልኪዳን ይሰጠው ነበር፡፡
አባታችንም በድፍን ኢትዮጵያ በአራቱ አቅጣጫ እየዞረ በተአምራቱ ድውያንን እየፈወሰ፣ ሙታንን እያስነሳ፣ ወንጌልን እያስተማረ፣ እያጠመቀ፣ አብያተ ክርስቲያናትን እየሠራና አገልጋይ የሚሆኑ ቀሳውስትን እየሾመ በሀገራችን ላይ ብርሃንን የፈነጠቀ ለኢትዮጵያ መግለጽ ከሚቻለው በላይ ታላቅ ባለውለታዋ ነው፡፡ ከአባ ሰላማ በፊት እኛ ኢትዮጵያውያን ክርስቶስን ከማመን በቀር ጥምቀትና ሥጋ ወደሙ የመቀበል ልማድ አልነበረንም፡፡ በድንኳን ካለችው ታቦተ ጽዮን በቀርም ታቦታትና አብያተ ክርስቲያናትም አልነበሩንም፡፡ ይሄ ሁሉ ሲታሰብ ከአባ ሰላማ ውለታ አንጻር እንደዋለላት ውለታና እንደሠራላት እጅግ ታላቅ ሥራ ቅድስት ቤተክርስቲያናችን እንደሚገባው መጠን አላከበረችውም ማለት ይቻላል፡፡ ጌታም በመጨረሻ ቃልኪዳን ሲሰጠው ‹‹ስለ ትምህርትህና ስለ ስብከትህ ኢትዮጵያን ከጨለማ አውጥተህ በሃይማኖት ስለ አበራሃት ከፍ ያሉ ክብራትንና ማዕረጋትን ፈጽሜ ሰጠሁህ›› ነው ያለው፡፡ ‹‹ነቢያትና ሐዋርያት ፊቴን አይተው ስለእኔ መረዳት ያቻሉትን አንተ ግን ፊቴን አይተህ ስለ እኔ እንድትረዳ አደረግሁህ፣ ለቅዱሳንም ሁሉ ብርሃናቸው አድርጌሃለሁ›› ተብሎ በጌታችን አንደበት የተነገረለትን ቅዱስ፣ ጻዲቅ፣ መናኝ፣ ሐዋርያ፣ ጳጳስ… ቤተክርስቲያናችን አሁን እያከበረችው ባለው መልኩ ብቻ አልነበረም ማከበርና መዘከር የነበረባት፡፡
በተንቤን ምድር ብቻ በብሕትውናና በጽሙና ሲቀመጥ ቋጥኝ ፈልፍሎ በሠራው ቤተክርስቲያን ላይ የብርሃን መሰላል ተተክሎለት በእርሱም ወደ ሰማይ ወጥቶ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር አጥኗል፡፡ የተንቤንንም ምድር ቡሩካን በሆኑ እጆቹ አንስቶ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ መንበር ፊት አቅርቦ አስባርኳታል፡፡ መልአክም ሰማያዊ መናና ኅብስት እያመጣ ይመግበው ነበር፡፡ ወንጌልንም ካዳረሰ በኋላ በዋሻ ገብቶ በበዓት ተወስኖ ሰውነቱን በመከራ ይቀጣ ነበር፡፡ በጎጃም ክፍለ ሀገር በሞጣ ዓባይ በኩል በምትገኝ ቦታ እያስተማረና ሐዋርያዊ ተልዕኮውን እየተወጣ ሳለ ጊዜው መሽቶ ፀሐይ ልትጠልቅ ስትል እንደ ኢያሱ ገዝቶ ያቆማት ሲሆን ጌታ ግዝቱን እንዲፈታ ከነገረው በኋላ ነው ግትዙን አንስቶላት የጠለቀችው፡፡ በታዘዘውም መሠረት ከጎጃም ወደ ትግራይ ሲሄድ የዓባይን ባሕር በመጠምጠሚያው ለሁለት ክፍሎ ከእርሱም ጋር የነበሩትን አሻግሯቸዋል፡፡ በደመናም ተጭኖ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ሄዶ አይሁድ ቀብረው በደፈኑት በክርስቶስ መስቀል ላይ ጸሎት አድርጎ ሰግዷል፡፡ ከጌታችንና ከእመቤታችንም መካነ መቃብር አፈር ዘግኖ ወደ ሀገራችን በማምጣት በሚያንጻቸው አብያተ ክርስቲያናት ላይ ነስንሶታል፡፡
አባታችን አባ ሰላማ ሐምሌ 26 ቀን ሲያርፍ ነፍሱን መላእክት ያይደሉ ራሱ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ተቀብሎ ከእርሱ ጋር አሳርጓታል፡፡ መላእክትም ሥጋውን ከጌታችንና ከእመቤታችን መቃብር አድርሰው ወደ ደብረ መድኃኒት የመለሱት ሲሆን በመቃብሩም ላይ ብርሃን ወርዶ ለሁሉም ታይቷል፡፡ ነገሥታቱም ከዐረፈ በኋላ ወደ ደብረ መድኃኒት መጥተው ለመካነ መቃብሩ ሲሰግዱ አባ ሰላማም ተገልጦላቸው ከነሠራዊታቸው ባርኳቸዋል፡፡ የሰላማ ከሣቴ ብርሃን በረከታቸው ይደርብን፡፡
ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ይሁን! እኛንም በአማላጅነታቸው የምንታመን የተዋሕዶ ልጆች የሆንን ሁላችንን የአቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃንን ረድኤት በረከታቸውን ያሳድርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡
(ምንጭ፡- ገድለ አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን፣ የመስከረም፣ የግንቦትና የሐምሌ ወር ስንክሳር


 እኔ የምመርጠው ሳይሆን እግዚአብሔር የመረጠው ይሁን

በክርስቶስ የተወደድሽ እህቴ ሆይ መልካም የትዳር ሰው ትፈልጊያለሽ እንግዲያው ሀብትና ገንዘብ ያለው፣ውጫዊ መልኩ ቆንጆ የሆነ ፣ተክለ ስውነቱ ያማረ፣ወይም ሀብታም ፣የተማረ ድልቅቅ አርጎ የሚያኖርሽ አይሁን ምርጫሽ ይልቁንስ እግዚአብሔር ን የሚፈራ ሰውን የሚያከብር ቢሆን ይሻላል።
ምክምያቱም በጥንተ ፍጥረትም ሆነ በሐዲስ ተፈጥሮ ትዳርን የመሠረተ ጋብቻን ያጸና እግዚአብሔር ነው። (ዘፍ2፣18ና ዮሐ2፣1)
ትዳር በሀብት ብዛት የማትወሰን በመልክ ማማር የማትመካ ድንቅ የሕይወት መንገድ የእግዚአብሔር ስጦታ ናት ።
እህቴ ሆይ ! መልኩ ሳይሆን፤ስብእናው ቆንጆ የሆነውን፣ ልብሱ ሳይሆን ልቡ ንፁህ የሆነውን መሻት ነው።
ንፁህ የሆነውን የሕይወት አጋርሽን ከፈለግሽ የምትወጂውን ወንድ ከማንም ጋር አታወዳድሪው። ሃይማኖቱን ያጸና ምግባሩን ያቀና ባል እንዲሆን አስተምሪው።


