Tuesday, February 25, 2014

‹‹ዓብይ ጾም››


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅድስ አሐዱ አምላክ አሜን
‹‹ዓብይ ጾም››
ጾም የቃሉ መሠረታዊ ትርጉም መታቀብ መከልከል ማለት ነው በቤተክርስቲያናችን እምነትና ትምህርት ጾም ማለት የሰው ልጅ ሕይወቱን ለሰጠው የሕይወትን መመሪያ ላዘጋጅለት ፈጣሪ እየታዘዘ ኃጢዓትን ለማስተሰረይ የምኞት ፍትወትን ኃይል አድክሞ ሥጋ ለነባቢት ነፍስ ትገዛለት ዘንድ በሕግ በታወቁ ጊዜያት ከመብል መጠጥ በመከልከልና የመንፈስ ብርታት ማግኛ የጥበብ መንገድ ነው::
ጾም ጸሎት ምጽዋት የተያያዙ የሥነ ምግባር ሰንሰለቶች ስለሆኑ በተግባር ተጠብቀው ሲተረጎሙ የእኛንም ሕይወት ከእግዚአብሔር ጋር ያገናኛሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎ እንደምናነበው አበው ማንኛውንም ሥራ ለመሥራት ሲያስቡና ሲያቅዱ፣ ሲጀምሩና ሲፈጽሙ በጾም በጸሎት ነው፡፡






ሐዋርያው ጳውሎስ ‹‹የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ›› እንዲል (ኤፌ 6፡10) የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር የተባሉ መሣሪያዎች ጾም፣ ጸሎት ፣ ምጽዋት አጠንክሮ የሚጠቀምባቸው ክርስቲያን የችግርን ጊዜ የማለፍ ኃይል ይኖረዋል፡፡
ጸሎት እምነት እንዲለመልም እንዲፋፋ እንዲያፈራ ይረዳል፣ ጾም ደግሞ እምነትን ጸሎትን እያጠናከረ ብዙ ድንቅ ሥራዎች እንዲሰሩ ያደርጋል፡፡
ጾም ነፍስን በእግዚአብሔር ፊት ትሑት ያደርጋል የሥጋን ፈቃድ አስገዝቶ ነፍስ እንድትነፃ እንድትቀደስ አቋሟን እንድታስተካክል ይረዳታል ጾም ለነፍስ ብቻ ሳይሆን በሥጋ ሕይወትም ለሆድ ዕቃዎች (ለሰውነታችን) የውስጥ የምግብ ማዘጋጃ ክፍሎች ዕረፍትን ይሰጣል ጾም ትሑትና ቅን ያደርጋል በሥጋዊ ፍላጎቶቻችን ፈቃዶቻችን ላይ አዛዦች መሆናችንን ያረጋግጥልናል፡፡
ጾም ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ተቃራኒ በሆኑ ርኩሳን መናፍስትና በአጋንንት ላይ ኃይል እንድናገኝ ከፈተናዎች እንድንድን ይረዳል ክህደትን ጥርጥርን ያጠፋል እምነትንና በእምነት የምንሰራቸውን ሥራዎች ያጠናክራል የጥበብን መንገድ የሕይወትን ጎዳና ይገልፃል፡፡
የቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓትና ድንጋጌ (የሕግ ምንጭ) በሆነው ፍትሐ ነገሥት ስለጾም በተመለከተው አንቀጽ እንደተገለጸው ጾም
_ ጾመ ሕግ
_  ጾመ ፈቃድ ተብሎ በሁለት ይከፈላል
ጾመ ሕግ ሃይማኖታቸው የቀና 318ቱ የኒቂያ ጉባኤ ሊቃውንት አበው በወሰኑት መሠረት ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15 ላይ የተመለከቱትና ክርስቲያኖች ሁሉ እንዲጾሟቸው የታዘዙት አፅዋማት ሰባት ሲሆኑ
1.   ዐብይ ጾም
2.   ጾመ ድህንት (ረቡዕና ዓርብ)
3.   ጾመ ነነዌ
4.   የልደትና ጥምቀት (ጋድ/ገሐድ ጾም)
5.   የሐዋርያት (የሰኔ) ጾም
6.   የነቢያት (የገና) ጾም
7.   የፍልሰታ ጾም ናቸው
 

