Saturday, January 2, 2021

የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በቤተ ክርስቲያን አንደበት

 




ታኅሣሥ ፳፰ እና ፳፱ ልደቱ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ

‹‹ሰው ሆይ! ፈጽመህ ደስ ይበልህ፣ እግዚአብሔር ዓለሙን ወዶታልና አንድ ልጁንም የሚያምንበት ሁሉ እስከ ዘለዓለም ፈጽሞ ይድን ዘንድ አሳልፎ ሰጥቷልና ልዑል ክንዱን ሰደደልን፡፡››
‹‹በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች ታላቅ ብርሃን ወጣላቸው፤ በቅዱሳን ላይ የሚያድር እግዚአብሔር እኛን ለማዳን ልዩ ከሆነች ድንግል ሰው ሆኗልና ኑ ይህን ድንቅ እዩ፤ ስለተገለጠልን ምሥጢር ምስጋና አቅርቡ፤ ሰው የማይሆን ሰው ሆኗልና ቃል ተዋሕዷልና ጥንት የሌለው ሥጋ ጥንታዊ ቀዳማዊሆነ፣ ዘመን የማይቆጠርለት መለኮት ዘመን ተቆጠረለት፡፡ የማይታወቅ ተገለጠ፣ የማይታይ ታየ፣ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ በእርግጥ ሰው ሆነ፡፡››
‹‹ከቅድስት ሥለሴ አንዱ ወልድ መዋረዳችንን አይቶ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ባሕርዩን ዝቅ አደረገና መጥቶ በድንግል ማኅፀን አደረ፤ ከብቻዋ ከኃጢአት በቀርም እንደ እኛ ሰው ሆነ፡፡ ነቢያት ትንቢት እንደተናገሩለት በቤተልሔም ተወለደ፤ ፈጽሞ አዳነን፣ ወገኖቹም አደረገን፡፡›› ቅዱስ ኤፍሬም
ሶሪያዊ በጌታችን ድንቅ ልደት የተደረገልንን ድንቅ የማዳን ሥራ በተናገረበት ድርሳኑ ላይ ነው እንዲህ ብሎ የጻፈው፡፡
ሰው ሆይ! ፈጽመህ ደስ ይበልህ!!! ፍጹም መዳን ይሆንላችሁ ዘንድ በስሙ አምናችሁ ለአምላክነቱ የምትገዙለት የክርስቶስ ወገኖች በእናቱም በወላዲተ አምላክ በድንግል ማርያም ፍጹም አማላጅነት የምትታምኑ የተዋሕዶ ልጆች ሁላችሁ እንኳን ደስ አላችሁ፣ እንኳን ደስ አለን፡፡ እንኳን አደረሳችሁ፣ እንኳን አደረሰን፡፡ እነሆ የጌታችንን የልደቱን ጥንተ ነገር አምጥተን መጻሕፍትን ጠቅሰን መምህራንን ዋቢ አድርገን እንነግራችሁ ዘንድ እንወዳለን፡፡
አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን አምላክን ከመውለዷ ከ1520 ዓመት በፊት የፈላስፋዎችን የፍልስፍና መጽሐፈ ሕግ መርምሮ የሚያውቅ በለዓም የሚባል አንድ ታላቅ ፈላስፋ ነበረ፤ እርሱም የፈላስፎች ሁሉ አለቃ ነው፡፡
ከዕለታትም በአንደኛው ቀን ከአዳም እስከ ሙሴ ዘመን ያሉትን የሰዎች ትውልድ ቁጥር የያዙ የፍልስፍና መጻሕፍትን ሁሉ ሰበሰበ፡፡ ዳግመኛም እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ በየጊዜው የሚነሡትን የሰዎች ቁጥርና ትንቢት የያዘ መጽሐፍ አቅርቦ መረመረ፡፡ እነዚህንም መጻሕፍት ገልጦ ሲመረምር በውስጣቸው አምላክን የወለደች ክብርት እመቤታችንን አገኛት፡፡ ባገኛትም ጊዜ እርሷ ድንግል ስትሆን ልጇን ክርስቶስን ታቅፋ አያት፤ በአጠገቧም ታላቅና ብሩህ ኮከብ ነበረ፡፡ በዚያን ጊዜም በለዓም ቀደ መዝሙሩን ዘረደሸትን እና ከእርሱ በታች ያሉትን ፈላስፎች ሁሉ ሰብስቦ በብራናው ላይ የተሣለውን የእመቤታችንንና የልጇን የመድኃኔዓለምን ሥዕል በአጠገባቸውም ያለውን ኮከብ አሳያቸው፡፡ ፈላፋው መሰግልም በእርሱ ዘንድ ለተሰበሰቡት ፈላስፎች ‹‹ይህ ኮከብ በእናንተ ዘመን ወይም በልጆቻችሁ ዘመን ምልክት ቢያሳይ ወይም ቢገለጥ የዚያን ጊዜ ድንግል ከነልጇ ወዳለችበት መርቶ ያደርሳችሁ ዘንድ እርሱን ተከተሉት›› አላቸው፡፡ ይህንንም ምልክት ከነገራቸው በኋላ ፈላፋው በለዓምና የእርሱ ተከታዮች ሁሉ ሞቱ፡፡ ነገር ግን በሕይወት ያሉትና ከእነርሱም በኋላ የተነሡት ሰዎች ያችን ሥዕል በቤተ መዛግብት ውስጥ አኖሯት፡፡ ያችም ሥዕል ለሚጎበኟት ሁሉ በኋለኛው ዘመን የሚደረገውን አባቶቻቸው የተናገሩትን ትንቢት ይነግሯቸው ነበር፡፡
ከአንድ ሺህ አምስት መቶ ዓመታት በኋላ ጌታችን በቤተልሔም ሊወለድ ሁለት ዓመት ሲቀረው ያ ኮከብ በሀገራቸው ላይ በግልጽ ታየ፡፡ በዚያ ጊዜም ያንን ሥዕል ከቤተ መዛግታቸው አወጡና በሥዕሉ አጠገብ ያለውን የኮከብ ሥዕል ቢመለከቱ በአየር ላይ ከተገለጸላቸው ኮከብ ጋር አንድ መልክ ወይም ትክክል መሆኑን አረጋገጡ፡፡ አባታቸው ዘደረሸት እንዳስረዳቸው የሀገሩ ፈላስፎችና መኳንንቶች ሁሉ ከሠራዊቶቻቸው ጋር እጅ መንሻውን ይዘው ሥዕሉን ተሸክመው ለመሄድ ተነሡ፡፡ ኮከቡም ከሰው ቁመት ርቀቱ 75 ሜትር በሆነ ከፍታ ላይ ሆኖ በፊት በፊታቸው ይመራቸው ነበር፡፡ ከእነርሱ ወገን ያልሆነ ልዩ ጠባይ ወይም ባሕል ወይም ቁም ነገረኛ ያልሆነ ሰው የተከተላቸው ወይም በመሀላቸው የተገኘ እንደሆነ ኮከቡ ይሰወራቸው ነበር፡፡ ነገር ግን እነርሱ ከእርሱ ወገን ያልሆነውን ተመራምረው ከመካከላቸው ባስወገዱት ጊዜ ኮከቡ እንደቀድሞው ተገልጾ ይመራቸው ነበር፡፡ በመሸም ጊዜ ወደ ማደሪያ ቦታ ያደርሳቸውና ሲነጋ ዳግመኛ ይመራቸዋል፡፡ ኮከቡም መልኩ በብዙ ዓይነት ልውጥ ነበር፡፡ ሕፃን የታቀፈች ድንግል ብላቴናን ይመስላል፡፡ በእንዲህ ዓይነት ጉዞ እየተጓዙ ጌታችን ከተወለደበት ቦታ ኢየሩሳሌም በሁለት ዓመት ደረሱ፡፡
ኢየሩሳሌም እንደደረሱ ያ እየመራ ያመጣቸው ኮከብ ተሠውራቸው፡፡ እነርሱም እጅግ አዝነው የሚያደርጉትን አላወቁም ወደ ከተማ ገብተው ስለተወለደው ንጉሥ ጠየቁ፡፡ የእነዚህም ሰዎች አጠቃላይ ቁጥራቸው ሠላሳ ሺህ ነው፣ ነገሥታቱም ሦስት ናቸው፡፡ ለእያንዳንዱ ንጉሥ 10 ሺህ ሠራዊት ነበረውና ሄሮድስ ይህን ያህል ሰው የተወለደውን የአይሁድን ንጉሥ ለማየት መምጣታቸው እጅግ አስደነገጠው፡፡ መላዋ ኢየሩሳሌምም ከሄሮድስ ጋር ታወከቸ፡፡ ሄሮድስም የካህናት አለቆችንና የሕዝቡን ጸሐፊዎች ጠርቶ ‹‹ክርስቶስ በየት ይወለዳል?›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹በነቢይ ‹የአፍራታ ዕፃ ቤተልሔም አንቺም ከይሁዳ ነገሥታት አታንሺም ወገኖቼ እስራኤልን የሚጠብቅ ንጉሥ ካንቺ ይወለዳልና› ተብሎ ተነግሯልና በቤተልሔም ይወለዳል›› አሉት፡፡ ከዚህም በኋላ ሄሮድስ ሰብዓ ሰገልን ጠርቶ ኮከቡ የታየበትን ዘመን ከእነርሱ ተረዳ፡፡ ‹‹ሄዳችሁ የሕፃኑን ነገር መርምራችሁ ያገኛችሁት እንደሆነ እኔም መጥቼ እሰግድለት ዘንድ በእኔ በኩል ተመልሳችሁ ኑ›› አላቸው፡፡ እነርሱም የነገራቸውን ሰምተው ከንጉሡ ዘንድ ሄዱ፡፡ እነሆ ያ በምሥራቅ ያዩትና ይመራቸው የነበረው ኮከብ ዳግመኛ ወደ ቤተልሔልም እስኪያደርሳቸው ድረስ ይመራቸው ነበር፡፡ ሕፃኑም ካለበት ዋሻ ላይ ደርሶ ቆመ፡፡ ኮከቡንም ባዩት ጊዜ እጅግ ደስ አላቸው፡፡ ሕፃኑንም ድንግል እናቱ በክንዷ እንደታቀፈችው እነርሱ ከያዙት ሥዕል ጋር አንድና ትክክል ሆኖ ሆኖ ባገኙት ጊዜ እጅግ አደነቁ፤ ፈጽመውም ተደሰቱና እጅ ነሱት፤ ወድቀውም ሰገዱለት፡፡ ሣጥናቸውንም ከፍተው ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤውን እጅ መንሻ አቀረቡለት፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ርጉም ሄሮድስ እንዳይመለሱ በሕልም ተረድተው በሌላ መንገድ ወደሀገራቸው ተመለሱ፡፡ አምላክ በሥጋ ስለመገለጡ ዓዋጅ ነጋሪዎችና ሰባኪዎች ሆኑ፡፡
ይህችም ዕለት ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ ብሎ ትንቢት የተናገረላት ናት፡- ‹‹እነሆ ድንግል ፀንሳ ወንድ ልጅ ትወልዳለች፣ ስሙንም ዐማኑኤል ትለዋለች፣ትርጓሜውም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ ማለት ነው፡፡
ስለዚህችም የበከረች ድንግል ነቢይ ሕዝቅኤል ‹‹እግዚአብሔርም አለኝ ‹ይህች በር ተዘግታ ትኖራለች፣ አትከፈትም፣ የሚገባበትም የለም የእስራኤል ፈጣሪ እግዚአብሔር እንደተዘጋች ይገባባታልና ተዘግታ ትኑር››› አለ፡፡
ነቢዩ ዳንኤልም ‹‹ሌሊት በራእይ አየሁ ‹እነሆ ታላቁ እንደ ሰው ልጅ በሰማይ ደመና መጣ፤ ዘመኑን ወደሚያስረጅ ደረሰ፣ ከፊቱም አቀረቡት፣ የዘላለምአገዛዝ፣ ጌትነት፣ መንግሥት ተሰጠው፡፡ ሕዝቡና አሕዛቡ ሁሉ መንደር መንድረው የሚኖሩትና ነገዱም ነገሥታቱም ሁሉ ይገዙለታል፤ አገዛዙም የዘላለም አገዛዝ ነው፤ መንግሥቱም የማያልፍ የማይጠፋ ነው››› አለ፡፡
ዳግመኛም ኢሳይያስ ‹‹እግዚአብሔር እንደ እኔ የሥጋ መጋረጃ በመጋረድ ተገለጠልኝ›› አለ፡፡ አሁንም ደግሞ ‹‹አዲስ ሰማይ አዲስ ምድር እሠራ ዘንድ አለኝ›› አለ፡፡ ሁለተኛም ‹‹በእሴይ ሥር በትር ትወጣለች፣ ከእርሷም ጽጌ አበባ ይወጣል›› አለ፡፡ ዳግመኛም ‹‹ሕፃን ተወልዶልናልና ወንድልጅም ተሰጥቶናልና ይኸውም ሥልጣን በጫንቃው የሆነ ክርስቶስ ነው፣ ስሙም ድንቅ መካር፣ ኃያል አምላክ፣ የዘላለም አባት፣ የሰላም አለቃ ይባላል›› አለ፡፡
ነቢዩ ኤርምያስም ስለ እግዚአብሔር ‹‹በዚያን ወራት ለዳዊት ብርሃንን አወጣለሁ፣ በምድርም የቀና ፍርድን ያደርጋል፣ እግዚአብሔርም ያመኑትን ያድናቸዋል›› አለ፡፡
ኤልሳም ‹‹እግዚአብሔር ከሰማይ ይወርዳል፣ በእስራኤል ልጆች አደባባይም በመመላለስ ለሕዝቡ ዕውነትን ያስተምራቸዋል፡፡ ከአብርሃም ልጅነት ልዩ ከሆኑወገኖች በቀር አሕዛብ ሁሉ ይታዘዙለታል›› አለ፡፡
ናሆምም ‹‹እግዚአብሔር በእኔ አርአያ ይመጣል፣ ልብሱም እንደልብሴ ነው›› አለ፡፡
ኢዩኤልም ‹‹የእግዚአብሔር ዙፋን የሆነች ብላቴና ድንግልን አየሁ፣ እርሷም እንደ እሳት ያልባት ነበር፡፡ ስለእርሷ ‹ይህች ማናት/› ብዬ ኪሩብን ጠየቅሁት፡፡ እርሱም ‹ከአዳም ልጆች የተመረጠች የእግዚአብሔር ዙፋን ይህች ድንግል ናት፣ በእርሷም የተጎሳቆሉ አሕዛብ ይድናሉ፤ ለአመነባትም ረድኤትና መጠጊያ ናት› ብሎ ነገረው፡፡››
ዳዊትም በመዝሙሩ ‹‹እግዚአብሔር አንተ ልጄ ነህ፣ ዛሬም በተዋሕዶ ወለድኩህ አለኝ፡፡ ለምነኝ አሕዛብን ርስት አድርጌ እሰጥሃለሁ፣ ግዛትህም በመላውዓለም ነው፡፡›› ዳግመኛም አብ አለ ‹‹ቀዳማዊ ወልድ በኃይል ቀን ካንተ ጋራ ሳለሁ ከአጥቢያ ኮከብ በፊት ከሆድ ወለድኩህ፣ እንደ መልከ ጸዴቅ ሥርዓት አንተ የዓለሙ አገልጋይ ካህን ነህ ብሎ እግዚአብሔር ማለ፣ ከማለም አይፀፀትም፡፡››
ቤዛ ይስሃቅ በግዕ ከኅቱም ዕፀ ሳቤቅ እንደተገኘ፣ ለእስራኤልም በበረሃ ውስጥ ከኅቱም ዓለት ውኃ እንደፈለቀ፣ የደረቀ የአሮን በትርም እንደለመለመችና እንዳፈራች፣ በሶምሶንም እጅ ውስጥ ከአህያ መንጋጋ አጥንት ውኃ እንደፈሰሰ እንዲሁ የጌታችን ልደት በኅቱም ድንግልና ሆነ፡፡ በዕፀ ጳጦስ ውስጥ እሳት እንደነደደች፣ ዕፂቱም እንዳልተቃጠለች እንዲሁ የመለኮቱ እሳት ድንግልን አላቃጠላትም፡፡ ምስጋና ለእግዚአብሔር ይሁን ለዘላለሙ አሜን፡፡
ዳግመኛም ዛሬ ልደታቸው ከጌታችን ጋር የተባበረላቸው ብዙ ቅዱሳን አሉ፡፡ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ፣ ቅዱስ ላሊበላ፣ ቅዱስ ነዓኩቶ ለአብ፣ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ፣ ቅዱሳን ነገሥታት አብርሐ ወአጽብሓ፣ አቡነ አካለ ክርስቶስ፣ አቡነ መዝራእተ ክርስቶስ፣ መስፍኑ ኢያሱ፣ የገርአልታው አቡነ ዳንኤል፣ ዳግማዊ ቂርቆስ ዘቡልጋ እነዚህ 11 ቅዱሳን ልደታቸው ከጌታችን ጋር የተባበረላቸው ናቸው፡፡ በረከታቸው ይደርብን፡፡
ሌሎችም ዕረፍታቸው ሆኖ በዓመታዊ በዓላቸው የሚታሰቡ ቅዱሳን አሉ ነገር ግን በዚህች የበዓላት ሁሉ ራስ በሆነች እጅግ በከበረቸ የጌታችን የልደት በዓል ዕለት ገድላቸውን ልናወሳ አልወደድንም፡፡ ከወርሃ ጥር ጋር አብረን እናየዋለን፡፡ በዚህች ዕለት ግን ከበዓለ ልደት ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ነጥቦች እናያለን፡፡
ነቢያት በትንቢታቸው ‹‹በሬ የገዢውን አህያም የጌታውን ጋጣ አወቀ›› (ኢሳ 1፡3)፣ ‹‹አቤቱ ድምፅህን ሰምቼ ፈራሁ ሥራህንም አይቼ አደነቅሁ፤ በሁለት እንስሳ መካከል አየሁህ›› (ዕን ፫፥፪) ብለው እንደተናገሩት ጌታችን በበረት ውስጥ አህያና ላም ትንፋሻቸውን ገብረውለታል፡፡ የሌሊቱን ቁር ለመግለጽ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም ዓለምን የሚገዛው በኪሩቤል ሠረገላ ላይ የሚቀመጠው የባሕርይ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ በከብቶች በረት የመወለዱን ነገር በማንሣት በአድናቆት ‹‹በበረት ውስጥ የዓለም ገዢ መተኛት እጅግ ድንቅ ነው፤ በበረት ከጽርሐ አርያም ይልቅ ረዘመ፤ ከምድር ዳርቻም ሰፋ፤ ሕዝቅኤል ካየው ሠረገላ ዳንኤልም ካየው ኪሩባዊ ዙፋን በረት በለጠ (ሕዝ 1፡18-23፣ ዳን 7፡9)፤ በረት ነባቢ ለሆነ መሥዋዕት መሻተቻ መንበርን ሆነ፤ ይኸውም የቅድስቲቱ እንቦሳ ልጅ ንጹሕ በግ ነው፤ ሰማይና ምድና የማይወስኑትን በረት ቻለው፤ ወሰነውም›› አለ፡፡
በሌሊት መንጋቸውን የሚጠብቁ እረኞች ነበሩ፡፡ መልአኩ መጥቶ እንዲህ አላቸው፡- ‹‹እነሆ! ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፤ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና፡፡ ይህም ምልክት ይሆንላችኋል፤ ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግምም ተኝቶ ታገኛላችሁ›› አላቸው፡፡ ሉቃ 2፡10-12፡፡ ከመለአኩም ጋራ ሠራዊተ መላእክት መጥተው ‹‹ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ለዕጓለ እመሕያው-ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ›› አሉ፡፡ ቅዱሳን መላእክትም ከእነርሱ ተለይተው ወደ ሰማይ በወጡ ጊዜ እረኞቹ እርስ በርሳቸው ‹‹እንግዲህ እስከ ቤተ ልሔም ድረስ እንሂድ፣ እግዚአብሔርም የገለጠልንን ይህን የሆነውን ነገር እንይ›› ተባባሉና ፈጥነው መጡ፡፡
ማርያምንና ዮሴፍን ሕፃኑንም በግርግም ተኝቶ አገኙ፡፡ አይተውም ስለዚህ ሕፃንየተነገረላቸውን ነገር ገለጡ፤ የሰሙትን ሁሉ እረኞቹ በነገሩአቸው ነገር አደነቁ፤ የብርሃን እናቱ እመ አምላክ ግን ይህን ነገር ሁሉ በልብዋ እያሰበች ትጠብቀው ነበር፡፡ ሉቃ 2፡13-19፡፡
መላእክትም ሰማይ መንበሩ ምድር የእግሩ መረገጫ የሆኑለት አምላክ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በጎል ተኝቶ በጨርቅ ተጠቅልሎ አይተውት ደስ ብሏቸው ወደ ሰማይ ቢያርጉ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በዕሪና ከመንበሩ አይተውት ‹‹ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት›› ብለው አመስግነውት በጣዕም ላይ ጣዕም፤ በጸጋ ላይ ጸጋ ተጨምሮላቸው ደስ ብሏቸዋል፡፡ ልደቱን ይሹታልና፤ መላእክትም ብቻ አይደሉም እንስሳትም አራዊትም ደስ ብሏቸዋል፡፡ ይህም ሊታወቅ አንድ ባሕታዊ ቋርፍ ሲምስ ምዳቋ ‹‹ዮም ተወልደ መድኃኔዓለም ዮም ተወልደ ቤዛ ኵሉ ዓለም ዮምተወልደ ከሣቴ ብርሃን›› እያለች ስትዘል አይቷል። በጌታችን በልደቱ የባሕር ውኃ ወተትና ማር ተራሮች እንጀራ እንጨቶችም የበረከት ፍሬ ሆነዋል፡፡ ልደቱንም በኮከብ ተረድተው ሰብአ ሰገል (የጥበብ ሰዎች) ስማቸውም ማንቱሲማር፣ ሜልኩ በዲዳስፋ የተባሉ የፋርስ ነገሥታት ከገነት የተገኘ ወርቅ፣ ዕጣን ከርቤ አምጥተው ገብረውለታል፡፡
ይህንንስ ከምን አገኙት? ቢሉ አዳም ከገነት ከወጣ በኋላ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ቅዱስ ገብርኤል እና ቅዱስሩፋኤል ወርቅ ዕጣን ከርቤ አምጥተው ሰጡት፡፡ እርሱ ለሔዋን ሰጣት። ሔዋን ለሴት ሰጠችው። ከሴት ሲወርድ ሲዋረድ ከኖኅ ደረሰ። ኖኅ ከመርከብ ከወጣ በኋላ ለሴም ሰጠው። ሴም መልከጼዴቅን አስጠበቀው፤ መልከጼዴቅ ለአብርሃም ሰጠው። ከአብርሃም ሲወርድ ሲዋረድ በዳዊት በሰሎሞን አድርጎ ከአካዝ ደረሰ። በሱ ዘመን ቴልጌልፌልሶር ማርኮ ወስዶ ከቤተ.መዛግብቱ አኑሮታል። አባታቸው ዥረደሽት ይባላል፤ ፈላስፋ ነበር። አንድ ቀን በቀትር ከውኃ ዳር ሆኖ ሲላሰፍ በሰሌዳ ኮከብ ድንግል ሕፃን ታቅፋ አየ። ያየውን በሰሌዳ ቀርጾ አስቀመጠው። ሲሞት ልጆቼ እንዲህ ያለ ኮከብ ሲወጣ ባያችሁ ጊዜ ሰማያዊንጉሥ ይወለዳልና ይህን ወስዳችሁ እጅ ንሱ ብሎ ሰጥቷቸዋል። አንድም በለዓም ‹‹ከያዕቆብ ቤት ኮከብ ይወጣል›› ያለውን ሰምተው ይዘው መጥተዋል፡፡ዘኅ 20፡17፡፡
አንድም ትሩፋን በባቢሎን ሳሉ ነገሥተ ተርሴስ ወደ ስያት ስጦታ (ገጸ በረከት) አመጡ፤ ንግሥተ ሳባ ወዓረብ እጅ መንሻ ያመጣሉ እያሉ ሲጸልዩ ይሰሙ ነበረና ይኸን ይዘው መጥተዋል፡፡ አንድም ባሮክ አቴናወርዶ ነበር። ያን ጊዜ ዛሬ የሀገራችሁን ንጉሥ የሚገብረውን ወርቅ ኋላ ከእኛ ወገን ንጉሥ ሲወለድ ይገብረዋል ብሎ የነገራቸውን ይዘው ነው።
የተወለደ ዕለት ኮከቡን አይተው አባታችን የነገረን ደረሰ ብለው 12 ሆነው ሠራዊቶቻቸውን አስከትለው ተነሱ። ብዙም ሳይርቁ ጠላት ተነስቶባቸው ዘጠኙ ተመለሱ። እኒህ ሦስቱ ግን ኮከቡ እየመራቸው ኢየሩሳሌም ደርሰው በሄሮድስ በኩል አድርገው ቤተልሔም ወርደው አግኝተው ገብረውለታል።