በትዳርሽ ደስታ እንዲኖርሽ ከፈለግሽ ሕይወትሽን ከማንም ጋር አታወዳድሪው። ባልሽ ማለት የአባትሽ ምትክ ማለት ነው።
ተንከባከቢው እንጂ አትጨቃጨቂው ።ባልሽ የደስታ ምንጭሽ ነው። ከእቅፉ ውስጥ ገብተሽ ሌላ አለም ውስጥ የገባሽ እስኪመስልሽ የሚያስደስትሽ ባልሽ ነው።
ያንቺ ባል ላንች ውብና ቆንጆ ንጉስሽ ነው። አክብሪው በደካማ ጎኑ ገብተሽ አበርችው ኃይል ሁኚው፤ አጠንክሪው።
ከተሳሳተ አስርጂው አርሚው ደስታን ስጪው ፤ብርታት ሁኚው። ያኔ የሕይወት ጣእሙን ታውቂያለሽና።
“ለሁሉም በአምላኩ የሚፀና ወንድ ፈጣሪውን የሚፈራ ትዳሩን ያከብራልና።”
በክርስቶስ የተወደድክ ወንድሜ ሆይ መልክ፣ውጫዊ ውበት ተክለ ሰውነት ትዳር አሆንም፣ ቤትንም አያቆመውም። ወዳጄ ሆይ ልብ በል በጎ ስጦታ ሁሉ ከላይ ከሰማይ ነውና እግዚአብሔርን ደጅ ጥና ተንበርክከህ ጠይቀው። አስተውል ትዳር ማለት የሕይወትን ጣዕም የምታውቅበት የምትደጋገፍበት በሳል የምትሆንበት አባት የምትሆንበት ከብቸኛነት ወጥተህ ሁለተኛ እናት የምታገኛበት፣ ሃሳብህን የምትጋራልህ ፣ መፍትሄ የምትስጥህ የሕይወትህ ማጣፈጫ ደስታን የምትሰጥህ ሴት ከፈለክ መልኳን ሳይሆን ከአስተሳሰቧ፣ ከአለባበሷ ሳይሆን ፈጣሪ ፈሪነቷ ይሁን ምርጫህ።
በክፉው ዘመን ፈጣሪዋን የምትፈራ ሴት ማግኘት መታደል ነውና። መልካም ና እግዚአብሔርን የምትፈራ ሴት የምትፈተነው በክፉው ዘመን ነውና በታመምክ ጊዜ አልጋህን የምታነጥፍልህ ጎንበስ ቀና ብላ የምታስታምምህ፣ በተበሳጨህ ጊዜ የምትታገስህ፣ በሐዘንህ የምታዝን በደስታህ የምትደሰት በመከራህና ገንዘብ በሌለህ ጊዜ በጽናት አብራህ የምትቆይ ባንተ የምትተማመን ፣ተስፋ በቆረጥህ ሰዓት ከጎንህ ሆና የምታጽናናህ እርሷ ከላይ ከእግዚአብሔር የተሰጠች ስጦታ ናት።
ውጫዊ ውበቷን ሳይሆን ለአንተ ያላትን አመለካከት አስብ።
በእርግጥ ውጫዊ ሥነ-ምግባር ለውስጣዊ ማንነት አስተዋጽኦ ይኖረዋልና በዓለም ውስጥ እየኖርን በጥበብ መመላለስ ግድ ይለናል።
ወንድሜ ሆይ ለዘላለም አብሮህ የሚኖረው ንጹህ ልቡናዋና ስብእናዋ ለክርስቶስ ያላት ፍቅር እንጂ መልኳ አይደለም፣ ምክንያቱም እግዚአብሔር ን የምትፈራና ለአምላኳ ልዩ ፍቅር ያላት ሴት ለባሏ በፍቅር ትገዛለች።
ወዳጄ ሆይ ለሕይወትህ ስኬትን ከፈለግህ ዓይንህ ሳይሆን ልብህ ያረፈባትን ሴት አግባ።
ዓይን አዋጅ ነው እንዲሉ አበው ። ዓይን ብዙ ያምረዋልና ልብህን አዳምጥ። ያንተ ሚስት ላንተ ብቻ ቆንጆና ውብ ናት ያንተ ሚስት ላንተ ንግሥት ናት።
ባለቤትህን ከማንም ጋር አታወዳድራት። ራስን ሆኖ መኖር ጥበብ ነው።እንደ ራስ መኖር ብስለት ነው።
ሕይወትህን ከማንም ጋር አታወዳድር ( ትዳርህን) እንደራስህ ሆነህ ከኖርክ ራስህን ከማንም ጋር ሳይሆን ከራስህ ጋር ካወዳደርከው በሕይወትህ ደስተኛ ነው የምትሆነው።
መልክ ትዳር አይሆንም፣ ጎጆን አያቆምም። መጽሐፍ "መልክ ከንቱ ደም ግባትም ከንቱ እግዚአብሔርን የምትፈራ ሴት ግን የምትመሰገን ናት።" (ምሳ 30፤8) ይላልና።


  ቁስቋም

---------

ኀዳር ፮ ቀን እመቤታችን ወደ ግብጽ አገር ተሰዳ ስትመለስ ቁስቋም በምትባል አገር ገብታ ያረፈችበት በዓል ነው፡፡ ከገነት የተሰደደውን አዳም ወደ ገነት ለመመለስ ሲል ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከድንግል ማርያም ከአረጋዊው ዮሴፍና ከሰሎሜ ጋር ወደ ግብጽ ተሰደደ፡፡ ጌታችን ከ፫ ዓመት ከ፮ ወር የግብጽ ስደት በኋላ ወደ እስራኤል እንደሚመለስ አስቀድሞ ነቢየ ልዑል ሆሴዕ በትንቢት መነጽርነት ተመልክቶ “ልጄንም ከግብጽ ጠራሁት ” ብሎ ተናግሯል ሆሴ ፲፩፥፩ በዚህም መሠረት ቅዱስ ዮሴፍ እመቤታችን ከተወዳጅ ልጇ ጋር ይዞ ወደ ገሊላ ተመልሷል ኅዳር ፮ ቀንም ሀገረ ቁስቋም ገብተው አርፈዋል።


መንበረ መንግስት ቁስቋም
ለእግዝአብሔር ካላቸው አክብሮትና ፍርሃት ለቤተ ክርስቲያንና በንግሥና ለሚያስተዳድሩት ህዝብ ካላቸው ፍቅር የተነሣ በህዝቡ “እምዬ” የሚል ስም የተሠጣቸው ንጉሠ ነገሥት አፄ ሚኒሊክ ከባለቤታቸው እቴጌ ጣይቱ ብጡል ጋር ሠራዊታቸውን አስከትለው ከእንጦጦ ቤተ መንግስታቸው ወደ ፍልውሃ እና ወደ ተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ሲንቀሣቀሱ መንበረ ንግስት ቁስቋም ማርያም ቤተ ክርስቲያን በታነፀችበት ሥፍራ ላይ ድንኳናቸውን ተክለው ቆይታ ያደርጉበት ነበር፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን እረፍት ባደረጉበት ሥፍራ እንቅልፍ ሸለብ ያደርጋቸውና አንዲት እጅግ የተዋበች ሴት ልጅ አዝላ በእቴጌ ጣይቱ አማሣል “ይህንን ቦታ ልቀቁልኝ፤ ቤቴን ልስራበት !!” ስትላቸው ያያሉ፡፡ ንጉሡም ከእንቅልፋቸው በመንቃት ያዩትን ሁሉ ለባለቤታቸው ለእቴጌ ጣይቱ ብጡል ይነግሯቸዋል፤ በመቀጠልም በእቴጌ ጣይቱ አምሣል ስለታየቻቸው በስምሽ ሆስፒታል ትሰሪበት ዘንድ ፈቅጄልሻለሁ ብለው ቦታውን ለእቴጌ ጣይቱ ይሰጧቸዋል፤ ከግዜ በኃላ ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒሊክ ስለታመሙ እቴጌ ጣይቱ ባለቤታቸውን ማስታመም ይጀምራሉ፤ አብረዋቸው አባታቸውን ያስታምሙ ለነበሩት ንግሥተ ነገሥት ዘውዲቱ አፄ ምኒሊክ ንጉሡ ያዩትን ራዕይና ሀኪም ቤቱን ለመስራት ያለመቻላቸውን ጭምር ይነግሯቸዋል፡፡ ከጥቂት ዓመታት በኃላ ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒሊክ አርፈው እቴጌ ጣይቱም እንጦጦ በቤተመንግስት ተቀምጠው ከእምዬ ምኒሊክ ጋር ያሣለፉትን ህይወት በማስታወስ አዲስ አበባን ቁልቁል እየተመለከቱ “ነበር እንዲህ ቅርብ ነው ወይ አሉ ይባላል !!” ብዙም ዓመት ሳይቆዩ እቴጌም ባለቤታቸውን ተከትለው አረፉ፡፡
ልጅ ኢያሱ መሪነቱን ይዘው በነበሩበት ሠዓት ከመኳንንቱ፤ መሳፍንቱ እና ሹማምንቱ ጋር በአስተዳደር ባለመግባባታቸው ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ሚኒሊክን ንግሥናቸውን እንዲረከቡ ሲደረግ ራስ ተፈሪ መኰንን አልጋወራሽነትን እንዲረከቡ ተደረገ፡፡ የንግሥና ህይወታቸውን ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ሚኒሊክ በመባል በትረ መንግስታቸውን ከተረከቡ በኃላ እቴጌ ጣይቱ የነገሯቸውን አስታውሰው፤ ዛሬ መንበረ ንግስት ቁስቋም ማርያም ቤተ ክርስቲያን በተተከለችበት ቦታ ላይ ሆስፒታሉን ለመሥራት የመሠረት ቁፋሮ ይጀመራል፡፡ በቁፋሮውም ወቅት አስደናቂ ነገር ይከሠታል፤ ይኽውም “ታቦተ ቁስቋም የሚል ፅሑፍ ያለበት የንግሥት እሌኒ የመዳብ ወንበር እና የብረት መስቀል” ይገኛል፡፡ ንግሥት እሌኒ የአፄ ዘርዓያቆብ እህት ሲሆኑ በ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበሩ ንግሥናቸውም በ1426 ዓ/ም እንደነበረ የኢትዮጵያ ታሪክ ያስረዳናል፡፡ የ492 ዓመት ዕድሜ ያለው ንብረት ከመሬት ተቀብሮ በጥበብ እግዚአብሔር ተጠብቆ ምንም ሳይበላሽ መገኘቱ ድንቅ የእግዝአብሔር ሥራን ያመላክተናል፡፡ በዚህም ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ተደንቀው ንዋየ ቅዱሣቱን መስቀል እና ሌሎቹንም የተገኙትን በታሪከ ነገሥታት በዓታ ለማርያም እንዲቀመጥ ያደርጋሉ፡፡ በቁፋሮው ግዜ በተገኘው ንዋየ ቅዱሣት ምክንያት ሥራው ወደ ተቋረጠው የሆስፒታል ቦታ በመሄድ ቤተክርስቲያን ይሠራ ዘንድ ሕዳር 6 ቀን 1918 ዓ.ም የመሠረት ድንጋይ አስቀመጡ፡፡ መቃኞውም በአስቸኳይ ይሠራ ዘንድ ለራስ ዳምጠው ትዕዛዝ ተሰጠ፡፡
በበጎ ሥራቸውና ካህናትን በመውደዳቸው ምክንያት ዘመነ ካህናት ተብሎ በሚጠራበት ግዜ በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ሚኒሊክ ዘመነ ንግሥና በግብፃዊው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማቴዎስ ፍፃሜ ዘመን በሰሜን አዲስ አባባ ልዩ ስሙ እንጦጦ በተባለ ስፍራ በራስጌ ርዕሰ አድባራት እንጦጦ መንበረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም እና ደብረ ኃይል ቅዱስ ዑራኤል ወቅዱስ ኤልያስ በግርጌ ሀመረ ኖህ ቅድስት ኪዳነ ምህረት እና ቀጨኔ ደብረ ሠላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያንን አዋሣኝ አድርጋ በመሐል ባለ ልዩ ጉብታ (መሶብ) በምትመስል በግማሽ አዲስ አባባን ሊያሣይ በሚችል ቦታ ላይ መቅደስና ቅኔ ማህሌት ያለው መቃኞ ቤተክርስቲያን ሠርተው በትእዛዙ መሠረት አሠርተው ታቦተ ቁስቋም ማርያምንና ታቦተ መድኃኔዓለም እየሱስን ሌሎችንም ንዋየ ቅዱሳት በእጨጌ ተድላና በዓቃቤ ሰዓት መምሬ አበበ ትዕዛዝ በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ሚኒሊክ ካህናትና ዲያቆናት በምዕመናንና ምዕመናት ታጅቦ ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ እና ታላላቅ ሹማምንት በተገኙበት በግብፃዊው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማቴዎስ ባራኪነት ታቦቷ ኅዳር 6 ቀን 1919 ዓ.ም ገባች፡፡ ስያሜዋንም “መንበረ ንግሥት ቁስቋም ማርያም” ብለዋታል፤ የመጀመሪያው አስተዳዳሪም ቄስ ገበዝ ብሥራት ኃ/ማርያም ነበሩ፡፡

















 ምክረ ቅዱሳን

ሀ) "ራስህን በሐሰት አትውቀስ:: ራስን መክሰስ ትህትና አይደለም ታላቁ ትህትና ሰዎች ሲወቅሱህ መታገስ ነው::" /ቅዱስ ስራፕዮን/
ለ) "የማታምንበትን ነገር ለሰው ስትል አትስራው ከሰራኸው እንደምትጠፋበት እወቅ፡፡" /መጽሐፈ ምክር/
ሐ) "አንደበቱን ከቧልት ከሐሜት ያየውንም ምስጢር ከመናገር የሚከለከል ሰው ልቦናውን ከኀልዮ ኃጥያት ያርቀዋል፡፡" /አረጋዊ መንፈሳዊ/
መ) "ጸጋ ቢሰጥህ በተሰጠህ ጸጋ አመስግን ያልተሰጠህን እሻለሁ በማለት የተሰጠህን እንዳታጣ፡፡" /ማር ይስሐቅ/
ሠ) "ራሱን የሚንቅ የሚያቃልል ሰው ከእግዚአብሔር ዘንድ እውቀትን ያገኛል አዋቂ ነኝ የሚል ሰው ከፈጣሪው ጥበብ ይለየዋል፡፡" /አረጋዊ መንፈሳዊ/
ረ) "እግዚአብሔር ሆይ አፈርና ትቢያ ሆኜ ሳለ ጻድቅ አድርገው ከሚቆጥሩኝ ሰዎች አድነኝ::" /አባ እንጦንስ/
ሰ) "ፍጡራንን መርምሮ ማወቅ ካልተቻልን ሁሉን የፈጠረ እርሱን መርምሮ ማወቅ እንደምን ይቻለናል?" /ቅዱስ አትናቴዎስ/
ሸ) "ወርቅ በእሳት እንደሚፈተን ሁሉ የክርስቶስንም ፀጋና ክብር ሳይፈተኑ ማግኘት አይቻልም:: የዚህ ዓለም ፈተናና እሳት ቶሎ ያልፋል ይጠፋል ኃጢያተኞች የሚገቡበት የገሀነም እሳት ግን ለዘለዓለም እንደ ነደደ ይኖራል::" /ቅዱስ ሚናስ/