ምሥጢሩም፡-
ወርቅ መገበራቸው: ይኸን የምንገብርላቸው ነገሥታት ቀድሞም ፍጡራን ኋላም ኀላፍያን ናቸው። አንተ ግን ቀድሞም ያልተፈጠርህ ነህ፤ ኋላም የማታልፍ ነህ ሲሉ፤ አንድም ወርቅ ጽሩይ ነው፤ ጽሩየ ባሕርይ ነህ ሲሉ፤ እንዲሁም በአንተ ያመኑ ምዕመናንም ጽሩያነ ምግባር ወሃይማኖት ናቸው ሲሉ። አንድም ወርቅ የሃይማኖት ምሳሌ ነው። የሃይማኖት ጽሩይነቱና ግብዝነቱ የሚታወቅ መከራ ሲቀበሉበት ነውና።
ዕጣን መገበራቸው፡- ይኸንን የምናጥናቸው ጣዖታት ቀድሞም ፍጡራን ኋላም ኀላፍያን ናቸው። አንተ ግን ቀድሞም ያልተፈጠርህ ኋላም የማታልፍ ነህ ሲሉ። አንድም ዕጣን ምዑዝ ነው፤ አንተም በባሕርይ ምዑዝ ነህ ሲሉ እንዲሁ ደግሞ በአንተም የሚያምኑ ምእመናንን ምዑዛነ ምግባር ወሃይማኖት ናቸው ሲሉ። አንድም ዕጣን የተስፋ ምሳሌ ነው። ዕጣን ከሩቅ እንዲሸት ተስፋ ያልያዙትን እንደያዙት ያላዩትን እንዳዩት ታደርጋለችና።
ከርቤ መገበራቸው፡- ምንም ቀድሞ ያልተፈጠርህ በኋላም የማታልፍ ብትሆንም በሰውነትህ መራራ ሞትን ትቀበላለህ ሲሉ፤ አንድም ከርቤ የተሰበረውን ይጠግናል፤ የተለየውን አንድ ያደርጋል። አንተም ከማኅበረ መላእክት የተለየ አዳምን አንድ ታደርገዋለህ፤ ጽንዓ ነፍስ ሰጥተህ ታጸናዋለህ ሲሉ። አንድም በዕለተ ዓርብ ያቀምሱታልና ከርቤ አመጡለት። ከርቤ የምዕመናን ምሳሌ ነው። በፍቅር አንድ ይሆናሉና። ከርቤ የፍቅር ምሳሌ ነው። ከርቤ አንድ እንዲያደርግ ፤ ፍቅርም አንድ ታደርጋለችና።
በአጠቃላይ ሰብአ ሰገል ወርቅ፣ እጣን ከርቤ የገበሩለት ሃይማኖት፣ ፍቅር፣ ተስፋ፣ ገንዘቦችህ ናቸው ሲሉ ነው። በሌላ መልኩ ወርቅ ለመንግሥቱ፣ ዕጣን ለመለኮቱ፣ ከርቤ ለሞቱ ምሳሌ ናቸው።
ሰብዓ ሰገል እጅ ነስተው ከወጡ በኋላ አንዱ እንዴት ያለ ሽማግሌ ነው ብሎ አደነቀ። ሁለተኛው የምን ሽማግሌ ጎልማሳ ነው እንጅ አለ። ሦስተኛው ደግሞ ሕፃን ነው እንጂ አለ። ገብተን እንይ ተባብለው ቢገቡ ሽማግሌ መስሎ ለታየው ጎልማሳ፤ ጎልማሳ መለስሎ ለታየው ሕፃን፤ ሕፃነ መስሎ ለታየው ሽማግሌ መስሎ ታያቸው። ወጥተው እንዳንተ ነው እንዳንተ ነው ይባባሉ ጀመር። መልአኩ መጥቶ እንደሁላችሁም ነው አላቸው። በጆሮ የሰሙትን በዓይን ቢያዩት ይረዳል ብለው ለሦስተኛ ጊዜ ገቡ። ሽማግሌ ጎልማሳ መስሎ ለታየው ሕፃን፤ ጎልማሳ ሕፃን መስሎ ለታየው ሽማግሌ፤ ሕፃን ሽማግሌ መስሎ ለታየውጎልማሳ መስሎ ታያቸው። እጹብ እጹብ ብለው አመስግነው፤ አምላክነቱን ተረድተዋል። በሚሄዱበትም ጊዜ እመቤታችን የገብስ እንጀራ ጋግራ ሰጠቻቸው። ሀገራቸው እስኪገቡ ድረስ ከሠራዊቶታቸው ጋር (እያንዳንዳቸው አስር ሺህ፤ አስር ሺህ ሠራዊት) ሲመገቡ ቆይተው ከከተማቸው ሲደርሱ ይህን ቅዱስ ምግብ ከከተማችን አናስገባም ብለው ከከተማው በር ቀብረውት ገቡ። ደርሳችሁ መጣችሁን? አሏቸው። አዎን በአርባ ቀን መጣነው፤ እናቱም የሰጠችንን የገብስ እንጀራ እኛ እና ሠራዊቶቻችን ስንመገበው መጥተን ከከተማችን አናገባም ብለን ከከተማው በር ቀብረነዋል አሏቸው። አሳዩን አሉ። ተያይዘው ቢሄዱ ሲጨስ አግኝተውታል።
የልደት በዓል መቼ መከበር ጀመረ? ቀኑስ ምን ቀን ይውላል?
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበትን እርግጠኛውን ዕለት ለማወቅ የአስትሮኖሚ፣ የአርኬዎሎጅና የታሪክ ምርምር ሰዎች /ሊቃውንት/ ብዙ ጥናት አድርጓል፡፡ ዳሩ ግን በአንድ ሐሳብ ሊስማሙ ባመቻላቸው፣ የክርስቲያኑ የቀን መቈጠሪያዎች በዚሁ ሁኔታ አንድ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡ ይሁን እንጂ በኢትዮጵያ መከበር የተጀመረው ከአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ እንደሆነ ታሪክ ያስረዳል፡፡ ለዚህም በጎርጎርዮሳውያን የዘመን ለቈጣጠር የሚጠቀሙት የዓለም ሕዝቦች የክርስቶስን ልደት እኛ ኢትዮጵያውያን ከምናከብረው የልደት በዓል 13 ቀን ቀድመው ያከብራሉ፡፡ የሮም ቤተ ክርስቲያን የጌታችን ልደት በታኅሣሥ 25 ቀን ታከብር እንደ ነበር ከ336ዓ.ም ጀምሮ ግልጽ ነው፡፡ ይህ ቀን በአህዛብ ዘንድ የፀሐይ በዓል እየተባለ ይከበር ስለነበር ክርሰቲያኖች ይኽንን የጣኦት አምልኮ ጠባይ ያለውን በዓል ለማጥፋት ሲሉ የጌታን ልደት በዚሁ ቀን ማክበር ጀመሩ፡፡ የምሥራቅ ቤተ ክርስቲያንም ቅድሚያ ሰጥታ የምታከብረው እ.ኤ.አ ጥር 6 ቀን የሚውለን የኤጲፋንያ በዓል ነበር፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ግንየጌታን ጥምቀቱና ልደቱን ጥር 6 ቀን ስታከብር እንደቆየች የእውቀትና የታሪክ መድበል /ኢንሳይክሎፕዲያ/ ይገልጻል፡፡
*ቤተ ክርስቲያን አንዲት ስትሆን በክርስቲያን ዓለም ውስጥ እንዲህ ያለ ልዩነት እንዴት ሊፈጠር ቻለ?በመሠረቱ ዓለም ከመለያየት በስተቀር አንድ ለመሆን ያሰበበት ወቅት ምን ጊዜ የለም፡፡ (በታሪክ እንደምንረዳው) ልዩነቱ እንዴት እንደሆነ እንመልከት
*ከጌታ ልደት አስቀድሞ /በፊት/ በ46ዓ.ዓ ጁሊዮስ የተባለው የሮማ ቄሣር በጊዜው የከዋክብት መርማሪ የነበረው ሶስግነስን አስጠርቶ ተመሰቃቅሎ የነበረውን የዘመናት አቈጣጠር እንዲያስተካክል አዘዘው፡፡ ይኸም፣ ሊቅ ፈቃደኛ ሆኖ ዓመቱንም በ12 ወሮች ከፋፍሎ እያንዳንዱን ወር ከየካቲት በስተቀር በማፈራረቅ 31 እና 30 ቀናት እንዲኖራቸው አድርጎ አዘጋጀ፡፡ የካቲት ወር ግን 29 ቀን እንዲኖረው አደረገ፡፡ ነገር ግን በየአራቱ ዓመቱ አንድ ቀን ትርፍ ስለሚመጣ በአራተኛው ዓመት የካቲት 30 ቀን እንዲሆን ወሰነ፡፡ ጁሊየስ ቄሣርም የሮማው ሕዝብ በዚሁእንዲገለገል አዋጅ አወጀ፡፡ በተጨማሪም ጁሊየስ የዓመት መለወጫ መጋቢት የነበረውን ለውጦ /አዛውሮ/ ጥር እንዲሆን አደረገ፡፡ በዚሁም የጁሊየስን የዘመን አቈጣጠር ብዙ ሀገሮችለ1500 ዓመታት ያህል ሲገለገሉበት ቈይተዋል፡፡ ምክንያቱም የዓመቱ ቀናት ተቀምረው 365 ቀን ከሩብ ሊሆን መቻላቸው ነበር፡፡ ይህም ሆኖ የጁሊየስ አቈጣጠር ህጸጽ አልታጣበትም ምክንያቱም 11 ደቂቃ ከ14 ሰኮንድ ትርፍ ያሳይ ነበርና፡፡ ከዚህም የተነሳ እ.ኤ.አ በ1582ዓ.ም የነበረው የሮማው ፖፖ ጎርጎርዮስ /ስምንተኛ/ የከዋክብትን ሊቃውንት ሰብስቦ ከተመካከረበት በኋላ የዘመኑ አቈጣጠር ተሻሽሎ እንዲሰራበት አዋጅ አስተላለፈ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን በጎርጎርዮስ የዘመን አቈጣጠር መቈጠር ጀመረች፡፡ በእምነት ተከታዮቻቸው የሆኑትም አገሮች ተቀብለው ወድያውኑ በሥራ ላይ ሲያውሉት የጀርመን ግዛቶች ግን እስከ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ በጁሊዮስ አቈጣጠር ይጠቀሙ ነበር፡፡ እንግሊዝም ብትሆን አዋጁን የተቀበለችው በ1752ኛ.ም እ.ኤ.አ ነው፡፡ ከዚያ ወዲህ ግን ምዕራባውያን አገሮች ተቀብለውታል፡፡ይህም ሊሆን የቻለው በ1582ዓ.ም የተጨመሩት 10 ቀናት ተጠራቅመው ጎርጎርዮስና ጁሊዮስ በተባለው የዘመን አቈጣጠር መኻከል ልዩነት ስለፈጠሩ ነው፡፡
*በዘመን አቈጣጠር ልዩነት የተነሣ የምዕራባውያንና ኢትዮጵያውያን የልደት በዓልን በማክበር በ13 ቀናት ይለያያሉ፡፡ ይሁን እንጂ በመጀመሪያው እንደተናገርኩት ዓለም ብዙ ጊዜ ስለ ዘመን አቈጣጠር ችግር ገጥሟት እንደ ነበረ ግልጽ ቢሆንም ኢትዮጵያ ግን በዘመነ ኦሪትም ሆነ በዘመነ ሐዲስ እንደ ንጋት ኮከብ የሚያበሩ ልጆች ስለነበሯት በቊጥር ግራ አልተጋባችም፡፡ ቀድሞም ዛሬም ባህልዋንና ቀመርዋን እንደያዘች ትገኛለች፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ አቈጣጠር ደግሞ እንደሚከተለው እንመልከት፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አቈጣጠርበዘመናችን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የጌታ ልደት ሌሎች አብያተ ክርስቲያናት እንደሚያከብሩት ለምን አታከብርም? የሚል ጥያቄ በየአቅጣጫው ከተሰማ ውሎ አድሯል፡፡ አንድ ነገር መታወቅ ያለበት ግን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በዓለ ልደትን 29 ቀን የምታከብረው ብቻዋን ሳትሆን ከእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ጋር በመሆኑ ነው፡፡
*በቀን አከባበር ስለተፈጠረው መለያየት ምክንያቱንና የነገሩን ምንጭ ከእነማስረጃው አትቶ "በእንተ ልደት ድንግልናዌ" በሚል ርዕስ የእስክንድርያው ሊቅ ዮሐንስ አቤል ሄረም ጽፎት ይገኛልና ከዚያ መመልከት ይጠቅማል /አንቀጽ 84/ ዓይነተኛ ጉዳዩ ግን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃነት የተመሠረተ ነው ብላ ስለአመነችበት እንጂ ብዙ ዘመናት ሲሠራበት በመቈየቱ ወይም ደግሞ የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ስለምታከብረው ብቻ አይደለም፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት ስለ አለው ማስረጃ እንደሚከተለው እንረዳለን፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ የተጸነሰበትም ቀን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በድንግል ማኅፀን ለተጸነሰበትና ለተወለደበት ቀን መነሻ ሆኖ የሚገኝበት አለ፡፡ ይኸንም ለመረዳት ወንጌላዊ ሉቃስ የጻፈውን እንመልከት፡፡
*በይሁዳ ንጉሥ በሄሮድስ ዘመን ከአብያ ክፍል የሆነ ዘካርያስ የሚባል አንድ ካህን ነበረ፡፡ ሚስቱም ከአሮን ልጆች ነበረች፡፡ ስምዋም ኤልሳቤጥ ነበረ፡፡ ሁለቱም በጌታ ትእዛዝና ሕግጋት ሁሉ ያለነቀፉ እየሄዱ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን ነበሩ፡፡ ኤልሳቤጥም መካን ነበረችና ልጅ አልነበራቸውም፣ ሁለቱም በዕድሜያቸው አርጅተው ነበር፡፡ እርሱም በክፍሉ ተራ በእግዚአብሔ ፊት ሲያገለግል፣ እንደ ካህናት ሥርዓት ወደ ጌታ ቤተ መቅደስ ገብቶ ለማጠን ዕጣ ደረሰበት፡፡ በዕጣንም ጊዜ ሕዝቡ ሁሉ በውጭ ቁመው ይጸልዩ ነበር፡፡ የጌታም መልአክ በዕጣኑም መሠዊያ ቀኝ ቆሞ ታየው፡፡ ዘካርያስም ባየው ጊዜ ደነገጠ፣ ፍርሃትም ወደቀበት፡፡ መልአኩም እንዲህ አለው፡፡ ዘካርያስ ሆይ ጸሎትህ ተሰምቶልሃልና አትፍራ፣ ሚስትህ ኤልሳቤጥም ወንድ ልጅ ትወልድልሃለች፣ ስሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ ደስታና ተድላም ይሆንልሃል፣ በመወለዱም ብዙዎች ደስይላቸዋል፡፡ በጌታ ፊት ታላቅ ይሆናልና /ሉቃ.1፡5-15/፡፡