 ድምጽ በራማ ተሰማ

=============
“እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ የዋይታና የመራራ ልቅሶ ድምፅ በራማ ተሰማ ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች የሉምና ስለ ልጆችዋ መጽናናትን እንቢ አለች ።” (ኤር. 31፡15)
ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች ። ይህች ራሔል የያዕቆብ ሚስት ራሔል ከሆነች እርስዋ በወሊድ ምክንያት ሞተች እንጂ ልጆችዋ ዮሴፍና ብንያም አልሞቱባትም ። በርግጥ በግብጽ ምድር የታነቁት ሕፃናት ትውልዶቿ ናቸውና ከቀኑ በፊት አዝናለች ፣ የፍቅር አንጀቷ ስለ እነርሱ ተላውሷል ማለት ይሆናል ። ይህች ራሔል በግብጽ የባርነት ዘመን የነበረች ከሆነች ድርስ እርጉዝ ሁና ጡብ የሚሠራበትን ጭቃ ስትረግጥ ልጇ ፈትለክ ብሎ ከማኅፀኗ ወጣ ። በዚህ ጊዜ ደንግጣ ብትቆም አስገባሪው፡- “እርገጭው ምን ይለዋል ፣ የሰው ደም እንደውም ያጠነክረዋል” አላት ። በዚህ ጊዜ “በዚህ ሰማይ የእስራኤል አምላክ የለምን!” ብላ እንባዋን ወደ ላይ ረጨችው ። የራሔልም እንባ መንበረ ጸባዖትን አራሰው ። እግዚአብሔርም ለፍርድ ና ለፍትሕ ተነሣ ፣ እስራኤልም ፈረኦንን ሰብሮ የበኩር ልጆችን ከግብጽ ባርነት ነጻ አወጣ።
ዛሬም ራሔል ስለ ልጆችዋ እያለቀሰች ነው። ይህች ራሔል የዘመናት አልቃሾችን ፣ በልጅ ሞት ፣በወገን ሞት የሚተክዙትን ወክላ የቆመች ናት ።
ያቺ ራሔል የዘመናትን የልጆች ሞት ሲገልጥ ይኖራል ። በባቢሎን ምርኮም የእስራኤል ሕፃናት እንደ ጎመን ሲቀረደዱ ፣ እንደ ዛፍ ሲቆረጡ ይህች ራሔል ታወሰች (ኤር. 31፡15) ። ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች ተባለ ። ሄሮድስም የቤተ ልሔም ሕፃናትን ሲፈጃቸው ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች በማለት ቅዱስ ማቴዎስ ያነሣታል (ማቴ. 2፡17) ። ወንጌላዊው ማቴዎስ ያነሣት የመጀመሪያው መራራ ኀዘን መሆኑን ስለመግለጥ ነው ። ሁለተኛ ታሪክ መደገሙን ለማንሣት ነው ። ክፉ ታሪክ ሲደገም ሰው ካለፈው አለመማሩን ያሳያልና ያሳምማል ። ካለፈው ትርፍ እንዳልተገኘ ተገንዝቦ አሁንም ትርፍ የሌለው ነገር መሥራቱ ያሳዝናል ።
ራሔል ዛሬም ያሉትን ፣ በመላው ዓለም በተለይም በኢትዮጵያ ስለ ልጆቻቸው የሚያለቅሱትን አባቶች እናቶች ትወክላለች ። በአገራችን በኢትዮጵያና በቤተክርስቲያን ራሔል ጠፍታም ፣ ልቅሶዋም ነጥፎ አያውቅም ። የዘመናት አልቃሽ ሁና ዛሬም ትጮኻለች ። የዋይታና የልቅሶ ድምፅ በአርያም እየተሰማ ነው ። ባለፉት አርባ ዓመታት እንኳ ስንት ወጣት ረገፈ ። ቀይ ሽብርና ነጭ ሽብር እየተባባለ ስንቱ እንደ ወጣ ቀረ ። ሬሣው የሚያነሣው ጠፍቶ በአደባባይ ዋለ ። እርጉዞች ተገደሉ ፣ ብዙ ወጣቶች የት እንደ ደረሱ ሳይታወቅ ደብዛቸው ጠፋ ። በመቀጠል ለ17 ዓመታት በዘለቀ ጦርነት በሰሜኑ የአገራችን ክፍል ብዙ ወጣት ረግፎ ቀረ ። ይህም ምንም ትርፍ የሌለው የወንድማማቾች እልቂት ነበር ። በ1990 ዓ.ም. “የክፍለ ዘመኑ ኋላ ቀር ጦርነት” ተብሎ በተሰየመው በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል በተደረገ ጦርነት ትውልድ እንደ ወጣ ቀረ ። እነዚያ ወጣቶች እንዳጎደሉ የሚያውቀው ዛሬም ያ ቤተሰባቸው ብቻ ነው ። የእኛ የኢትዮጵያውያን ጸጋችን መርሳት ነውና ረስተናቸዋል ። ላለፉት አርባ ዓመታት ጥቁር ልብስ ያላወለቁ ፣ በኀዘን ምክንያት በሽተኛ የሆኑ ፣ አቅላቸውን ስተው ያበዱ ፣ ከኅዘን የተነሳካሉት በታች ከሞቱት በላይ ነዋሪ ሁነው የቀሩ ብዙ ራሔሎች አሉ ። በዚህ የደም ገንቦ ላይ እንጨምርበታለን ተብሎ አይታሰብም ነበር ። አሁንም እያትረፈረፍነው ነው ። አዎ ጣፋጩ ትረካችን “ኢትዮጵያ ማንንም ወርራ አታውቅም” የሚል ነው። ኢትዮጵያውያን ግን ሲተላለቁ የሚኖሩ ናቸው ። እስከ ሰባት ቤት ደም ከሚቃቡት ጀምሮ ያለ ምክንያት እስከሚፈጁት ወገኖች ድረስ የደም ጥምቀት በአገራችን የተለመደ ሁኗል ። ያለፈው ሳይካስ ሌላ ዕዳ እያመጣን ፣ የወለድናቸው ለአንድ ቀን እንኳ የሰላም ድምፅ እንዳይሰሙ አድርገን እያሸማቀቅናቸው ነው ።
ራሔል ኢትዮጵያ ስለ ልጆችዋ አለቀሰች ። በጠፍ ጨረቃ ፣ በውድቅት ሌሊት በራቸው ተንኳኩቶ ስለታረዱት ፣ በጎሣቸው ምክንያት ስለተፈጁት ምስኪኖች ልቅሶ በአርያም ተሰማ ። እግዚአብሔር ፍርድ ሲሰጥ ሰምተን እንዳልሰማን የሆነውን ፣ እኔን ካልነኩኝ ብለን ያለፍነውን ሁሉ የብይኑ በትር ያገኘናል ። ሁሉም ነገር ካለቀ በኋላ ወሬ ማሯሯጥ ጥቅም የለውም ። ንጹሕ ነኝ ብሎ ማሰብም ከንቱ ነው ። ማንን ነው የምንቀየመው ? ብለን ስንጠይቅ ገዳይም ሟችም ሁሉም ኢትዮጵያዊ ነው ።
“የገደለው ባልሽ የሞተው ወንድምሽ ፣
ኀዘንሽ ቅጥ አጣ ከቤትሽ አልወጣ ፤”
ሌላም ግጥም ትዝ ይለናል፡-
“አንጀቴ ተቆርጦ ከሆዴ ከወጣ ፣
እንግዲህ ሐኪሙ ምን ሊቀጥል መጣ ?”
አዎ ሁለት ነገሮች ያስፈልጋሉ ። የእኛ አባት መገለጥ ቀላል አይደለም ። ፍርድና ትምህርት ያስፈልጋሉ ። ከተመከርንበት የሕንዱ የነጻነት ታጋይ የነበሩት ማኅተማ ጋንዲ እንዲህ ብለው ነበር፡- “በምድር ላይ ብቻህን ብትቀር እንኳ ከግፈኞች ጋር አትተባበር ።”
እግዚአብሔር የመጽናናትን መንፈስ ይላክልን ። ላዘኑት የሚያረጋጋ መልአክ ይላክልን ። ልብ ይስጠን ።
“ጎዳናው ሳይጠበን አመል እያጋፋን ፣
አካሄዱ ቀርቶ አቋቋሙ ጠፋን ፤”
(ሰባኪውና ጸሐፊው)
ሕዳር ፫፣፳፲፩፫


Monday, November 9, 2020


እመቤታችንን በተመለከተ ለዘመናት በመናፍቃን ለሚነሱ ጥያቄዎች የማያዳግም መልስ 

ለዘመናት የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ዘለዓለማዊ ድንግልና ለመቃወም ዲያቢሎስ ያዘመታቸው
መናፍቃን ለሚያነሷቸው ጥያቄዎች ሁሉ የማያዳግም መልስ በዝርዝር እና በአንድምታ ቀርቧል ፡፡ ከጌታ ውጭ
ከቅዱስ ዮሴፍ ልጅ ወልዳለች ብለው ለተሰናከሉ ሁሉ በዚሁ አጋጣሚ ስለ ዮሴፍ ማንነት ጭምር ትምህርቱ
በጥቂቱ ይዳስሳል መልካም ንባብ፡-‹‹‹ አረጋዊው ዮሴፍ ማነው ? መናፍቃን ድንግል ማርያም ከጌታ ውጭ ከዮሴፍ
እንደወለደች ሲናገሩ እንሰማለን ማስረጃ ባይኖረውም። ነገር ግን የዮሴፍን ማንነት በጥቂቱም ቢሆን መረዳት
ለስህተታቸው ማሰታገሻ መድኃኒት ነውና እነሆ፡- አረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ሀገሩ ናዝሬት ሲሆን ሐናፂም ነጋዴም ነበር።
ዘሩ ከዳዊት ወገን ነው። ሦሰት ሴቶች እና አምሥት ወንዶች ልጆች ነበሩ። ልጆቹ ገሚሶቹ ከ12ቱ
ሐዋርያት ገሚሶቹ ደግሞ ከ72ቱ አርድዕት ውስጥ የነበሩ ሲሆን ከሚስቱ ጋር 52 ዓመት፤ሚስቱ ከሞተች በኋላ
ደግሞ 40 ዓመት ኖሯል። በድምሩ 92 ዓመት ከኖረ በኋላ ለእመቤታች ጠባቂ ሆኖ ተመረጠ። 
ከእመቤታችን እና ከጌታ ጋር ደግሞ በስደት ፣ በመከራ 22 ዓመታትን አሳልፏል። ሊጠብቃትም 
ሲመረጥ ከ1,985 ሽማግሌዎች ውስጥ ዕጣ ደርሶት ነው።
በፈቃደ እግዚአብሔርም የከተሰበሰቡት ሁሉ የርሱ በትር ለሦስት ጊዜ ያህል በተደጋጋሚ አብባና ለምልማ ተገኘ።
አረጋዊ ዮሴፍ በ114 ዓመቱ ሐምሌ 26 ቀን አርፏል። ከማረፉ በፊት ግን ጌታችንን ‹‹ ሥጋዬን በዚህ ምድር
አታስቀረው ›› ብሎ ለምኖት ነበርና ዛሬም ድረስ ዮሴፍ መቀበሩን እንጂ ቅዱስ ሥጋው የት እንዳለ የሚያውቅ
የለም ጌታ ስለ ጸሎቱ (ስለልመናው) ሰውሮታልና። ‹‹‹ አረጋዊው ዮሴፍ ለምን ተመረጠ? 
*ይህ ጻድቅና ንጹሕ አረጋዊ ዮሴፍ ድንግል ማርያምን ሊጠብቅ ስለተመረጠበት ምክንያን አስረጋጭ ማስረጃዎች
እነሆ።
1ኛ) አገልጋይዋ ተላላኪዋ ሆኖ ሊጠብቃት።
2ኛ) መከራዋን እንዲጋራ። አንድም ዮሴፍ ዘመዷ ነው
መከራን ለብቻ አይዘልቁምና በልጇ አማካኝነት የሚደርስባትን ስደት እና መከራ አብሯት እንዲካለፈል
ነው። ዝምድናቸው ሲዘረዘር የሚከተለውን ሃቅ ያስረዳናል፡- ግንዱ ‹‹ አልዓዛር ›› በሁለት ወገን የሚከተሉትን
ወልዷል ፡- 1)* ማታን = * ቅስራ* 2) * ያዕቆብ = * ኢያቄም * 3)* ዮሴፍ = * ድንግል ማርያም
(የነዚህ የዘር ሐረጋት ግንዱ ከላይ እንዳየነው * አልዓዛር* ነው ስለዚህ የዘር ሐረጋቸው አንድ ነውና ሊጠብቃት
እንጂ ሊያገባት አይችልም)

3ኛ) ከመደብደብ ሊያድናት። በኦሪ.ዘኁ 5፥19 በተጠቀሰው መሠረት አንዲት ሴት ከባልዋ ውጭ ጸንሳ
ብትገኝ ማየ ዘለፋ ያጠጥዋት ነበር። እንዲሁም አንዲት ሴት ባል ሳታገባ ብትጸንስ በሙሴ ሕግ መሠረት
ደብድበው ይገድሉአት ነበር። ስለዚህ እመቤታችን ለዮሴፍ ሳትታጭ ቀርታ ቢሆን ለድብደባ ባበቁአት ነበር።
4ኛ) ትንቢቱ እንዲፈጸም ነው። ጌታ ከዳዊት ቤት እና ወገን እንዲወለድ ኢሳ 11፥1 ፣ 10 ላይ ትንቢት ነበር።
ዮሴፍም የዳዊት ዘር ነውና ክርስቶስ በዮሴፍ የዳዊት ልጅ ተብሎ እንዲቆጠር ነው። ምነው በእናቱ የዳዊት ልጅ
አይባልምን? ቢባል አይሁድ ሴትን ከትውልድ ቁጥር አግብተው አይቆጥሩምና ነው።

5ኛ) ኃይለ አርያማዊት (ከሰማይ ወረደች እንጂ ምድራዊት አይደለችም) የሚሉ ወገኖች ነበሩና
ምድራዊት መሆኑኗን ለማጠየቅ ነው። ሆኖም ከምድር መገኘቷን ለመግለጽ እንጂ ድንግል ማርያም በክብሯ ሰማያዊት
ናት። የባሕርያችን መመኪያ መባሏም ከሰው ዘር መገኘቷን ልብ እንዲሉ ነው። ስለዚህ ድንግል ማርያም ለዮሴፍ
መታጨቷ ስለዚህ እና ይህን ለመሰለ ምክንያት ነው እንጂ ለሚስትነት አልነበረም። አንድም ዮሴፍ እመቤታችን
ሊጠብቃት በተመረጠ ጊዜ ጀርባው ጎብጦ ፣ ጉልበቱ ዝሎ ፣ ዓይኑ ሞጭሙጮ ነበር 92 ዓመት አልፎት ነበር አረጋዊ
(ሽማግሌ) መባሉም ለዚህ ነው። በመሆኑም አረጋዊ ዮሴፍ ስለነዚህ ምክንያት ድንግል ማርያም ሊጠብቃት
ተመረጠ እንጂ ሊያገባት አይደለም። ሊያገባት የተመረጠ ቢሆን ኖሮ ድንግል ማርያምን መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል
ሊያበሥራት ሲመጣ ‹‹ ወንድ ስለማላውቅ እንዴት ይሆናል›› ባላለችውም ነበር ። ሊያበሥራት የተላከው
ለዮሴፍ ከታጨች በኋላ ነውና። በዚህም ንግግሯ ለዮሴፍ የታጨችው ሊጠብቃት እንጂ ሊያገባት እንዳልሆነ አረጋግጣለች።
ዛሬ የተነሱ መናፍቀን ምሥጢር ይጎድላቸዋልና ዮሴፍን እንደወጣት ሰው ቆጥረው ድንግል ማርያምን ሊያገባ
እንደታጨ በደካማ ጎናቸው ያስባሉ እውነቱ ግን ይሄ ነው።

 1) የእጮኛ ትርጉም 

እጮኛ የሚለው ቃል ጠባቂ ማለት ነው ሌላ ከሰው ልብ የፈለቀ ትርጉም ሊሰጠው አይችልም። ለምሳሌ ‹‹እናንተን
ለዘለዓለም ለእኔ እንድትሆኑ አጭቻችኋለሁ ›› ሆሴ 2፥21 ማለት ለጋብቻ ነውን? ያሳዝና አጣመው ለተረጎሙት።
አሁንም ሐዋርያው ከጌታችን ጋር ስላዋሐዳቸው ‹‹ ለእርሱ አጭቻችኋለሁ ›› 2ኛ ቆሮ 11፥3 ማለቱን አስተውል።
እንደገናም ምእመናንን የከበረች ማደርያው ስላደረጋቸው ‹‹ ለሰማያዊው ክብር አጭቻችኋለሁ ›› ኤፌ 5፥26 ታዲያ
እንዲህ ሲል ላጋባችሁ ነው ማለት ይሆን(ሎቱ ስብሐት)። እመቤታችን ንግሥተ ሰማይ ወምድር ነችና በ15 ዓመቷ
መለኮት ተዋሐዳት። ሲዋሐዳትም ለዮሴፍ ታጨች ሉቃ 1፥26። እንግዲህ እጮኛ ማለት ትርጉሙን ያላወቁ ይወቁ
እንላለን። ነገር ግን ሰው በራሱ ፍቃድ አይተርጉም ! ሌላው እጅግ የሚደንቀው ነገር ደግሞ ድንግል ማርያም
ክርስቶስን ከመውለዷ በፊት እንጂ ከወለደች በኋላ ዮሴፍ ‹‹ እጮኛ ›› ተብሎ በአንድም ስፍራ አለመጠቀሱ ነው
ማስረጃ ‹‹ ሕጻንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብጽ ሽሽ ›› ማቴ 2፥3 እንዲሁም በግብጽ 3 ዓመት ከ3ወር በስደት ከቆዩ
በኋላ ይህንኑ ቃል ለዮሴፍ በህልም ተነግሮት ‹‹ ሕጻኑን የሚፈልጉት ሞተዋልና ሕጻንና እናቱን ይዘህ ወደ ናዝሬት
ተመለስ ›› አለው እንጂ እጮኛህን(ሚስትህን) ይዘህ ተመለስ አላለውም (ማቴ 2፥20)።