*ወንጌላዊ ከተረከው የተገኘ ቅርጸ ሐሳብ የቱ ነው? ተብሎ ቢጠየቅ ትክክለኛ ጥያቄ ሆኖ ይገኛል፡፡ ፍሬ ሐሳቡ መልአኩ ገብርኤል ለዘካርያስ ስለመጥምቁ ዮሐንስ መወለድ ያበሠረበት ጊዜ መቼ ነው? የሚለው ነው፡፡ ይኸ በዕብራውያን ዘንድ በዓለ አስተሥርዮ ተብሎ ይከበር የነበረው ቀን መሆኑነው፡፡ በዓለ ሥርየትም ሲባል ደግሞ በዕብራውያን አቈጣጠር በሰባተኛው ወር ማለት /ጥቅምት አሥር ቀን የሚውል ታላቅ በዓል ነው/ /ዘሌ.16፡29-34/፡፡ /ዘኊ.29፡7-11/፡፡
*እነሆ ዘካርያስ ወደ ቤተ መቅደስ በገባ ጊዜ መልአኩ ያበሠረው በዚህ ጊዜ ነው፡፡ /ሉቃ. 1፡8-10፡21/፡፡ ይህ ዘካርያስ የተበሠረበት ቀን በአይሁድ በዓለ ሥርየት የዋለበት በዕብራውያን የዘመን አቈጣጠር ጥቅምት 10 ቀን ለመሆኑ ከጥንት አባቶች ዮሐንስ አፈወርቅ ማር.ዮሐንስ መስክረዋል፡፡ አሁንም ደግሞ ይህ ቀን ከኢትዮጵያ የቀን አቈጣጠር ያለው ተዛምዶ እንደሚከተለው ነው፡፡ መጀመሪያ ነገር በባሕረ ሐሳቡ የአቈጣጠር ሕግ እንደሚታወቀውሁሉ 5500ዓመተ ዓለምን በዐቢይ ቀመር፣ በንዑስ ቀመር፣ በማዕከላዊ ቀመር ተተንትኖ ተከፋፍሎ ውጤቱ የ5500 ዓመተ ዓለም ተረፈ ቀመር 9 ሆኖ ስለሚገኝ አንድን ለዘመን አትቶ መንበሩ 8ይሆናል፡፡ 8x11=88-60=28 አበቅቴው 28 ካለፈው የተያዘ 11የጨረቃ እና ዕለቱ 28 አበቅቴ ሲደመር ሠረቀ ሌሊቱ፣ 10 ሆኖ መጥቅዑም 2 ይሆናል፡፡ በሠረቀ ሌሊቱ 10+4=14 ጨረቃ ሆነ፡፡ እንግዲህ 14 የጨረቃ ሌሊት ይዘን እስከ መስከረም 16 ቀን ብንሄድ በዚያን ጊዜ የጨረቃ ብርሃን 29 መሆኑን ያሳየናል፡፡ መስከረም 18 ቀን ደግሞ የጨረቃ ብርሃናዊ ልደት ነው፡፡ የአይሁድ የቀዳማዊ ወርኅ ታሥሪን /መባቻ/ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ፀሐያዊ አቈጣጠር መስከረም ስለ አላለቀ እንዲህ እያልን እሰከ መስከረም 27 ቀን እንሄዳለን፡፡ በዕብራውያን ጥቅምት 10 ቀን ሲሆን በእኛ ደግሞ መስከረም 27 እንደነበረ እንረዳለን፡፡ በዚሁ ዘካርያስ ልጅ እንደሚወልድ ተበሠረ፡፡ ዘካርያስም ይህን አገልግሎት ከፈጸመ በኋላ ከበዓለ ሥርየት በኋላ እስከ 15ኛው የጥቅምት ጨረቃ በዓል ስለአልነበረ ወደ ቤቱ ገባ መጥምቁ ዮሐንስ ተጸነሰ፡፡ ይህም ሊቁ ኢትዮጵያዊው ቅዱስ ያሬድ ከሁለት ቀንም በኋላ ኤልሳቤጥ ጸነሰች፡፡ በማለት አስረድቶናል፡፡ አቡን /ብርሃነ ሕይወት/ ድጓ የታኅሣሥ ገብርኤል/ ቅዱስ ያሬድ ከሁለት ቀን በኋላ ኤልሳቤጥ ጸነሰች ያለው ቀንና ዘካርያስ ልጅ እንደሚወልድ እስከ ተበሠረበት ድረስ ያለው ቀን ብንደምረው ከመስከረም ይዘነው የመጣን 27 ቀን፣ የክህነት አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደ ቤቱ እስከ ተመለሰበት ድረስ ያለው ጊዜ 3 ቀን፣ 27+3=30 ቀናት ይሰጠናል፡፡
*ሐዋርያው ሉቃስ ወደ ጻፈው ቃል እንመለስ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ኤልሳቤጥ ከጸነሰች በስድስተኛው ወር ወደ ቅድስት ድንግል ማርያም መላኩ፣ እና ቅዱስ ሉቃስም ዮሐንስ ከተጸነሰ በኋላ ኢየሱስ ክርስቶስም በስድስተኛው ወሩ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋን፣ ከነፍስዋ ነፍስን ነሥቶ ሰው የሆነበት ዕለት፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የትርጓሜና የቊጥር መምህራን በማያሻማ መልኩ ተንትነው ቀምረው ለዚህ ትውልድ ማድረሳቸው እግዚአብሔር ከእነሱ ጋር እንደ ነበር ቋሚ ማስረጃ ነው፡፡ እንግዲህ የዮሐንስ ትንቢታዊ መጸነስ ክርስቶስ ሰው ለሚሆንበት ቀን የዕለታት ፋናው እያበራ ክርስቶስ ተጸንሶ እስከ ተወለደበት ዕለት ያደርሰናል፡፡
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መጋቢት 29 ቀን ተጸንሶ ታኅሣሥ 29 ቀን ስለመወለዱጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቼ ተጸንሶ መቼ እንደተወለደ ለማወቅና ለመረዳት ሐዋርያው ሉቃስ ወደተለመልን የአኀዝ ቊጥር እንመለሳለን፡፡ እነሆም በስድስተኛው ወር መልአኩ ገብርኤል በናዝሬት ወደም ትኖር ወደ ድንግል ማርያም ተልኮ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን እንደምትጸንስና እንደምትወልድ ነገራት /ሉቃስ. 1፡26-38/ ይህም ቀን በኢትዮጵያ አቈጣጠር መጥምቁ ዮሐንስ ከተጸነሰበት ዕለት ጀምሮ ተቈጥሮ መጋቢት 29 ቀን መሆኑ እንገነዘባለን፡፡ ለምሳሌ ጥቅምት፣ ኅዳር ታኅሣሥ፣ ጥር፣ የካቲት፣ መጋቢት ድምር 6 ወር ነው፡፡ስለዚህ መጋቢት 29 ቀን ቃል /ቃለ እግዚአብሔር ወልድ/ ሰው ሥጋ የሆነበት፤ በድንግል ማኅፀን ያደረበት፤ በዓለ ትስብእት ነው፡፡ አሁን /ሰው የመሆኑ/ ሰው የሆነበት ቀን ከተረዳን፤ የተወለደበት ቀንና ወር ለማረጋገጥ ከመጋቢት 29 ቀን እስከ ታኅሣሥ 28 ቀን ጳጒሜን ጨምሮያለው ጊዜ 275 ቀናት ይሆናሉ፡፡ ይህም 275 ለ30 ሲካፈል 9 ወር ከአምስት ቀን ይሆናል፡፡ ይህም ማለት ከመጋቢት 2 ቀን፣ ከሚያዝያ እስከ ኅዳር መጨረሻ ወር ያሉት ወራት (8x30=240) ቀናት፣ 5 ቀናት የጳጒሜን፣ 28 ቀን ከታኅሣሥ፤ አጠቃላይ ድምር 275 ቀናት ናቸው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሠ ድንግል 9 ወር ከአምስት ቀን ከቈየ በኋላ በዕለተ ሠሉስ ታኅሣሥ 29 ቀንበ1ዓ.ም ከሌሊቱ 7 ሰዓት እስከ 10 ሰዓት ባለው ጊዜ በቤተልሔም ተወለደ፡፡ /ጊዮርጊስ ወልደ አሚድ ገጽ 158 እና 159/፡፡
ይህም በሒሳባዊ መንገድ የሚደረስበት ስለሆነ አያጠራጥርም፡፡ ሕጋዊ የሆነ የወንድ ልጅ በእናቱ ማኅፀን ተጸንሶ እስከሚወለድበት ጊዜ ድረስ የሚቈይባቸው ቀናት ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ለመሆኑ ከብዙ ዘመናት ጀምሮ ታምኖበት የቈየ ነው፡፡ አንዳንድ የቀናት መብዛትና ማነስ የሚታየው ህጸጽ አይነካውም /ኢሳ 7፡14፣ ገላ4፡4/፡፡ እነሆ ምሥራቃዊ ኮከብ ሰብአ ሰገልን የተወለደው ሕፃን እስከ አለበት ቦታ እየመራ እንዳደረሳቸውሁሉ ወንጌላዊው ሉቃስም እያነጣጠረ ያመለከተው ዘካርያስ የተበሠረበት ኮከባዊ ቀንም ፋናውን እየተቈጣጠረች ለምትከታተል ኢትዮጵያዊት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሕፃኑ ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ ተወለደበት እንዳደረሳት ታምናለች፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያዊት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጌታን ልደት ታኅሣሥ 29 ቀን በታላቅ ምሥጋና ታከብረዋለች፡፡ /ማቴ. 2፡1-11፣2ጴጥ.1፡19-21/፡፡
ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጋር በዓለ ልደትን የሚያከብሩ አገሮች ወይም አብያተ ክርስቲያን፣ ግብጽ፣ ሶርያ፣ ህንድ፣ ኢትዮጵያ፣ አርመን ሲሆኑ ከሩቅ ምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ደግሞ የግሪክ ኦርቶዶክስ የሩሲያ ቤተ ክርስቲያን ናቸው፡፡ አውሮፓውያን በዓለ ልደትን የሚያከብሩት ከእኛ 13 ቀናት ቀደም ብለው ነው፡፡ ይህም ማለት በእኛ አቈጣጠር ታኅሣሥ 16 ቀን ነው እንደ አውሮፓውያን ዘመን አቈጣጠር December 25 ቀን ነው፡፡ ልዩነቱ ለማወቅ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በዓለ ልደትን የምታከብረው ታኅሣሥ 29 ቀን ነው ይህም ማለት ከ29-16=13 ቀናት ወይም 16+13=29 ቀን ይሆናል፡፡ ይህ ቁጥር የሚያሳየን አውሮፓውያን ከእኛ በ13 ቀናት ቀድመው በዓለ ልደትን ሲያከብሩ ኢትዮጵያውያን ግን ከ13 ቀናት በኋላ ቈይተው ታኅሣሥ 29 ቀን በዓለ ልደትን ያከብራሉ፡፡
ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ታኅሣሥ 29 ቀን ለመወለዱ የመሰከሩ ሊቃውንት
1. ማሪ.ኤፍሬም ሶርያዊ
2. ሰዒ.ድ ወ/በጥሪቅ
3. መበንጋዊ/ማኅቡብ
4. ጊዮርጊስ ወልደ አሚድ
5. ወልደ መነኮስ
6. በዲድስቅልያ አንቀጽ 29 ገጽ 37
7. የኢትዮጵያ መምህራን ሁሉ ናቸው
‹‹በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች ታላቅ ብርሃን ወጣላቸው፤ በቅዱሳን ላይ የሚያድር እግዚአብሔር እኛን ለማዳን ልዩ ከሆነች ድንግል ሰው ሆኗልና ኑ ይህን ድንቅ እዩ፤ ስለተገለጠልን ምሥጢር ምስጋና አቅርቡ፤ ሰው የማይሆን ሰው ሆኗልና ቃል ተዋሕዷልና ጥንት የሌለው ሥጋ ጥንታዊ ቀዳማዊሆነ፣ ዘመን የማይቆጠርለት መለኮት ዘመን ተቆጠረለት፡፡ የማይታወቅ ተገለጠ፣ የማይታይ ታየ፣ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ በእርግጥ ሰው ሆነ፡፡››
‹‹ሰው ሆይ! ፈጽመህ ደስ ይበልህ፣ እግዚአብሔር ዓለሙን ወዶታልና አንድ ልጁንም የሚያምንበት ሁሉ እስከ ዘለዓለም ፈጽሞ ይድን ዘንድ አሳልፎ ሰጥቷልና ልዑል ክንዱን ሰደደልን፡፡››
ሰው ሆይ! ፈጽመህ ደስ ይበልህ!!!ፍጹም መዳን ይሆንላችሁ ዘንድ በስሙ አምናችሁ ለአምላክነቱ የምትገዙለት የክርስቶስ ወገኖች በእናቱም በወላዲተ አምላክ በድንግል ማርያም ፍጹም አማላጅነት የምትታምኑ የተዋሕዶ ልጆች ሁላችሁ እንኳን ደስ አላችሁ፣ እንኳን ደስ አለን፡፡ እንኳን አደረሳችሁ፣ እንኳን አደረሰን፡፡
(ምንጭ፡- ተአምረ ማርያም፣ ስንክሳር ዘውርሃ ታኅሣሥ፣ ቅዱስ እግዚአብሔር አብ ሰ/ት/ቤት እና የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ያዘጋጇቸው ጽሑፎች)



ዓለምን የቀየረው የከበረው የክርስቶስ ልደት

 


ዓለም ካስተናገደቻቸው የታላላቅ ሰዎች፣ ነገሥታት ወይም ቅዱሳን ልደት ሁሉ የከበረው ልደት የትልቁ የክርስቶስ ልደት ነው።

የሁሉም ልደት የሚከበረው በተወሰኑ የሕብረተሰብ ክፍሎች ብቻ ሲሆን የክርስቶስ ልደት ግን በዓለም ሁሉ ውስጥ ባሉ አማኞችም ሆነ በፈላስፎችና በኢአማንያንም ዘንድ ሳይቀር ይታሰባል ይታወቃልም ።
ይህም የሆነበት ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደበት በተወደደችው ዓመት የዓለም ሚዛን በአማንያንም በኢአማንያንም ዘንድ የተዛባበት ወቅት ስለነበረ ነው። አማኞቹ አዳማውያን በመንፈሳዊው ሕይወት በዲያብሎስ ቅኝ ግዛት ጀርባቸው ጎብጦ ነፍሳቸው ዝሎ ግዞተኞች ሆነው ነበረ።
በአንጻሩ ዓለም በተለይ ከአባታቸው አብርሃም ወገን ክርስቶስ የተወለደው ዕብራውያን በተደጋጋሚ ጦርነትና በቅኝ ግዛት ተሰቃይተው በኢኮኖሚም ቢሆን ከስረው የነበረበት ዘመን ነበረ። ጥበብ ጠፍቶ ጠቢባን ዕውቀታቸው ለዛውን ባጣበት ወቅት የአብርሃም ተስፋ እንባን የሚያብሰው መንግስትን የሚመልሰው ጥበብ ክርስቶስ ተወለደ ከሚል የምስራች በላይ ምን ደስታ ይኖራልና።
ዓለም ሁሉ ጭው ብሎ ሰዎች ለመኖር ምንም ዋስትና ባላገኙበት በዚያ ዘመን ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለም ተስፋ ሆኖ በዓለም ላይ አዲስ ብርሃን ከማብራት በላይ ምን ትልቅ ዜና ይኖራል(ሉቃ ፪፥፲-፲፪)
የዓለምን ሚዛን የሚቀይረው ወንድ ልጅ ፣ ንጉሥ ተወለደ የሚለው ቃል ሙት የሚቀሰቅስ ድምጽ ነበር። እውነትም የሚታይ ነገር ባይኖር ሁሉም ነገር ተስፋ አስቆራጭ በሆነበት ዘመን ሁሉን አዲስ የሚያደርግ ንጉሥ የመወለዱ ዜና የተቆረጠ ተስፋን የሚቀጥል ነበር።
ዛሬም ጥያቄዎች የበዙበትና ሰዎች ለመኖር ምክንያት ያጡበት ዘመን ይመስላል። ራስ ወዳድነት ነግሷል ሰው ሠራሽ ደስታዎችም የቆርቆሮ ጩኽት ሆነዋል ሰው እንደ አበደ ውሻ እርካታን አጥቶ ይቅበዘበዛል፤ ስልቹነትም ወረተኛ አድርጎታል የመኖር ቁም ነገሩ ገንዘብ ሆኗል፣ ሕግ ሚዛናዊነትን አጥቶ ድሆችን ሲገዛ ባለጠጎች ግን ይገዙታል፤ ታማኝነት ጊዜ ያለፈበት ሆኗል፤ ትልቁ ተቋም ቤተሰብና ትዳር ፈርሷል ፣ አደንዛዥ ዕፅ ና ግብረ ሰዶማዊነት ብልጭልጩ ዓለም ትውልዱን ማርከውታል። ጅምላ ጨራሽ መሣሪያዎች ፣ የተፈጥሮ አደጋዎች ፣ረሃብና ቸነፈር ሥጋት ሆነው ሳለ ሌላ የጦርነት ሥጋት ደም መፋሰስና እርስ በእርስ መጨካከን ትውልዱን አስጨንቆታል፣
ሕይወት ለብዙዎች ትርጉም የለሽ ሆኗል ብዙዎች እንደ ሸማኔ መወርወሪያ ቁም ነገርና ዝቅጠት ላይ ደርሰው ይመላለሳሉ። ብቻ ምን አለፋን ትውልዱ ለወንድሜ ከማለት ይልቅ የራስ ወዳድነት አባዜ ተጸናውቶት ከእናቱ መሃረብም ቢሆን ይሰርቃል፣ የእናቴ ልጆች ተጣሉኝ እንዳለ ዮሴፍ የእናቱን ልጅ ወንድሙን በግፍ እንደ ቃኤል ይገድላል።የረጋ ምንነት ሲጠፋ ሰው ራሱን ማግኘት በፍጹም አልቻለም።
ታዲያ ይህ ሁሉ ቢሆን እንኳ በጭራሽ ቀኑ አልጨለመም፣ እንዲያውም በጨለማ ለሄደው ሕዝብ ሁሉ ብርሃን ወጣ እንጅ (ኢሳ ፱፥፪) ፣የሰው እንጅ የእግዚአብሔር መልካምነት አላለቀም ፣ የተስፋችን የክርስቶስ ልደትም ሁልጊዜ አዲስ ነው ፣ የዓለምን ሚዛን የሚቀይረው ወንድ ልጅ ተወለደ የሚለው ዜና ዛሬም ትኩስ ዜና ነው፣አለቅነት በጫንቃው ላይ የሆነ ድንቅ መካር ኃያል የሰላም አለቃ ነውና (ኢሳ ፱፥፮)
ከሁኔታዎች በላይ የሆነው ታላቁ የምስራች፣ አእምሮን ሁሉ የሚያልፈው ሰላም ክርስቶስ ወወለዱ ነው። ታላቁ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በሰዓታት ድርሰቱ " ሞገድ የማይቀርበው መርከባችን ፣ ብል የማያበላሸው መዝገባችን የእግዚአብሔር ልጅ ነው"። እንዲል ጨለማ ያላሸነፈው ለሁላችን የወጣው የጽድቅ ፀሐያችን አማኑኤል ነው(ሚል፬፥፪)። ዓለም የሌላት ያለው ጥበብ እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። በፈረሰው ግርግዳ በኩል የሚቆም ጉድለታችን የሚሞላ ሙላታችን መሲሑ ነው። ዛሬ ሁላችን የሰው ልጆች በተለይ እኛ ኢትዮጵያውያን በዙሪያችን ያሉት የእኛ የሆኑት ወገኖቻችንም ሆኑ ክስተቶች ሁሉ በእጅጉ ያስፈራሉ ፣ ነገር ግን ከወደቅንበት ተነስተን በእምነት ሆነን ክርስቶስን ካየን ልደቱን ካስተዋልን በሁሉ ነገር ላይ እንደፍራለን እንጽናናለን። መድኃኔዓለም ክርስቶስ በሁሉ ነገር ላይ ስልጣን አለው። ረቂቃኑ ነፋሳትና የባህር ማዕበል እንኳ የሚታዘዙለት እርሱን ብናምነው ጌታችን ነው ፣ የማይታለፈውን እናልፋለን ፣ ክፉውን ዘመን እንሻገራለን። (ማቴ፰፥፳፯)