2) የበኩር ትርጉም 
የበኩር ልጇን ወለደች የሚለው ቃል ብዙዎችን አሳስቷል። ይህም ሊሆን የቻለው በተለምዶ የበኩር ልጅ የሚባሉ
የግድ ተከታይ ያላቸው መሆን አለባቸው የሚል አስተሳሰብ በመናፍቃን ክፉ ልቦና ስለሰረጸነው። ነገር ግን በተለምዶ
የሚባል ነገር መጽሐፍ ቅዱስ ጋር አይሰራምና እንዲህ ይታረማል ፡- ‹‹ እግዚአብሔር ሙሴን ከእስራኤል ልጆች
ዘንድ ከሰውም ከእንስሳትም ማኅጸንን የሚከፍት በኩር ሁሉ ለእኔ ቀድስልኝ አለው ›› ዘጸ 13፥1-2
ይህ ቃል እንደሚገልጸው በኩር የሚባሉት ለመጀመርያ ጊዜ ከእናታቸው ማኅጸን የሚወጡ መሆናቸውን እንጂ
ግዴታ ተከታይ ሊኖራቸው እንደማይገባ ያረጋግጣ። አንድም ብቻ ቢሆን የእናቱም ማኅጸን ለመጀመርያ ጊዜ ከፍቶ
ከወጣ ተከታይም ባይኖረው በኩር ነው። ይሄ የበኩር ትርጉም ካልገባን ወደ ሌላ ፤ ይልቁን ወደ ማንወጣው
አዘቅት መዘፈቃችን አይቀሬ ነው። ለምሳሌ ቆላስየስ 1፥7 ላይ ስለ ክርስቶስ ሲናገር ‹‹ ከፍጥረት ሁሉ በፊት በኩር ነው ›› 
ይላል እዚህ ጋር በኩር የሚለው ቃል ተወዳዳሪ ላላቸው ነገሮች የሚጠቀስ ሆኖ ከቀረበ ጌታን ፍጡር አድርጎ ከፍጡራን ጋር አነጻጽሮ
እርሱ ከፍጥረታት በፊት ቀደም ብሎ የተፈጠረ ፍጡር ነው እንደማለት ይሆናልና(ሎቱ ስብሐት)። እንደገናም በኩር
የሚለውን ቃል በሥጋዊ ደማዊ ሃሳብ ከተረጎምነው ዕብ1፥6 ላይ ‹‹ በኩርን ወደ ዓለም ሲያገባ ›› የሚል ቃል
አለ እዚህ ላይ የክርስቶስ በኩር ተብሎ መጠራት አብ ቀዳሚ ተከታይ የሌለውን የባሕርይ ልጁን ወደ መሬት ሂድ፣ ውረድ
 ተወለድ ፣ ሙት ተሰቀል ብሎ እንደላከው ለመግለጽ ነው ። ታድያ አብ በኩርን ወደ ዓለም ሲልክ በኩር የሚለው ቃል
ተጠቅሷልና አብም ከክርስቶስ ሌላ ልጅ አለው ማለት ነውን? እናንት ግብዞች መናፍቃን የመጽሐፍን ቃል
በግርድፍ መረዳት ምን ያህል እንደሚያስት ተረዳችሁ? ድንግል ማርያምን የነካችሁ እየመሰላችሁ ባለቤቱን
ነቀፋችሁ ያሳፍራል !!! እርሷስ ክብር ይግባትና በእናንተ አፍ አትረክስም እርሱ ባለቤቱ አንዴ አክብሯታልና።
ለምትሰሙኝ ግን እላችኋለሁ ‹‹ የበኩር ልጇን ወለደች ›› መባሉ መጀመርያና መጨረሻ የሌለውን አምላከ አዶናይ ፣
ልዑለ ባሕርይን ወለደች ማለቱ ነው። 

3) የ-እስከ-ትርጉም

ሥጋውያኑ(መናፍቃን) ‹‹ እስከን ›› ተገን አድርገው ‹‹እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም ›› የሚለውን ቃል ፍጻሜ
ላለው ነገር በማስገባት ደግመው ደጋግመው ተሰናክለውበታል። ትርጉሙ(ፍቺው) ግን ይህ አይደለም
ለምሳሌ፡- 1ኛ) የሣኦል ልጅ ሜልኮል ‹‹ እስከሞተችበት ›› ቀን ድረስ ልጅ አልወለደችም (2ኛ ሳሙ6፥23)። ይህም ማለት
እስከመጨረሻው ልጅ አልወለደችም ማለት እንጂ ከሞተች በኋላ ወለደች ለማለት አለመሆኑ የታወቀ ነው።
2ኛ) ይህም ነገር በሠራዊት ጌታ በእግዚአብሔር ጆሮ ተሰማ ‹‹ እስከሞቱ ›› ድረስ ይህ በደል በእውነት
አየሰረይላቸውም ኢሳ 22፥14 ታዲያ የዚህ ትርጉም ከሞቱ በኋላ ይሰረይላቸዋል ማለት ነውን? እስከዘለዓለም
አይሰረይላቸውም ለማለት እንጂ። 3ኛ) ከአዳም ጀምሮ ‹‹ እስከሙሴ ›› ድረስ ሞት ነገሠ (ሮሜ 5፥14)   
ታድያ ከሙሴ በኋላ ሞት ቀረ ማለት ነውን? 4ኛ) እግዚአብሐየር ጌታዬን ጠላቶችህ ለእግህ መረገጫ
‹‹ እስካደርግልህ ›› ድረስ በቀኜ ተቀመጥ አለው መዝ101፥1 ታዲያ ጌታችን ጠላቶቹን(አይሁደን) በሥልጣኑ
ከረታ በኋላ በአብ ቀኝ መቀመጡ ቀረ ማለት ነው? 5ኛ) እነሆም እኔ ‹‹ እስከ ዓለም ፍጻሜ ›› ድረስ ከእናተ
ጋር ነኝ ማቴ28፥20 ከዓለም ፍጻሜ በኋላ ከእናንተ ጋር አይደለሀም ማለት ነውን ? 6ኛ) ቁራውንም ሰደደው እርሱም 
ወጣ ውሃውም ከምድር  ‹‹ እስከሚደርቅ ›› ድረስ ወዲያና ወዲህ ይል ነበር ዘፍ 8፥7 ሲል ውሃው ከደረቀ በኋላ ወዲያና ወዲህ ማለቱን
ተወ ማለት ነውን? እንግዲህ ከላይ በተዘረዘረው የእስከ ትርጉም መሠረት በማቴ1፥25 የተጠቀሰው ፍጻሜ
የሌለው ‹‹ እስከ ›› መሆኑን ያስረዳል ስለዚህ ዮሴፍ እመቤታችንን እስከ ፍጻሜው ድረስ በግብር አላወቃትም
ነበር ማለትነው፡፡ ከዚህ ውጭ በራሱ ፍቃድ የሚረተጉም ሁሉ የረተገመ ይሁን::

4) የወንድሞች ትርጉም 

አዲስ ኪዳን በተለያዩ ቦታዎች ላይ ጌታችንን ‹‹ወንድሞቹ›› እንደሆኑ ከሐዋርያት ወገን የሚጠቅሳቸው
አሉ። ይህን በመያዝ ብዙ ጥራዝ ነጠቅ አንባቢያን (መናፍቃን) ጌታ ወንድሞች እንዳሉት እና ድንግል
ማርያም ከጌታ ውጭ ልጅ እንዳላት በማውራት አነስተኛ የመጽሐፍ ቅዱስ ዕውቀታቸውን ለማንጸባረቅ ይሞክራሉ ፡፡
 ነገር ግን ማንም የራሱን ግላዊ ሃሳብ ከማንጸባረቁ በፊት የመጽሐፍ ቅዱስን የአጻጻፍ ዘይቤ መረዳት ያስፈልገዋል እንላለን።
መጽሐፍ ቅዱስ 1ኛ) በምን ቋንቋ እንደተጻፈ ፣ 2ኛ) በማን ባሕልና ዘይቤ እንደተጻፈ ፣ 3ኛ) በየትኛው ዘመን እንደተጻፈ 
አስቀድሞ ማወቅ ለማነበብና ለመረዳት ያስችላል ምክንያቱም ሃይማኖት መሠረታዊ ጉዳይ ነውና !!! መጽሐፍ ቅዱስን የጻፉት
ከ40 በላይ ቅዱሳን ሲሆኑ ከእነዚህም ውስጥ አብዛኛዎቹ ዕብራውያን ናቸው ፡፡ ስለዚህም መጽሐፍ ቅዱስን አንብቦ
ለመረዳት የዕብራውያንን ባሕል በከፊልም ቢሆን መረዳት ያስፈልጋል። ስለዚህም በዕብራውያን ባሕል ፡- 1ኛ) አብሮ
 አደግና ዘመዶችን በሥጋ እንኳ ከአንድ እናትና አባት ባይወለዱም ‹‹ ወንድም ›› ይባላሉ (ዘፍ 13፥11) 2ኛ) በሃይማኖት 
የሚመሳሰሉም ‹‹ ወንድሞች ›› ይባላሉ (ገላ4፥1) ‹‹ ወንድሞቼ ይህን ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ ›› 3ኛ) በሕብረት በአንድ 
(ማህበር) የሚቀመጡ ‹‹ወንድሞች ›› ይባላሉ ‹‹ ወንድሞች በሕብረት ቢቀመጡ እነሆ መልካም ነው እነሆም ያማረ ነው›› መዝ 133፥1።
በተጨማሪም ሐዋርያት እርስ በርስ ‹‹ ወንድሞች›› ይባባሉ ነበር። ከዚህ በመነሳት ለጌታ ‹‹ ወንድሞቹ ››
ተደርገው የተጠቀሱት ሦስቱ ሐዋርያት በሥጋ የተወለዱ አይደሉም። ድንግል ማርያምም ከጌታ ውጭ ምንም
ዓይነት ልጅ የላትም !!! ልጅ ብቻም ሳይሆን ልጅ የመውለድ ሃሳብም የላትም አልነበራትምም !!! በተጨማሪም 
ወንድሞቹ ተብለው የተጠቀሱት ‹‹ ያዕቆብ›› እና ‹‹ ይሁዳ ›› መልዕክቶቻቸውን ሲጽፉ ‹‹የጌታ ባሪያ›› እያሉ 
ጻፉ እንጂ ‹‹ የጌታ ወንድሞች ›› ነን ብለው አልጻፉም ማስረጃ ፡- የያዕቆብ መልእክት 1፥1 ‹‹ የጌታ የኢየሱስ 
ክርስቶስ ባሪያ ያዕቆብ ›› የይሁዳመልእክት 1፥1 ‹‹ የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ የያዕቆብም ወንድም የሆነ ይሁዳ ›› ስለዚህ እነዚህ
ሐዋርያት ዮሴፍ ከሟች ሚስቶቹ የወለዳቸውና አብረውት ያደጉ እንጂ ከድንግል ማርያም የተወለዱ አይደሉም።
‹‹‹እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም የሚለው ትርጉም ››› ይህን ቃል በመጥቀስ ድንግል ማርያም ክርስቶስን
ከወለደች በኋላ ዮሴፍ በግብር አውቋታል የሚሉ መናፍቃን አሉ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ከወለደች በኋላ ልጅ
ወልዳለች የሚል ቃል አልተጻፈም እንጂ !!! ይህን ቃል መነሻ አድርጎ ለመጀመርያ ጌዜ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን
የጠየቀው በ3ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረው ንጉሥ አርቃድዮስ ሲሆን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አምሥት
ነገሮችን ግልጽ አድርጎለታል። አርቃድዮስም መልሱን በሚገባ አምኗል ተረድቷል። ዛሬም ጥያቄውን በድርቅና ሳይሆን
 ልክ እንደ አርቃድዮስ በየዋህነት ለጠየቀ ሁሉ መልስ የማያስፈልገው ጥያቄ ነው። ሆኖም ለዚህ ስህተታቸው መልስ 
መስጠቱ ተገቢ ነውና አነሆ ፡- ‹‹የበኩር ልጇን እስክትወልድ ድረስ ዮሴፍ ድንግል ማርያምን አላወቃትም›› ማለት፡- ዮሴፍ ድንግል
ማርያም ጌታን እስከምትወልድበት ቀን ድረስ ማን እንደሆነች አላወቃትም(ማንነቷን) አልተረዳም ነበርለማለት ነው።
ኋላ ግን ጌታን በወለደች ጊዜ በቤተልሔም እረኞች (ኖሎት) እና መላእክት በአንድነት ሲዘምሩ ፣ የሩቅ ምሥራቅ ነገሥታት(ሰብዓ ሰገል) 
እጅ መንሻ ይዘው መጥተው ሲሰግዱለት ፣ እንዲሁም ቤተልሔም ላይ የብርሃን ድንኳን ከምድር እስከ ሰማይ
ተተክሎ ሲመለከት ድንግል ማርያም የአምላክ እናት መሆኗን አወቀ(ተረዳ) እስከዚያች ቀን ድረስ ግን ማለትም
ጌታን እስከምትወልድበት ቀን ድረስ ዮሴፍ ድንግል ማርያም የአምላክ እናት መሆኗን አላወቀም ፣ አልተረዳም
ነበር ለማለት ነው። አወቀ ማለት በግብር ተገናኘ ማለት አይደለም!!! እንዲህ ከታሰበ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንዲህ የሚል ቃል አለ፡-
‹‹ ከእነርሱም ጋር በማዕድ ተቀምጦ ሳለ እንጀራውን አንሥቶ ባረከው፥ ቈርሶም ሰጣቸው፤ ዓይናቸውም
ተከፈተ፥አወቁትም›› (ሉቃ 24፥30-31) ይህም ማለት ጌታችን መሆኑን አወቁ (ተረዱ) ከማለት
ውጪ ሌላ ምን ዓይነት ትርጉም ሊኖረው ይችላል ? (ማዕዱን ቆርሶ እስከሚሰጣቸው ድረስ ግን ጌታን
አላወቁትም ነበር)ስለዚህ ማወቅ ማለት መረዳት እንጂ የግድ በግብር መገናኘት ዓይደለም !!! ለምሳሌ ‹‹ ቃየል
ሚስቱን አወቀ ጸነሰችም ›› ዘፍጥረት 4፥17 የሚለው ቃል በግብር እንደቀረባት(እንደተገናኛት) የታወቀ ነው
ምክንያቱም አወቃት ብቻ ብሎ አላቆመም ‹‹ ጸነሰችም ›› ይላልና :: ነገር ግን ዮሴፍ ድንግል ማርያምን እስክትወልድ ደረስ
አላወቃትም ካለ በኋላ ሌላ ምንም ዓይነት ተቀጽላ ቃል የለውም። መናፍቃን በግድ እናጋባ እናዋልድ ካላላችሁ
በቀር ጸነሰችም ወለደችም አላለም አዚያው ላያ ያበቃል አራት ነጥብ። ‹ድንግል ማርያም ከክርስቶስ ውጪ ልጅ የላትም!›