ከሰው ልጆች የሃይማኖት መጥፋት ዓለምን ሥርዓት የለሽ ቢያደርጋት የሕግ የበላይነት ቢጠፋ፤ መልካም ሰው በመብራት ተፈልጎ ቢታጣ ፤ ሰው ለሰው መድኃኒቱ መሆኑ ቀርቶ ፍርሃቱ ቢሆንም እንኳ በእምነት ከሆንን "መንግስትና ኃይል የእግዚአብሔር ናትና " በምንም አንፍራ አንሸበር ጸንተን እንቁም። (ማቴ፮፥፲፫) ሁኔታዎች ከምንጊዜውም በላይ አደጋ ያንዣበበት ጊዜ መሆኑን ቢያሳዩም በክርስቶስ ለሚያምን ግን በጽናት ይህን ያልፋል። በቤተክርስቲያናችን የኪዳን ጸሎት "መናፍስት ያመጡትን የጎርፉን ፈሳሽነት ፀጥ ያደረግህልን ፤ ከጥፋት አድነህ የሕይወት ወደብ የሆንከን ፣የዘላለም ድኅነት ያለበት መሸሻ የሆንከን ፣በማዕበል የተጨነቁትን የምታድን አንተ ነህ።" እንዲል ሁሉን መሻገሪያ ወደባችን ሰላማችን ክርስቶስ ነው።
የሰው ልጆች ከኖሩበት ብዙ የታሪክ ምእራፍ እንዲህ እንዳለንበት ዘመን ራሳቸውን በሥልጣኔና በቴክኖሎጅ የለወጡበት ዘመን የለም። ሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን የዕውቀትና የመረጃ ዘመን ነው። አለም አንድ መንደር ሆናለች፣ አንድ ሰው ስለ ሰፈሩ ከሚያውቀው በላይ ስለ ዓለም በቂ ግንዛቤ አለው። ነገር ግን ዓለም በዘመናችን በብዙ ያልተመለሱ ጥያቄዎች ተሞልታለች። የነፍስን ባሕርይ የሚሞላ ዕውቀት እንጅ የመንፈስን ጥም የሚያረካ ነገር ጠፍቷል፣ ከትውልዱ ቅድስናና ፍቅር ርቋል (፪ጢሞ ፫፥፩-፱) ። ያለ እግዚአብሔር ጣልቃ ገብነት ሕይወት አስቸጋሪ መሆኗ ከመቼውም ጊዜ ይልቅ እውን ሆኗል። እግዚአብሔር ግን ላለብን የሥጋና የነፍስ ጥያቄ ከልጁ የተሻለ መልስ አይሰጠንም። ለዛሬና ለወደፊት ጥያቄዎቻችን ሙሉ መልስ አድርጎ አንድያ ልጁን በዳግም ልደት ሰጥቶናልና ። ክርስቶስ ካለን ለጥያቄዎች ሁሉ መልስ አለን ፣ ክርስቶስ ከሌለን ሁሉ ነገር ጥያቄ ይሆንብናል።
እግዚአብሔር የሰው ልጆችን በእጆቹ አበጃጅቶ በመዳፉ ቀርጾ የፈጠረው ለውርደትና ለጥፋት ሳይሆን ለክብር ነው። ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ ክብሩን አላወቀም እንዲል ነቢዩ (መዝ፵፰፥፲፪) ከታሰበለት ደረጃ በመውረድ ማለቂያ ለሌለው ለዚህ ሁሉ ምስልቅል መዳረጉ የእምነት መጉደልና የኃጢአት ውጤት ነው። የእግዚአብሔር ሃሳብ አሰናካይነት የለውምና ዛሬ በእምነት በንስሐ ተመልሰን በልደቱ የምሥራች ሐሴት ካደረግን እርሱ ሁሉን አዲስ ሊያደርግ የታመነ ነው። (ራዕ ፳፩፥፭) በታማኝነትና በጽድቅ የተሞላች መንግስቱን ይመሠርታል (ኢሳ ፲፩፥፩-፱) ተብሎ እንደተጻፈ የጌታችን ልደት ላለፉት ፳፻ ፲፫ ዓመታት ቀስትና ጦርነትን ሽሯል፣ ፍትህን አጽንቷል፣
የታሰሩትን ፈቷል። የመጣው ለድሆች የምሥራችን ይሰብክ ዘንድ፣ልባቸው የተሰበረውን ይጠግን ዘንድ ፣ ለተማረኩት ነጻነትን ለታሰሩት መፈታትን የሚያለቅሱትንም ያጽናና ዘንድ ነውና (ኢሳ፷፩፥፩-፮)።
እንደ ንጉሥ ይነግሣልና እርሱ በፍቅር በትር የሚገዛ ገዥ ነው፣ የእግዚአብሔር መቅደስ በሰዎች መካከል ይሆን ዘንድ፣ ጸብና ክርክር እንዲወገድ የክርስቶስን የልደት ዜና እኛ በንስሐ ልደት ተወልደን እናክብር (ኢሳ፲፩፥፩-፬)።
ይህ ሲሆን ሰው ሰውን የማይጠግበው ይሆናል ፣ የታወከው የዛሬው ሥርዓት በእግዚአብሔር የሰላም ወንዝ ይለመልማል። የተበላሸው የሰው ልጆች የሞራል ልሽቀትና ግብረገብነት ይስተካከላል። በሰላም አገር በኢትዮጵያም ዘረኝነት ጦርነትና ደም መፋሰስ ያለፈ ሥርዓት ይሆናል (ኤር ፳፫፥፩-፭)። ሁላችንንም ለኃጢአት የሚፈትነን አሮጌውን ተፈጥሮ የፈሪሳውያን እርሾ በክርስቶስ ይለወጣል።(ሮሜ ፰፥፳፫፤ ፪ ቆሮ ፭፥፩፥፭) እርግማን ሁሉ በበረከት ይለወጥልናል፣ ሰላም መኖሪያችን ፍቅርም ምግባችን ይሆናል ፣ እንደ ሸማም የምንደርበው የዘወትር ኩታ ይሆንልናል።
በከብቶች በረት ራሱን ዝቅ አድርጎ በትህትና ለእኛ ክብር ከተገለጠው ጌታ ጋር በማያልፍ ሕይወት እንኖራለን።


Thursday, November 12, 2020

ዳግሚት ሔዋን (አዲሲቱዋ ሔዋን )




ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር << በአንተና በሴቲቱ በዘርህና በዘርዋ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ : እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል አንተም ሰኮናውን ትነክሳለህ :: >> ( ዘፍ ፫፥፲፭ ) ሲል የተናገረው ይህ ተስፋ ትንቢት መፍቀሬ ስብእ የሆነው አምላክ ለሰው ልጆች ያለውን አምላካዊ የአድኅኖት ዕቅድና በጎ ፈቃድ የሚገልጥ መሪ የተስፋ ቃል ነው :: #በመሆኑም ይህ አምላካዊ ተስፋ ትንቢት በምክረ ከይሲ ተታለው በኃጢአት ተሰናክለው በመንጸፈ ደይን ወድቀው በእግረ አጋንንት ይጠቀጠቁ ለነበሩት ለአባታችን አዳምና ለእናታችን ሔዋን እንዲሁም ለልጆቻቸው ሁሉ የተሰጠ የመጀመሪያ አምላካዊ የድህነት ተስፋ ነው :: ስለሆነም መጽሐፍ <<ተፈጸመ ተስፋ አበው በማርያም ድንግል ወበቀራዮ ተተክለ መድኃኒት መስቀል ፤ የቅዱሳን አበው ተስፋ ድኅነት በቅድስት ድንግል ማርያም ተፈጸመ : የድኅነተ ዓለም ሥራ የተፈጸመበት መድኃኒት መስቀልም በቀራንዮ ተተከለ >> እንዳለው ወላዲተ አምላክ የዚህ ቃለ ትንቢት ፍጻሜ መሠረት መሆኑዋን የመለክቱዋል :: ከላይ የተጠቀሰው ምስጢረ ድኅነተ አለም ፣ቃለ ትንቢት ለጊዜው በቀዳሚነት ሔዋንና በጥንተ ጠላታችን በዲያቢሎስ መካከል ያለውን ጸብና ክርክር የሚያሳይ ሲሆን ፍጻሜ ምሥጢሩ ግን በዳግሚተ ሔዋን (አዲሲቱዋ ሔዋን ) በወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያምና ምክንያተ ስህተት በሆነው በሰይጣን መካከል የሚኖረውን ጠላትነት የሚገልጥ ነው :: (ራእ፲፪፥፩-፲፯) ከዚህም ሌላ የሴቲቱ (የድንግል ማርያም ) ዘር በሆነው በአምላካችን በመድኃኒታችን በፈጣሪያችን በኢየሱስ ክርስቶስና በሠራዊተ አጋንንት መካከል የሚኖረውን ጠላትነትም ያስረዳል :: ይህም ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት <<አንተም የዘንዶውን ራሶች ቀጠቀጥህ >> (መዝ ፸፫፥፲፬) ባለው መሠረት የድንግል ማርያም ልጅ መድኅነ ዓለም ክርስቶስ ጥንተ ጠላታችን የሆነውን የዲያቢሎስን ራስ በመስቀል ላይ ቀጥቅጧል :: በአንጻሩ ደግሞ << እጆቼንና እግሮቼን ቸነከሩኝ >>(መዝ ፳፩፥፲፮)ተብሎ እንደተጻፈ ጠላት ዲያቢሎስ በአይሁድ ልቡና አድሮ የአምላካችን የመድኃኒታችን የፈጣሪያችንን ቅዱሳት እግሮች በቀኖት አስቸንክሯል (ዮሐ ፲፱፥፳፫):: ታላቁ ሐዋርያ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስም ይህንን ድንቅ ምስጢረ ድኅነት አስመልክቶ ሲናገር <<ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ እግዚአብሔር ልጁን ላከ ከሴትም ተወለደ :: እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ ከሕግ በታች ያሉትን ይዋጅ ዘንድ >> (ገላ፬፥፬-፭) በማለት መስክሯል :: በዚህም ሐዋርያዊ ቃል መሠረት ከላይ የገለጽነው የድኅነተ ዓለም ተስፋ በቅድስት ድንግል ማርያም እንደተፈጸመ ልብ ይሏል :: ዳግመኛም በቅዱስ ወንጌል እንደተጻፈው አምላካችን ጌታችን መድኃኒታችን ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያምን የመጀመሪያውን ተአምር ባደረገበት በገሊላ ቃና ሠርግ ቤት በ(ዮሐ፪፥፬ 4) እንዲሁም የድኅነተ ዓለም ሥራን በፈጸመበት በቀራንዮ መስቀል ላይ (ዮሐ፲፱፥፳፮) "" አንቺ ሴት "" ሲል መጥራቱ አስቀድሞ ለሰው ልጆች የሰጠው የድህነት ተስፋ በእርዋ በኩል መፈጸሙን በምሥጢር ያጠይቃል :: በቀዳሚት ሔዋንና በዳግሚት ሔዋን በእመቤታችን መካከል ያለውን ምሥጢራዊ ንጽጽር በየዘመኑ የተነሡ የተለያዩ አበው ሊቃውንት መተርጉማን አምልተውና አስፍተው ገልጸዋል :: ይህውም ቀዳሚት ሔዋን ለፈቃደ እግዚአብሔር ባለመታዘዙዋ ምክንያት በመላው የሰው ዘር ላይ መርገምንና ሞትን አምጥታለች :: በአንጻሩ ደግሞ ዳግሚት ሔዋን የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለፈጣሪዋ ፈቃድ በመታመኑዋና በመታዘዙዋ ምክንያት በመርገምና በሞት ጥላ ሥር ወድቆ ለነበረው ዓለም በረከትንና ሕይወትን አስገኝታለች :: ይህንን አስመልክቶ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ሲናገር "" በእንተ ሔዋን ተዐጽወ ኖኅተ ገነት ወበእንተ ማርያም ድንግል ተርኅወ ለነ ዳግመ : በቀዳሚት ሔዋን ምክንያት የገነት ደጃፍ ተዘጋብን ዳግመኛም ስለ ዳግሚት ሔዋን ስለ ድንግል ማርያም ተከፈተልን "" በማለት አስገንባል :: ከዚህም ሌላ ሰፊና ጥልቅ በሆነው የነገረ ማርያም አስተምህሮው የዜና አበው ሊቃውንት "" የነገረ ማርያም አባት "" እያሉ የሚጠሩት ታላቁ የቤተክርስቲያን ሊቅ ቅዱስ ሔኔሬዎስ ከላይ የገለጥነውን ኃይለ ቃል መሠረት በማድረግ እመቤታችን "" የሔዋን ጠበቃ አለኝታ "" ብሏታል :: በዜና አበው ክፍለ ትምህርት እንደሚታወቀው ይህ አባት የነበረበት ዘመን "" የነገረ ማርያም ዘመነ ልደት "" በመባል ይታወቃል ::
#እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለነገር ድኅነት መሠረት መሆኗን በመግለጥ የተአምሯ መጽሐፍ "" እግዝእትነ ማርያም ነበረት እምቅድመ ዓለም በኅሊና አምላክ "" ይላል :: ከዚህም ኃይለ ቃል ድኅነተ ሰብእ የሆነው እግዚአብሔር አምላክ አስቀድሞ የፈቀደውና ያሰበው የቸርነቱና የመግቦቱ ሥራ መሆኑን እንረዳለን : እንገነዘባለን :: ከዚህም ጋር ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ "" ወበእንተ ዝንቱ አስተርእየ ወልደ እግዚአብሔር ከመ ይስዐር ግብሮ ለጋኔን : ስለዚህ የዲያቢሎስን ሥራ እንዲያፈርስ የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ "" (፩ኛ ዮሐ ፫፥፰) እንደመሰከረው ጥንተ ጠላታችን የሆነው ዳያቢሎስ በሥጋ ከይሲ ተሠውሮ አዳምንና ሔዋንን እንዳሳተ (ዘፍ ፫፥ ፩-፲፬) አካላዊ ቃል አምላካችን ፈጣሪያችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ ብእሲ ተሠውሮ ወደ ቀደመው ጸግና ክብር መልሷቸዋል :: ይህንን ምስጢር ሊቃውንተ ቤተክርስቲና አሞንዮስና አውሳብዮስ በመቅደመ ወንጌል ሲገልጡ "" ወበከመ ተኃብእ ሰይጣን በጉሕሎቱ ውስተ ሥጋ ከይሲ ከማሁ ኮነ ድኅነትነ በሠውሮተ ቃለ እግዚአብሔር በዘመድነ :ሰይጣን በሥጋ ከይሲ ተሰውሮ አዳምን እንዳሳተው ጌታችን መድኃኒታችን ፈጣሪያችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም በስጋ ብእሲ ተሰውሮ መጥቶ ዓለምን አዳነ "" በማለት ተናግረዋል :: በዚህም ትርጉዋሜ ምስጢር መሠረት የሰው ልጅ በምክረ ከይሲ ተታሎ ሕገ እግዚአብሔርን አፈረሰ በሀጢያቱም ምክንያት ከፈጣሪው አንድነት ተለየ ሲባል በአካለ ተደልሎ በልሳነ ከይሲ ተታሎ መሳቱን መናገር ነው :: ስለሆነም ጥንተ ጠላታችን ዲያቢሎስ አካለ ከይሲን መሰወሪያ ልሳነ ከይሲን መናገሪያ አድርጎ በማሳቱ በማኅደሩ ኃዳሪውን መናገሩ እንጂ ለሰው ልጅ ስሕተት ምንጩና መሠረቱ ራሱ ዲያቢሎስ መሆኑን መረዳት ያሻል ::
#ቤዛዊት ዓለም ድንግል ማርያም በዘመነ ብሉይ በተለአየ ኅብረ አምሳል መገለጧና በብዙ ዓይነት ኅብረ ትንቢት መነገሯም በነገረ ድኅነት ውስጥ ያላትን ሰፊ ድርሻ በጥልቀት ያስረዳል :: በዚህም መሠረት የነገረ ማርያም ትምህርት ከነገረ ድኅነት ትምህርት ጋር የተያያዘ ጥልቅ ምሥጢር እንዳለው ልብ ይሏል :: የመጋቤ ሐዲስ የቅዱስ ገብርኤል ዜና ብሥራትና የእመቤታችን ተአምኖና ተአዛዚተ እግዚአብሔር መሆን የመሲሕ ክርስቶስን ወደዚህ ዓለም መምጣትና የአዲስ ኪዳንን መጀመር ያበሥራል :: በአጠቃላይ ይህንን ታላቅና ድንቅ ምስጢር በተመለከት አራቱ ወንጌላውያን ይልቁንም ደግሞ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ የእመቤታችንን ሁለንተናዊ ሕይወት በመግለጥ በልዑል እግዚአብሕሄር ፊት ያላትን ክብርና የባለሟልነት ሞገስ እንዲሁም ከመልአከ ብሥራቷ ከቅዱስ ገብርኤል ጋር ያደረገችውን ቃለ ምልልስ በሰፊው ተናግሮላታል ::
#በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የነገረ ማርያም አስተምህሮ አምላካዊ የድኅነት ዓለም ጉዞ በማህጸነ ድንግል እንዲጀምር ምክያትና መሠረት የሆነው የመልአከ ሰላም የቅዱስ ገብርኤል ዜና ብሥራት አስቀድሞ የሰው ልጆች በኃጢያት የወደቁበትን መርገምና ሞት ወደ ዓለም የገባበትን የመልአክ ጽልመት የዲያቢሎስን ተንኮል የሻረና ክፉ ምክሩንም ያፈረሰ የበረከትና የሕይወት መንገድ ነው :: በመሆኑም በእመቤታችን በድንግል ማርያም አማካይነት የተፈጸመው የሥጋዌ ምሥጢር መፍቀሬ ሰብእ የሆነው ቸሩ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያለውን ጥልቅ ፍቅር የገለጠበት ታላቅ የድኅነት ምሥጢር ነው :: በቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጸው የመጀመሪያዪቱ ሔዋን በምክረ ከይሲ ተታልላ የጠላት ዲያቢሎስን ክፉ ምክር ሰምታ በመቀበሏ ምክንያት ለሰው ልጆች ድቀት (ውድቀት ) እንዲሁም የሞት ፍርድ ምክያት ሆናለች ( ዘፍ ፫ ፥፬-፮) :: በአንጻሩ ደግሞ ዳግሚት ሔዋን የተባለችው ቅድስት ድንግል እመቤታችን በልዑል እግዚአብሔር ፊት በባለሟልነት የሚቆመውን መልአከ ሰላም ቅዱስ ገብርኤልን ቃለ ብስራት ሰምታ "" ይኩነኒ በከመ ትቤለኒ : እንደቃልህ ይሁንልኝ ይደረግልኝ "" ብላ በእምነት በመቀበሏ ምክንያት ድኅነት ሆነችን :: ይህን ቃሏን ምክንያት አድርጎም አካላዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድ ከሥጋዋ ሥጋ :ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ በማኅጸኗ አደረ :: በመሆኑም ቀዳሚት ሔዋንን ምክንያተ ስሕተት : ምክንያተ ሞት በመሆኗ ሲወቅሳትና ሲከሳት የነበረው የሰው ዘር በሙሉ ምክንያተ "" ድኅነት ምክንያተ በረከት ወሕይወት የሆነች ዳግሚት ሔዋን እመቤታችንን << ብፅዕት አንቲ እንተ ተአምኒ ከመ ይከውን ቃል ዘነገሩኪ እምኅበ እግዚአብሔር ፤ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልከው ከእግዚአብሔር ዘንድ አግኝተው የነገሩሽ ቃል እንዲፈጸም የምታምኚ አንቺ በእውነት ብጸዕት ነሽ ንዕድ ክብርት ነሽ >>(ሉቃ ፩፥ ፳፰-፴፰) እያለ የሚያመሰግናት ሆኗል :: ከላይ እንደተገለጠው ወላዲተ አምላክ የቅዱስ ገብርኤልን ዜና ብሥራት ሰምታ በማመኗ ምክንያት መድኅነ ዓለም ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም ስለመጣ ብሥራተ መልአክ የብሉይ ኪዳን አምሳልና ትንቢት ፍጻሜ ወይም መደምደሚያ ሆነ :: ይህንን ታላቅና ድንቅ ሚስጢር አስመልክቶ የቤተክርስቲያናችን የነገረ ማርያም መጽሐፍ ሲናገር "" ወቅዱስ ገብርኤል በቃለ ብሥራቱ ኅተመ ትንቢትዮሙ ለነቢያት :: ገብርኤል ውእቱ ዘአፈልፈለ ስቴ ፍሥሐ ለኩሉ ዓለም ወአብጠለ እማልባበ ሰብእ ኩሉ ስቴ ኃዘን መሪር ዘየአኪ እምሕምዘ አፍሀት ዘይቀትል "" ይላል :: ይህም ማለት "" ቅዱስ ገብርኤልም በምሥራቹ ቃል የቅዱሳን ነቢያትን ትንቢት አተመ :አጸና : ፈጸመ : ዘጋ : አረጋገጠ :: ለዓለም ሁሉ የደስታ መጠጥና ምንጭን ያፈለቀ : ያስገኘ : ያመነጨ : ገዳይ ከሆነ የእባብ (የአውሬ ) መርዝም የሚከፋ መራራ የኃዘን ውኃን (መጠጥን :ምንጭን ) ከሰው ሁሉ ልቡና ያስወገደ ያራቀ ይህ ቅዱስ ገብርኤል ነው "" ማለት ነው :: በዚህም መሠረት ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ የጻፈው የነገረ ብሥራት ምሥጢር ለኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን የንገረ ሥጋዌ ትምህርት ምንጭ ለሆነው የነገረ ማርያም ትምህርት ዐቢይ መሠረት ጥሏል :: ከዚህ በተጨማሪም ብሥራተ መልአክ የሰው ልጆችን አስከፊ የኃጢያትና የመርገም ታሪክ የቀየረ ታላቅ ክስተት በመሆኑ ለቤተክርስቲያናችን ጥልቅ የነገረ ድኅነት አስተምህሮ በቂ ማስረጃና ምስክር ነው :: እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለመልአኩ ዜና ብስራት በሰጠችው ቃለ ተአምንሮ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር ከጥንት ያሰበውና የፈቀደው ያድህነተ ዓለም ሥራ እንዲፈጸምና አማናዊ እንዲሆን አድርጋለች :: ይህም ወላዲተ አምላክ በነገረ ድኅነት ውስጥ ያላትን ታላቅ ሱታፌ በጉልህ ያሳያል :: ይህንን ምሥጢር በተመለከተ ኢትዮጵያዊው ሊቅ በድርሰቱ "" ዘበቃለ ጉሕሎቱ ለሰይጣን መልአክ ስሕተት ተሰፍሐ ግላ ጽልመት ውስተ ኩሉ ዓለም :ወበቃለ ብሥራቱ ለገብርኤል መልአክ ጽድቅ ተሰፍሐ ብርሀነ ሕይወት ውስተ ኩሉ ዓለም : የስሕተት አለቃ በሆነው በሰይጣን የክፋትና የጥፋት ቃል ምክንያት የጨለማ መጋረጃ በዓለም ሁሉ እንደተዘረጋ : የእውነት መልአክ በሆነው በቅዱስ ገብርኤል የምሥራች ቃል ደግሞ የሕይወት ብርሀን በዓለም ሁሉ ተዘረጋ በማለት መስክሯል :: ኢትዮጵያዊው የዜማ ሊቅ ቅዱስ ያሬድም እመቤታችን በነገረ ድህነት ውስጥ ያላትን ልዩ ሥፍራ ሲናገር "" በእንተ ተሠግዎቱ ለወልደ አምላክ እምኔኪ ቀሩባነ ኮነ እምድር ውስተ አርያም :ብኪ ወበከመ ወልድኪ "" ብሏል :: የዚህ ኃይለ ቃል ትርጉዋሜ ምሥጢርም ቃለ እግዚአብሔር ወልድ ከሥጋሽ ሥጋ :ከነፍሥሽ ነፍስን ነሥቶ ካንቺ ሰው በመሆኑ ከምድር ወደ ሰማይ :ከሞት ወደ ሕይወት : ከመርገም ወደ በረከት : ከኃሳር ወደ ክብር : ከሲኦል ወደ ገነት የተሸጋገርንብሽ ማለት ነው :: ከላይ የተጠቀሰውን በቃዲምት ሔዋንና በዳግሚተ ሔዋን መካከል ያለውን ምሥጢራዊ ንጽጽር አስመልክቶ
'' ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ ""በመባል የሚታወቀው ሊቁ ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ሲገልጽ "" ለእመ ኃሠሥላ ለሔዋን ትረክባ በህየ እንዘ ትትፌሣሕ በወለታ ዘእምጽአት ፈውሰ ለቁስሊሀ : ለእመ ኃሠሦኮ ለአዳም ረክቦ በህየ እንዘ ይትፌሣሕ ወይገብር በዓለ ምስለ ዳግማዊ አዳም "" በማለት በንጽጽሩ ውስጥ ያለውን ጥልቅና ረቂቅ ምሥጢረ ድህነት አስተምሯል :: እንደ ሊቁ አገላለጽ ዳግሚት ሔዋን የተባለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ፍሬ ሕይወት ወመድኃኒት የሆነው ጌታ የተገኘባት አማናዊት ዕጸ ሕይወት በመሆኗ የዕጸ በለስን ፍሬ በልታ ሞትን ላመጣችብን ለቀዳሚቷ ሔዋን ካሣ ናት :: ምክንያቱም ከዳግሚት ሔዋን ከድንግል ማርያም የተወለደው የማኅጸኗ ፍሬ ጌታችን መድኃኒታችን አምላካችን ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሚያርቅ :በረከተ ሥጋ :በረከተ ነፍስን የሚያድል ሕይወተ ሥጋን ሕይወተ ነፍስን የሚሰጥ : ቀዳሴ ሥጋ ወነፍስ ወመንፈስ የሆነ ቡሩክ አምላክ ነውና ::
ወስብሀት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን ::


ሐኪሙ ወንጌላዊ(ቅዱስ ሉቃስ)

================
ሐኪሙ ወንጌላዊ በማለት ሊቃውንት የሚጠሩት ቅዱስ ሉቃስ ነው። ቅዱስ ሉቃስ ሀገሩ አንጾኪያ ነው፡፡ አስቀድሞ ከ፸፪/72ቱ አርድእት ወገን የተቆጠረ ሲሆን ከበዓለ ሃምሳ በኋላ ወደ አንጾኪያ ወርዶ ወንጌልን ሰብኳል ከሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎሰ ጋር የተገናኘውም በዚሁ ነው፡፡ ቅዱስ ሉቃስ የሕክምና ሙያ የነበረው ሲሆን ያጠናውም ከአቴናና እስክንድርያ ሊቃውንት መሆኑ ታውቋል፡፡ ከዚህ ሙያው በተጨማሪ የሥነ-ሥዕል ችሎታም እንደነበረው ይነገራል፡፡ይህንን ችሎታውንም በወንጌሉና በሐዋርያት ሥራ መጽሐፉ ላይ ባለው ሥዕላዊ አገላለጥ ከማንጸባረቁም ሌላ በእጁ የተሳሉ ሥዕሎች በተለያዩ ሀገሮች ይገኛሉ፡፡
የቅዱስ ሉቃስ ስዕሎች እመቤታችን ልጇን አቅፋ ( ምስለ ፍቁር ወልዳ) የሳላቸው ሲሆኑ በኢትዮጵያ በተድባ በማርያም ፤ በደብረ ዘመዶ ፤ በዋሸራ ፤በጅበላ ሲገኙ ተመሳሳዩም በስፔን ቅድስት ማርያም ካቴድራል እንደሚገኝ ይነገራል ፡፡
ቅዱስ ሉቃሰ የድንግልና ሕይወት የነበረው ወንጌላዊ ነው፡፡ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በሰማዕትነት እስካረፈበት ጊዜ ድረስ ደቀ መዝሙር በመሆን አገልግሎታል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በ67 ዓ.ም. በሮማ በሰማዕትነት ሲያርፍ ሉቃስ ወደ ድልማጥያ መጣ፡፡ በዚያም በሽምግልና ዘመኑ ወንጌልን በመስበክ ላይ እያለ አይሁድና ካህናተ ጣዖት ተባብረው ትምህርቱን በመቃወም ተነሡበት፡፡ መስከረም 20 ቀን 68 ዓ.ም. አይሁድና አረማውያን ጉባዔ አድርገው ነገር በመሥራት ለሮም ንጉሥ ከሰሱት፡፡ በዚያን ዘመን ኔሮን እብደቱ ያየለበት ጊዜ በመሆኑ የቅዱስ ሉቃስን ከሮሜ ማምለጥና ወደ ድልማጥያ መምጣት ሲሰማ 200 ወታደሮችን ላከበት ቅዱስ ሉቃስም የሰዎችን መምጣት በመንፈስ ቅዱስ ተረድቶ ያሰተምራቸው የነበሩትን ምእመናን ወደየቤታቸው ላከና በድልማጥያ አጠገብ
ወደሚገኘው ባሕር ተጠጋ፡፡
በባሕሩ አጠገብ አንድ ዓሣ አስጋሪ ቆሟል፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ወደ ዓሣ አስጋሪው ቀረበና ጨዋታ ጀመሩ፡፡ ቀስ በቀስም ወንጌል ይሰብክለት ጀመር፡፡ ዓሣ አስጋሪውም ቅዱስ ሉቃሰ የሚነግረውን ሁሉ ሥራውን አቁሞ በደስታ ያዳምጠው ነበር፡፡ በመጨረሻ እንካ እነዚህ የሕወትን መገንድ ይመሩሃል አለና የያዛቸውን መጻሕፍት ሁሉ ሰጠው፡፡ ያም ዓሣ አስጋሪ እጅግ ተደስቶ ዕቃ በሚያስቀምጥበት ቦታ በክብር አኖራቸው፡፡
ቅዱስ ሉቃሰ መጽሐፉን ሰጥቶት ዘወር ሲል የኔሮን ወታደሮች ተረባረቡና ያዙት፡፡ ከዚያም ወደሮም ተወሰደና የኔሮን ፍርድ ቤት ቀረበ፡፡ ጥቅምት 22 ቀን አንገቱን ተሠይፎ በአሸዋ በተሞላ ከረጢት አስገብተው በተወለደ በ84 ዓመቱ ወደ ባሕር ወረወሩት፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍቱን ግን ያ ዓሣ አስጋሪ ለዚህ ትውልድ አትርፏቸዋል፡፡
የቅዱስ ሉቃስ ወንጌል ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃሰ በዓይኑ የተመለከተውን ከሐዋርያትም የሰማውን ጠንቅቆ በማሰብ 24 ምዕራፍ፣1149 ቁጥሮች የያዘ ወንጌል አበርክቶልናል፡፡ ወንጌሉን የጻፈው ከ58-60 ዓ.ም. ባው ጊዜ ውስጥ ቅዱስ ጳውሎስ በእሥር ላይ ባገኘው ዕረፍት መሆኑ ይነገራል፡፡ ወንጌሉ የተጻፈው በግሪክ ቋንቋ ነው።
የሐዋርያት ሥራ የሐዋርያት ሥራን የጻፈው ቅዱስ ሉቃስ ነው፡፡ ቅዱስ ሉቃስ በወንጌሉ ከ1-34 ዓ.ም. ያለውን የክርስትና ታሪክ ካሰፈረ በኋላ ቀጣዩንና ከ34-58 ዓ.ም. ያለውን ደግሞ
በሐዋርያት ሥራ መጽሐፉ ላይ ጽፏል፡፡
ከምዕራፍ 1-8 ያለው የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ በኢየሩሳሌም የሚያሳይ ሲሆን ከምዕራፍ 9-12 ያለው ታሪክ ደግሞ በእስጢፋኖስ ሰማኝትነት በተነሣው ስደት የተበተኑት የኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን ልጆች በአካባቢው ያደረጉትን ሐዋርያዊ ጉዞ የሚያሳይ ነው፡፡ ከምዕራፍ 13
ጀምሮ እስከ ፍጻሜው ደግሞ የቅዱስ ጳውሎስን ጉዞዎች ተከትሎ የጻፈውና ክርስተና በታናሿ እኪያር በአውሮፓ እንዴት እንደተሰበከ የሚያሳየው ክፍል ነው፡፡ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በመጀመሪያው የሮም እሥራቱ በቁም እሥር ላይ ሆኖ ወንጌልን እንዲሰብክ ተፈቅዶለት በነበረ ሰዓት በሮም ከሚኖሩ አይሁድ ጋር በ58 ዓ.ም ስለሃይማኖት ያደረገውን ውይይት ተርኮ ያጠናቅቃል፡፡ ወንጌላዊው ሉቃስ የሐዋርያት ሥራን የጻፈው በ58/በ59 ዓ.ም/ ነው፡፡
ጥቅምት ፳፪ ቀን የበዓሉ መታሰቢያ ነው።
የቅዱሱ በረከት በእጥፍ ይደርብን።


 አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን

አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን በ330 ዓ.ም በሐዋርያው ቅዱስ አትናቴዎስ እጅ ጵጵስና የተሾሙበት ዕለት ነው፡፡ ይኸውም ቅዱስ ጌታችን ‹‹ኢትዮጵያን ከጨለማ አውጥተህ በሃይማኖት ስለ አበራሃት ከፍ ያሉ ክብራትንና ማዕረጋትን ፈጽሜ ሰጠሁህ›› በማለት ታላቅ ቃልኪዳን የሰጣቸው እጅግ የከበሩ ነገር ግን ቤተ ክርስቲያናችን እንደሚገባቸው መጠን ያላከበረቻቸው የመጀመሪያው አባታችን ናቸው፡፡

አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን፡- ቅዱስ አባታችን አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በኋላ በ245 ዓ.ም በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ህዳር 26 ቀን ሲወለዱ ታላቅ ብርሃን ከሰማይ ወርዶ ለ7 ቀናት አብርቷል፡፡ ቅዱሳን መላእክትም ወደ ምድር ወርደው በመወለዳቸው ታላቅ ደስታን አድርገዋል፡፡ በተወለዱም ጊዜ ‹‹ለአብ ስግለት ለወልድ ስግደት ለመንፈስ ቅዱስ ስግደት ይገባል፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን ለአወጡኝ ቅድመ ዓለም ለነበሩ ዛሬም ላሉ ዓለምን አሳልፈው ለሚኖሩ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል ብለው ዳግመኛም አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ›› ብለው ፈጣሪያቸውን በአንድነት በሦስትነት አመስግነዋል፡፡
ቅዱስ አባታችን በሌላኛው ስማቸው ፍሬምናጦስ እየተባሉ ይጠራሉ፡፡ በ40 ቀናቸው ጌታ በተጠመቀበት በዮርዳኖስ ያጠመቋቸውና ስመ ክርስትና የሰጧቸው ሊቀ ጳጳስ ‹‹ይህ ሕፃን ለኢትዮጵያውን ሁሉ ብርሃን ይሆንላቸዋል›› በማለት ትንቢት ተናግረዋል፡፡ በሊቀ ጳጳሱ በቅዱስ አትናቴዎስ በሚገባ ተምረው ካደጉ በኋላ በ257 ዓ.ም ከኢየሩሳሌም ወደ ኢትዮጵያ ስሙ ሜርጵዮስ ከሚባል ከአንድ ነጋዴ ጋር መጡ፡፡ ከእነሱም ጋር አድስዮስ የሚባል ልጅ ነበር፡፡ ወደ ሀገራችንም ሊመጡ የቻሉት እንዴት ነው? ቢሉ መጀመሪያ ለሰባት ወር በአንድ ሌላ አገር ኖረው ወደ ኢየሩሳሌም ሊመለሱ ሲሉ የበረሃ ሽፍቶች ሜርጵዮስንና ሌሎች መንገደኞችን ገደሏቸውና ሁለቱን ልጆች ማርከው ወስደው ስሙ አልአሜዳ ለሚባል ለአክሱም ንጉሥ ሰጡት፡፡ እርሱም አድስዮስን የቤተክርስቲያን የአልባሳትና የዕቃ ቤት ጠባቂ አድርጎ ሲሾመው ፍሬምናጦስን ደግሞ የቤተክርስቲያንና የሕግ ጠባቂ አደረገው የቤተክርስቲያንን ሥርዓቷንና አገልግሎቷን ጠንቅቆ ያውቅ ነበርና፡፡
በአክሱምም በተጋድሎና በትጋት ኖረ፡፡ ቅዳሜና እሁድ የዛፍ ቅጠሎችን ከመመገብ በቀር ሌላ ምግብ አይቀምስም ነበር፡፡ በየቀኑም አምስት ሺህ ስግደትን ይሰግድ ነበር፡፡ በእርሱም የተጋድሎ ዘመን ደጋግ የሆኑ ነገሥታት አብርሃና አጽብሓ ነገሡ፡፡ እነርሱም ሆኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍሬምናጦስን በጣም ይወዱት ነበር፡፡ አንድ ቀን ፍሬምናጦስ የአክሱሙን ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ሚናስን ‹‹ግዝረትና እምነት በእናንተ ዘንድ አለ ነገር ግን ጥምቀትና ሥጋ ወደሙ መቀበል በእናንተ ዘንድ የለም›› አለው፡፡ ቅዱስ ሚናስም ‹‹ግዝረትንስ አባቶቻችን ሌዋውያን አመጡ፣ በክርስቶስ ማመንን ሕንኬ የተባለች የኢትዮጵያ ንግሥት ጃንደረባ አመጣልን፡፡ ስለ ጥምቀትና ሥጋ ወደሙ ሐዋርያ ወደ እኛ አልተላከም ነገር ግን ያልከውን ሁሉ የሚያደርግልን የሚባርከንና የሚቀድሰን ጳጳስን ታመጣልን ዘንድ ሊቀ ጳጳሱ ወዳለበት ወደ እስክንድሪያ አገር አንተ ሂድ›› አለው፡፡ ጥምቀትስ በጃንደረባው በኩል አገራችን ገብቶ ነበር ነገር ግን ገና ስላልተጠናከና ብዙ ሕዝብም አልተጠመቀም ነበርና አባታችን ፍሬምናጦስ አጠናክሮ ያልተጠመቀውን ሁሉ አጥምቆአል፡፡
ፍሬምናጦስም ወደ እስክንድሪያ ለመሄድ አስቦ ሳለ እንደተኛ ድንግል ማርያም ተገልጣለት ‹‹ዲቁናና ቅስናን መቀበል ይገባሃል፣ ለጵጵስና ተዘጋጅ፣ እግዚአብሔር ይህችን ከፍ ያለችውን ማዕረግ ሰጥተሃልና የልጄ ወዳጅ ሆይ በጸሎትህና በልመናህ በስብከትህም የኢትዮጵያ ሰዎች ሁሉ ይድናሉ፣ በእጅህ ጥምቀትንና ሥጋ ወደሙን ይቀበላሉ›› አለችው፡፡ ጌታችንም እንዲሁ ተገልጦለት ‹‹ወደ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አትናቴዎስ ሄደህ ከፍ ያችውን ማዕረግ ተቀብለህ የኢትዮጵያን ሰዎች አጥምቅልኝ፣ ነቢዩ ዳዊት ስለ እነርሱ ‹ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች› ብሎ ተናግሯልና›› አለው፡፡ እርሱም ቅዱሳኑን ነገሥታት አብርሃንና አጽብሓን አግኝቶ ከእነርሱም ጋር ተማክሮ ወደ እስክንድሪያ ሄዶ በቅዱስ አትናቴዎስ እጅ በአገራችን ላይ ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ታኅሳስ 18 ቀን ተሾመ፡፡ ስሙንም ሰላማ ከሣቴ ብርሃን አለው፡፡ ሰላማ ማለት እግዚአብሔርንና ሰውን የሚያስታርቅ ማለት ነው፡፡ ከሣቴ ብርሃን ማለትም ሃይማኖትን ገልጦ የሚያስተምር ማለት ነው፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስም ከሾመው በኋላ ታቦትና በጣም ብዙ ንዋያተ ቅድሳትንና መገልገያ ዕቃዎችን ሰጥቶ መርቆ በሰላም ወደ ኢትዮጵያ ላከው፡፡
ቅዱሳን የሚሆኑ ሁለቱ ነገሥታትም መምጣቱን በሰሙ ጊዜ ‹‹ኢትዮጵያ ሰዎች ሁላችሁ እስከ 40 ቀን ተሰብሰቡ›› ብለው አዋጅ አስነገሩ፡፡ በደብረ ሲናም ሄደው ተገኛኙትና ከዚያች ቀን ጀምሮ ሕዝቡም ሁሉ እስከ 40 ቀን ድረስ ተጠመቁ፡፡ በዚያችም ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያች በደብረ ሲና አገር ላይ ወረደና ሕዝቡን ሁሉ ባረኮ ተመልሶ ሲያርግ ከአባ ሰላማ በቀር ያየው አልነበረም፡፡ ወደ አክሱምም ሄደው ነገሥታቱም የአድባራት ሁሉ የበላይ የምትሆን የቅድስት ጽዮንን ቤተክርስቲያን በወርቅና በዕንቊ ሠሩና አባ ሰላማ ባርኮ ቀደሳት፡፡ ታቦተ ጽዮንም ከድንኳን ወጥታ ማንም ካህን ሳይሸከማት አብርሃና አጽብሓ ወዳሠሩላት ቤተ መቅደስ ራሷ በመንፈስ ቅዱስ ገብታ ተገኘች፡፡ አባታችንም በእመቤታችንም በዓለ ዕረፍት ቀን ጥር 21 ቀን በውስጧ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲቀድስ ሚካኤልና ገብርኤል በግራ በቀኝ እየተራዱት እርሱም ከምድር ሦስት ክንድ ከፍ ብሎ ሥርዓተ ቅዳሴውን ፈጽሞ ለነገሥታቱና ለሕዝቡም ሁሉ አቆረባቸው፡፡ የዚያን ዕለትም እጅግ ታላቅ በዓልን አደረጉ፡፡
ከዚያም ሌሎችን እየሾመ ወደ ሌላ አገር ካሰማራ በኋላ እርሱም በየሀገሩ በአራቱም አቅጣጫ እየዞረ እያጠመቀና እያስተማረ አብያተ ክርስቲያናትንም እየሠራ ለኢትዮጵያ ሕዝቦች ታላቅ ብርሃን ሆነ፡፡ በየቀኑም እስከ ማታ ድረስ የሚጠመቀው ሕዝብ የሦስት ገበያ ሕዝብ ይሆናል፡፡ በመሸም ጊዜ እንደ ኢያሱ ፀሐይን እያቆመ ሕዝቡን ያጠምቅ ነበር፡፡ መድኃኔዓለምም በየጊዜው በአካል እየተገለጠለት አገልግሎቱን ያፋጥንለት ይባርከውና ቃልኪዳን ይሰጠው ነበር፡፡
አባታችንም በድፍን ኢትዮጵያ በአራቱ አቅጣጫ እየዞረ በተአምራቱ ድውያንን እየፈወሰ፣ ሙታንን እያስነሳ፣ ወንጌልን እያስተማረ፣ እያጠመቀ፣ አብያተ ክርስቲያናትን እየሠራና አገልጋይ የሚሆኑ ቀሳውስትን እየሾመ በሀገራችን ላይ ብርሃንን የፈነጠቀ ለኢትዮጵያ መግለጽ ከሚቻለው በላይ ታላቅ ባለውለታዋ ነው፡፡ ከአባ ሰላማ በፊት እኛ ኢትዮጵያውያን ክርስቶስን ከማመን በቀር ጥምቀትና ሥጋ ወደሙ የመቀበል ልማድ አልነበረንም፡፡ በድንኳን ካለችው ታቦተ ጽዮን በቀርም ታቦታትና አብያተ ክርስቲያናትም አልነበሩንም፡፡ ይሄ ሁሉ ሲታሰብ ከአባ ሰላማ ውለታ አንጻር እንደዋለላት ውለታና እንደሠራላት እጅግ ታላቅ ሥራ ቅድስት ቤተክርስቲያናችን እንደሚገባው መጠን አላከበረችውም ማለት ይቻላል፡፡ ጌታም በመጨረሻ ቃልኪዳን ሲሰጠው ‹‹ስለ ትምህርትህና ስለ ስብከትህ ኢትዮጵያን ከጨለማ አውጥተህ በሃይማኖት ስለ አበራሃት ከፍ ያሉ ክብራትንና ማዕረጋትን ፈጽሜ ሰጠሁህ›› ነው ያለው፡፡ ‹‹ነቢያትና ሐዋርያት ፊቴን አይተው ስለእኔ መረዳት ያቻሉትን አንተ ግን ፊቴን አይተህ ስለ እኔ እንድትረዳ አደረግሁህ፣ ለቅዱሳንም ሁሉ ብርሃናቸው አድርጌሃለሁ›› ተብሎ በጌታችን አንደበት የተነገረለትን ቅዱስ፣ ጻዲቅ፣ መናኝ፣ ሐዋርያ፣ ጳጳስ… ቤተክርስቲያናችን አሁን እያከበረችው ባለው መልኩ ብቻ አልነበረም ማከበርና መዘከር የነበረባት፡፡
በተንቤን ምድር ብቻ በብሕትውናና በጽሙና ሲቀመጥ ቋጥኝ ፈልፍሎ በሠራው ቤተክርስቲያን ላይ የብርሃን መሰላል ተተክሎለት በእርሱም ወደ ሰማይ ወጥቶ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር አጥኗል፡፡ የተንቤንንም ምድር ቡሩካን በሆኑ እጆቹ አንስቶ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ መንበር ፊት አቅርቦ አስባርኳታል፡፡ መልአክም ሰማያዊ መናና ኅብስት እያመጣ ይመግበው ነበር፡፡ ወንጌልንም ካዳረሰ በኋላ በዋሻ ገብቶ በበዓት ተወስኖ ሰውነቱን በመከራ ይቀጣ ነበር፡፡ በጎጃም ክፍለ ሀገር በሞጣ ዓባይ በኩል በምትገኝ ቦታ እያስተማረና ሐዋርያዊ ተልዕኮውን እየተወጣ ሳለ ጊዜው መሽቶ ፀሐይ ልትጠልቅ ስትል እንደ ኢያሱ ገዝቶ ያቆማት ሲሆን ጌታ ግዝቱን እንዲፈታ ከነገረው በኋላ ነው ግትዙን አንስቶላት የጠለቀችው፡፡ በታዘዘውም መሠረት ከጎጃም ወደ ትግራይ ሲሄድ የዓባይን ባሕር በመጠምጠሚያው ለሁለት ክፍሎ ከእርሱም ጋር የነበሩትን አሻግሯቸዋል፡፡ በደመናም ተጭኖ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ሄዶ አይሁድ ቀብረው በደፈኑት በክርስቶስ መስቀል ላይ ጸሎት አድርጎ ሰግዷል፡፡ ከጌታችንና ከእመቤታችንም መካነ መቃብር አፈር ዘግኖ ወደ ሀገራችን በማምጣት በሚያንጻቸው አብያተ ክርስቲያናት ላይ ነስንሶታል፡፡
አባታችን አባ ሰላማ ሐምሌ 26 ቀን ሲያርፍ ነፍሱን መላእክት ያይደሉ ራሱ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ተቀብሎ ከእርሱ ጋር አሳርጓታል፡፡ መላእክትም ሥጋውን ከጌታችንና ከእመቤታችን መቃብር አድርሰው ወደ ደብረ መድኃኒት የመለሱት ሲሆን በመቃብሩም ላይ ብርሃን ወርዶ ለሁሉም ታይቷል፡፡ ነገሥታቱም ከዐረፈ በኋላ ወደ ደብረ መድኃኒት መጥተው ለመካነ መቃብሩ ሲሰግዱ አባ ሰላማም ተገልጦላቸው ከነሠራዊታቸው ባርኳቸዋል፡፡ የሰላማ ከሣቴ ብርሃን በረከታቸው ይደርብን፡፡
ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ይሁን! እኛንም በአማላጅነታቸው የምንታመን የተዋሕዶ ልጆች የሆንን ሁላችንን የአቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃንን ረድኤት በረከታቸውን ያሳድርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡
(ምንጭ፡- ገድለ አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን፣ የመስከረም፣ የግንቦትና የሐምሌ ወር ስንክሳር