ተጨማሪ ማስረጃዎች እነሆ ፡- ሲጀመር መጽሐፍ ቅደስ በአንድም ቦታ ድንግል ማርያም ከክርስቶስ ውጪ ልጅ
አላት አይልም ብሎም አያውቅም ! መጽሐፍ ቅዱስ እውነቱን እውነት ሐሰቱንም ሐሰት የሚል መጽሐፍ ስለሆነ
ያልሆነውን ሆነ አይልም የሆነውንም አይደብቅም! ወንጌልን ለዓለም የሰበኩ ቅዱሳን ሐዋርያትም ድንግል
ማርያምን ማዕከል አድርገው አስተምረዋልና ከክርስቶስ በኋላ ልጅ ወልዳ ቢሆን ኖሮ ለምን ደበቁን ? ለምሳሌ
ጌታችን ሲሰቀል በመስቀል ሥር ሆና ስማልቀሷ ፣ ለዮሐንስ ስለመሰጠቷና መንፈስ ቅዱስ በወረደ ጊዜ እርሷ
በመሃከላቸው እንደነበረች ሲጽፉ ለምን ከጌታ ሌላ ልጅ መውለዷን አልነገሩንም? ለምንስ ደበቁን? አሁንም በዚህ
አቋም ለጸናችሁ መናፍቃን አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁ እውን መለኮት ባደረበት ማኅጸን ሰው ያድርበት ይሆን?
አዎ የምትል ከሆነ ያንተ ኢየሱስ ፍጡር እና ተራ ሰው እንጂ አምላክ አይደለም !!! የኛ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ
ባደረበት ማኅጸን ግን ማንም….. ማንም…. ማንም….  አያድርበትም። በድጋሚ ልምጣባችሁ እውን ድንግል 
ማርያም ከክርስቶስ ውጪ ሌላ ልጅ ያስፈልጋት ይሆን ከዚያ በኋላ ብትወልድም ሰው አምላክ አይሆን? አበው እንኳ ‹‹ሃምሳ
ቢወለድ …… ከተባረከ ይበቃል አንዱ›› ብለው የለ ታዲያ ድንግል ማርያም ከአንዱ ከብሩክ ልጇ ከክርስቶስ ሌላ
ምን ሽታ ትወልድ ይሆን ? መጽሐፍ ቅዱስ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋን እንዴት እንዳስቀመጠ ተመልከት ፡-
 1) “እቴ ሙሽራዬ የተቆለፈች ገነት የተዘጋ ምንጭ የታተመች ፈሳሽ ናት” መኃ.ዘሰ 4÷12 (ዳዊት የመንፈስ
አባቷ ነውና ልጄ ይላት ነበር ሰሎሞን ደግሞ የዳዊት ልጅ ነውና እህቴ ያላታል የመንፈስ ወንድሟ ነውና)
2) “የምስራቁም በር ለዘለዓለም ተዘግቶ ይኖራል ሰውም አይገባበትም እግዚአብሔር አንዴ ገብቶበታልና” .ሕዝ
44÷1-2 (ምሥራቅ የተሰኘች ድንግል ማርያም ናት በእርሷ ሰማይነት ክርስቶስ ፀሐይ ሆኖ ወጥቷልና) ይህን ቃል
ለቤተ መቅደስ ነው ብለህ የምትከራከር ካለህ ‹‹ለዘለዓለም የተዘጋ ቤ/መ በዚህ ምድር ላይ የለምና
እራስህን አታታል! 3) “ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆንልኛል” ሉቃ 1÷34 (ይህ የእመቤታችን አስደናቂ ንግግር ለወደፊትም
እራሷን አቅባ እንደምትኖር የሚያረጋግጥ ቃል ነው። አንድም ኃላፊ ግስ ነው የወደፊት ዓላማዋንም
ያረጋግጣል) ‹ እርሱ ብቻ ልጇ እንደሆነ የክርስቶስ ምስክርነት › 1ኛ) አይሁድ በምቀኝነት ክርስቶስን ሲሰቅሉት ከእግረ
መስቀሉ ሥር የተገኘው ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስና ድንግል ማርያም ብቻ ነበሩ። እመቤታችን ሌሎች ልጆች
ቢኖሯት ኖሮ ‹‹ እነሆ ልጅሽ ›› ብሎ ዮሐንስን ጠብቃት ባላለውም ነበር። በዚህ ላይ ዮሐንስም እኮ እናት
ነበረችው። ነገር ግን ድንግል ማርያም አንድያ ልጇ በመሆኑ ጌታችን ለዮሐንስ አደራ ሰጥቶአታል።
2ኛ) የኢየሩሳሌም ሴቶች ጌታችን መስቀል ተሸክሞ ሲያልፍ ተመልክተው አዝነው ሲያለቅሱ ‹‹ ለራሳችሁ እና
ለልጆቻችሁ አልቅሱ ›› ተብለዋል እመቤታችንም መስቀል ሥር ሆና ታለቅስ ነበር ታዲያ ለምን ‹‹ ሄደሽ ለልጆችሽ
አልቅሺ አላላትም ? ‹ትልቅ እርምት የሚሻው የመናፍቃን ስህተት› ‹ ይህ የጸራቢ ልጅ አይደለምን? እናቱስ ማርያም ትባል
የለምን? ወንድሞቹስ ያዕቆብና ዮሳ ስምዖንም ይሁዳም አይደሉምን? እኅቶቹስ ሁሉ በእኛ ዘንድ ያሉ አይደሉምን?
እንኪያስ ይህን ሁሉ ከወዴት አገኘው? ተሰናከሉበትም››(ማቴ13÷56) የሚለውን ቃል ለማን እንደተነገረ እንኳ
ሳያስተውሉ ጭራሽ ድንግል ማርያም ከክርስቶስ ሌላ ልጅ እንዳላት አድርገው ይህን አሳፋሪ ቃል ሲጠቀሙበት አይቼ
እኔም አፈርኩበት !!! የዚህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል ዓላማ አይሁድ ክርስቶስን ወንድሞች አሉት ፤ዮሴፍ ከሟች
ሚስቱ የወለዳቸውን ሁሉ ከድንግል ማርያም ነው ብለው በማሰባቸው ወይም በመናገራቸው ተሰናከሉ(ተሳሳቱ)
ማለት ነው። ታዲያ እነርሱ ክርስቶስ የዮሴፍ ልጅ ነው ፤ድንግል ማርያምም ሌሎች ልጆች አሏት ብለው በማሰባቸው
ተሳሳቱ ከተባለ ለምን አንተ ደግመህ ትሰናከላለህ? ይህን ስህተታቸውን ሲያስረግጥ ትንሽ ወረድ ብሎ ‹በአለማመናቸውም
 ምክንያት በዚያ ብዙ ተአምራት አላደረገም › ይላል ። ‹ስለ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋ ማጠቃለያ› እመቤታችን እንደማንኛውም
 ሴት አይደለችም! ክርስቶስን የጸነሰችው ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ ሲያበሥራት ነው ፡፡ ‹ወንድ ስለማላውቅ ይህ 
እንዴት ይሆንልኛል › በማለት እንደተናገረችው እንደሌሎች ሴቶች በዘር በሩካቤ አይደለምና ነው። ቅድስት
ኤልሳቤጥም ‹‹አንቺ ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ ›› (ሉቃ 13÷9) በማለት እንደተናገረችው። ቅዱስ ዳዊትም
‹‹ነኪር ነገሩ በእንቲአኪ ኦ ሀገረ እግዚአብሔር›› (የእግዚአብሔር ከተማ ሆይ ባንቺ የተደረገው ምንኛ ድንቅ ነው)
 አንዳለ በእመቤታችን የተደረገው ልዩ ነው። ለዚህ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋ አንክሮ(ምሥጋና) ይገባል::
አሜን

ወስብሀት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር አሜን-ይቆየን