 እኔ የምመርጠው ሳይሆን እግዚአብሔር የመረጠው ይሁን

በክርስቶስ የተወደድሽ እህቴ ሆይ መልካም የትዳር ሰው ትፈልጊያለሽ እንግዲያው ሀብትና ገንዘብ ያለው፣ውጫዊ መልኩ ቆንጆ የሆነ ፣ተክለ ስውነቱ ያማረ፣ወይም ሀብታም ፣የተማረ ድልቅቅ አርጎ የሚያኖርሽ አይሁን ምርጫሽ ይልቁንስ እግዚአብሔር ን የሚፈራ ሰውን የሚያከብር ቢሆን ይሻላል።
ምክምያቱም በጥንተ ፍጥረትም ሆነ በሐዲስ ተፈጥሮ ትዳርን የመሠረተ ጋብቻን ያጸና እግዚአብሔር ነው። (ዘፍ2፣18ና ዮሐ2፣1)
ትዳር በሀብት ብዛት የማትወሰን በመልክ ማማር የማትመካ ድንቅ የሕይወት መንገድ የእግዚአብሔር ስጦታ ናት ።
እህቴ ሆይ ! መልኩ ሳይሆን፤ስብእናው ቆንጆ የሆነውን፣ ልብሱ ሳይሆን ልቡ ንፁህ የሆነውን መሻት ነው።
ንፁህ የሆነውን የሕይወት አጋርሽን ከፈለግሽ የምትወጂውን ወንድ ከማንም ጋር አታወዳድሪው። ሃይማኖቱን ያጸና ምግባሩን ያቀና ባል እንዲሆን አስተምሪው።


በትዳርሽ ደስታ እንዲኖርሽ ከፈለግሽ ሕይወትሽን ከማንም ጋር አታወዳድሪው። ባልሽ ማለት የአባትሽ ምትክ ማለት ነው።
ተንከባከቢው እንጂ አትጨቃጨቂው ።ባልሽ የደስታ ምንጭሽ ነው። ከእቅፉ ውስጥ ገብተሽ ሌላ አለም ውስጥ የገባሽ እስኪመስልሽ የሚያስደስትሽ ባልሽ ነው።
ያንቺ ባል ላንች ውብና ቆንጆ ንጉስሽ ነው። አክብሪው በደካማ ጎኑ ገብተሽ አበርችው ኃይል ሁኚው፤ አጠንክሪው።
ከተሳሳተ አስርጂው አርሚው ደስታን ስጪው ፤ብርታት ሁኚው። ያኔ የሕይወት ጣእሙን ታውቂያለሽና።
“ለሁሉም በአምላኩ የሚፀና ወንድ ፈጣሪውን የሚፈራ ትዳሩን ያከብራልና።”
በክርስቶስ የተወደድክ ወንድሜ ሆይ መልክ፣ውጫዊ ውበት ተክለ ሰውነት ትዳር አሆንም፣ ቤትንም አያቆመውም። ወዳጄ ሆይ ልብ በል በጎ ስጦታ ሁሉ ከላይ ከሰማይ ነውና እግዚአብሔርን ደጅ ጥና ተንበርክከህ ጠይቀው። አስተውል ትዳር ማለት የሕይወትን ጣዕም የምታውቅበት የምትደጋገፍበት በሳል የምትሆንበት አባት የምትሆንበት ከብቸኛነት ወጥተህ ሁለተኛ እናት የምታገኛበት፣ ሃሳብህን የምትጋራልህ ፣ መፍትሄ የምትስጥህ የሕይወትህ ማጣፈጫ ደስታን የምትሰጥህ ሴት ከፈለክ መልኳን ሳይሆን ከአስተሳሰቧ፣ ከአለባበሷ ሳይሆን ፈጣሪ ፈሪነቷ ይሁን ምርጫህ።
በክፉው ዘመን ፈጣሪዋን የምትፈራ ሴት ማግኘት መታደል ነውና። መልካም ና እግዚአብሔርን የምትፈራ ሴት የምትፈተነው በክፉው ዘመን ነውና በታመምክ ጊዜ አልጋህን የምታነጥፍልህ ጎንበስ ቀና ብላ የምታስታምምህ፣ በተበሳጨህ ጊዜ የምትታገስህ፣ በሐዘንህ የምታዝን በደስታህ የምትደሰት በመከራህና ገንዘብ በሌለህ ጊዜ በጽናት አብራህ የምትቆይ ባንተ የምትተማመን ፣ተስፋ በቆረጥህ ሰዓት ከጎንህ ሆና የምታጽናናህ እርሷ ከላይ ከእግዚአብሔር የተሰጠች ስጦታ ናት።
ውጫዊ ውበቷን ሳይሆን ለአንተ ያላትን አመለካከት አስብ።
በእርግጥ ውጫዊ ሥነ-ምግባር ለውስጣዊ ማንነት አስተዋጽኦ ይኖረዋልና በዓለም ውስጥ እየኖርን በጥበብ መመላለስ ግድ ይለናል።
ወንድሜ ሆይ ለዘላለም አብሮህ የሚኖረው ንጹህ ልቡናዋና ስብእናዋ ለክርስቶስ ያላት ፍቅር እንጂ መልኳ አይደለም፣ ምክንያቱም እግዚአብሔር ን የምትፈራና ለአምላኳ ልዩ ፍቅር ያላት ሴት ለባሏ በፍቅር ትገዛለች።
ወዳጄ ሆይ ለሕይወትህ ስኬትን ከፈለግህ ዓይንህ ሳይሆን ልብህ ያረፈባትን ሴት አግባ።
ዓይን አዋጅ ነው እንዲሉ አበው ። ዓይን ብዙ ያምረዋልና ልብህን አዳምጥ። ያንተ ሚስት ላንተ ብቻ ቆንጆና ውብ ናት ያንተ ሚስት ላንተ ንግሥት ናት።
ባለቤትህን ከማንም ጋር አታወዳድራት። ራስን ሆኖ መኖር ጥበብ ነው።እንደ ራስ መኖር ብስለት ነው።
ሕይወትህን ከማንም ጋር አታወዳድር ( ትዳርህን) እንደራስህ ሆነህ ከኖርክ ራስህን ከማንም ጋር ሳይሆን ከራስህ ጋር ካወዳደርከው በሕይወትህ ደስተኛ ነው የምትሆነው።
መልክ ትዳር አይሆንም፣ ጎጆን አያቆምም። መጽሐፍ "መልክ ከንቱ ደም ግባትም ከንቱ እግዚአብሔርን የምትፈራ ሴት ግን የምትመሰገን ናት።" (ምሳ 30፤8) ይላልና።


  ቁስቋም

---------

ኀዳር ፮ ቀን እመቤታችን ወደ ግብጽ አገር ተሰዳ ስትመለስ ቁስቋም በምትባል አገር ገብታ ያረፈችበት በዓል ነው፡፡ ከገነት የተሰደደውን አዳም ወደ ገነት ለመመለስ ሲል ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከድንግል ማርያም ከአረጋዊው ዮሴፍና ከሰሎሜ ጋር ወደ ግብጽ ተሰደደ፡፡ ጌታችን ከ፫ ዓመት ከ፮ ወር የግብጽ ስደት በኋላ ወደ እስራኤል እንደሚመለስ አስቀድሞ ነቢየ ልዑል ሆሴዕ በትንቢት መነጽርነት ተመልክቶ “ልጄንም ከግብጽ ጠራሁት ” ብሎ ተናግሯል ሆሴ ፲፩፥፩ በዚህም መሠረት ቅዱስ ዮሴፍ እመቤታችን ከተወዳጅ ልጇ ጋር ይዞ ወደ ገሊላ ተመልሷል ኅዳር ፮ ቀንም ሀገረ ቁስቋም ገብተው አርፈዋል።


መንበረ መንግስት ቁስቋም
ለእግዝአብሔር ካላቸው አክብሮትና ፍርሃት ለቤተ ክርስቲያንና በንግሥና ለሚያስተዳድሩት ህዝብ ካላቸው ፍቅር የተነሣ በህዝቡ “እምዬ” የሚል ስም የተሠጣቸው ንጉሠ ነገሥት አፄ ሚኒሊክ ከባለቤታቸው እቴጌ ጣይቱ ብጡል ጋር ሠራዊታቸውን አስከትለው ከእንጦጦ ቤተ መንግስታቸው ወደ ፍልውሃ እና ወደ ተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ሲንቀሣቀሱ መንበረ ንግስት ቁስቋም ማርያም ቤተ ክርስቲያን በታነፀችበት ሥፍራ ላይ ድንኳናቸውን ተክለው ቆይታ ያደርጉበት ነበር፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን እረፍት ባደረጉበት ሥፍራ እንቅልፍ ሸለብ ያደርጋቸውና አንዲት እጅግ የተዋበች ሴት ልጅ አዝላ በእቴጌ ጣይቱ አማሣል “ይህንን ቦታ ልቀቁልኝ፤ ቤቴን ልስራበት !!” ስትላቸው ያያሉ፡፡ ንጉሡም ከእንቅልፋቸው በመንቃት ያዩትን ሁሉ ለባለቤታቸው ለእቴጌ ጣይቱ ብጡል ይነግሯቸዋል፤ በመቀጠልም በእቴጌ ጣይቱ አምሣል ስለታየቻቸው በስምሽ ሆስፒታል ትሰሪበት ዘንድ ፈቅጄልሻለሁ ብለው ቦታውን ለእቴጌ ጣይቱ ይሰጧቸዋል፤ ከግዜ በኃላ ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒሊክ ስለታመሙ እቴጌ ጣይቱ ባለቤታቸውን ማስታመም ይጀምራሉ፤ አብረዋቸው አባታቸውን ያስታምሙ ለነበሩት ንግሥተ ነገሥት ዘውዲቱ አፄ ምኒሊክ ንጉሡ ያዩትን ራዕይና ሀኪም ቤቱን ለመስራት ያለመቻላቸውን ጭምር ይነግሯቸዋል፡፡ ከጥቂት ዓመታት በኃላ ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒሊክ አርፈው እቴጌ ጣይቱም እንጦጦ በቤተመንግስት ተቀምጠው ከእምዬ ምኒሊክ ጋር ያሣለፉትን ህይወት በማስታወስ አዲስ አበባን ቁልቁል እየተመለከቱ “ነበር እንዲህ ቅርብ ነው ወይ አሉ ይባላል !!” ብዙም ዓመት ሳይቆዩ እቴጌም ባለቤታቸውን ተከትለው አረፉ፡፡
ልጅ ኢያሱ መሪነቱን ይዘው በነበሩበት ሠዓት ከመኳንንቱ፤ መሳፍንቱ እና ሹማምንቱ ጋር በአስተዳደር ባለመግባባታቸው ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ሚኒሊክን ንግሥናቸውን እንዲረከቡ ሲደረግ ራስ ተፈሪ መኰንን አልጋወራሽነትን እንዲረከቡ ተደረገ፡፡ የንግሥና ህይወታቸውን ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ሚኒሊክ በመባል በትረ መንግስታቸውን ከተረከቡ በኃላ እቴጌ ጣይቱ የነገሯቸውን አስታውሰው፤ ዛሬ መንበረ ንግስት ቁስቋም ማርያም ቤተ ክርስቲያን በተተከለችበት ቦታ ላይ ሆስፒታሉን ለመሥራት የመሠረት ቁፋሮ ይጀመራል፡፡ በቁፋሮውም ወቅት አስደናቂ ነገር ይከሠታል፤ ይኽውም “ታቦተ ቁስቋም የሚል ፅሑፍ ያለበት የንግሥት እሌኒ የመዳብ ወንበር እና የብረት መስቀል” ይገኛል፡፡ ንግሥት እሌኒ የአፄ ዘርዓያቆብ እህት ሲሆኑ በ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበሩ ንግሥናቸውም በ1426 ዓ/ም እንደነበረ የኢትዮጵያ ታሪክ ያስረዳናል፡፡ የ492 ዓመት ዕድሜ ያለው ንብረት ከመሬት ተቀብሮ በጥበብ እግዚአብሔር ተጠብቆ ምንም ሳይበላሽ መገኘቱ ድንቅ የእግዝአብሔር ሥራን ያመላክተናል፡፡ በዚህም ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ተደንቀው ንዋየ ቅዱሣቱን መስቀል እና ሌሎቹንም የተገኙትን በታሪከ ነገሥታት በዓታ ለማርያም እንዲቀመጥ ያደርጋሉ፡፡ በቁፋሮው ግዜ በተገኘው ንዋየ ቅዱሣት ምክንያት ሥራው ወደ ተቋረጠው የሆስፒታል ቦታ በመሄድ ቤተክርስቲያን ይሠራ ዘንድ ሕዳር 6 ቀን 1918 ዓ.ም የመሠረት ድንጋይ አስቀመጡ፡፡ መቃኞውም በአስቸኳይ ይሠራ ዘንድ ለራስ ዳምጠው ትዕዛዝ ተሰጠ፡፡
በበጎ ሥራቸውና ካህናትን በመውደዳቸው ምክንያት ዘመነ ካህናት ተብሎ በሚጠራበት ግዜ በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ሚኒሊክ ዘመነ ንግሥና በግብፃዊው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማቴዎስ ፍፃሜ ዘመን በሰሜን አዲስ አባባ ልዩ ስሙ እንጦጦ በተባለ ስፍራ በራስጌ ርዕሰ አድባራት እንጦጦ መንበረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም እና ደብረ ኃይል ቅዱስ ዑራኤል ወቅዱስ ኤልያስ በግርጌ ሀመረ ኖህ ቅድስት ኪዳነ ምህረት እና ቀጨኔ ደብረ ሠላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያንን አዋሣኝ አድርጋ በመሐል ባለ ልዩ ጉብታ (መሶብ) በምትመስል በግማሽ አዲስ አባባን ሊያሣይ በሚችል ቦታ ላይ መቅደስና ቅኔ ማህሌት ያለው መቃኞ ቤተክርስቲያን ሠርተው በትእዛዙ መሠረት አሠርተው ታቦተ ቁስቋም ማርያምንና ታቦተ መድኃኔዓለም እየሱስን ሌሎችንም ንዋየ ቅዱሳት በእጨጌ ተድላና በዓቃቤ ሰዓት መምሬ አበበ ትዕዛዝ በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ሚኒሊክ ካህናትና ዲያቆናት በምዕመናንና ምዕመናት ታጅቦ ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ እና ታላላቅ ሹማምንት በተገኙበት በግብፃዊው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማቴዎስ ባራኪነት ታቦቷ ኅዳር 6 ቀን 1919 ዓ.ም ገባች፡፡ ስያሜዋንም “መንበረ ንግሥት ቁስቋም ማርያም” ብለዋታል፤ የመጀመሪያው አስተዳዳሪም ቄስ ገበዝ ብሥራት ኃ/ማርያም ነበሩ፡፡