እነዚህ አጽዋማት የየራሳቸው የሆነ ታሪክና ትንታኔ ያላቸው ሲሆኑ ሁሉም ያለ ልዩነት በሁሉም ክርስቲያኖች በይፋ በማህበር እንዲጾሙ የተወሰኑ ናቸው፡፡
ጾመ ፈቃድ በግል ውሳኔ በኀጢዓት ስሜት የሻከረ ኅሊናን ለማጥራት ወይም ቅድስናን ጸጋና የበለጠ መንፈሳዊ ክብር ለማግኘት በመምህረ ንስሐ አማካኝነት አለዚያም ብቻ ለብቻ በሥውር አይቶ በግልፅ የሻቱትን ለሚሰጥ አምላክ የሚቀርብ ነው፡፡
ከሕግ አጽዋማት መካከል በኦርቶዶክስ ተዋህዶ አቢያተ ክርስቲያናት እምነትና ሥርዓት በየአመቱ ከሚመላለሱት አጽዋማት ዋናውና ትልቁ ጾመ ሁዳዴ (አብይ ጾም) ነው፡፡
ይህንን ጾም የምንጾመው ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን  አብነትና አርአያ አድርገን ነው:: አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ከመጀመሩ በፊት በ30 ዘመኑ በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ በኋላ ሳይውል ሳያድር ወደ ገዳመ ቆሮንጦስ በመሄድ ከቆመ ሳይቀመጥ፣ ከዘረጋ ሳያጥፍ እህል ውሃ ሳይቀምስ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾሞ የዚህ ዓለም ተፈታታኝ የሆነ ዲያብሎስን ከነፈተናው ድል ነስቶታል፡፡ በስስት ፣ በትዕቢት፣ በፍቅረ ንዋይ የመጣውን ፈተና አጥፍቶ የኃጢዓትን እሾህ አቃጥሏል፡፡
-    ስስት ያልተሰጡትን መሻት የሌሎችን ድርሻ በይበልጥ ለመሻማት መሞከር
-    ትዕቢት አምላክ እሆናለሁ ማለት በሌሎች ላይ ታላቅነትን፣ የበላይነትን መመኘት
-    ፍቅረ ንዋይ ያለኝ ይበቃኛል አለማለት በተሰጡት አለማመስገን ነው
 

እነዚህ ሦስቱ አርዕስተ ኃጣውዕ ይባላሉ፡፡ እያንዳንዳችን የልቡናችን በር ከፍተን እንደገና ካላስገባናቸው በቀር በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጾም ተወግዷል
ሀ/ ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾመ
1.   እርሱ ሠራዔ ህግ (ህግን የሠራ) ነውና፣ ሕግንና ነቢያትን ያጸና ዘንድ አንድም ሕግን ይሠራ ዘንድ ጾምን የሥራው መጀመሪያ አደረገ
2.   አንድም ለሐዋርያት ለሊቃውንት እንዲሁም ከዚያ በኋላ ለሚነሱት ክርስቲያኖች ሁሉ አርአያና ምሣሌ አብነትም ለመሆን 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሞ ጸልዮ ሥራ ጀምሯል፡፡ ከዚያ በኋላ ቅዱሳን ሐዋርያት ከእርሱ በተማሩት መሠረት የሥራቸው መጀመሪያ ያደረጉት ጾምን ነው፡፡ (ሐዋ 13፡1)
3.   መብል ለኃጢዓት (ለጥንተ አብሶ) መሠረት በመሆኗ በመብል ምክንያት ኃጢዓት ወደ ዓለም መጥቷልና፣ በመብል ምክንያት ወደ ዓለም የገባው ኃጢዓትና ኃጢዓት ያስከተለው ሞት ከሥራቸው ተነቅለው ተደምስሰው፣ የጠፋው የሰው ሕይወት የታደሰው በጌታችን ጾም ነው:: ሰው በሥጋዊ መብልና መጠጥ ብቻ ሰውነቱ የሚያምር በጾም የሚጠወልግ የሚጎዳ እየመሰላቸው ጾምን የሚፈሩት የሚሸሹት ጥቅም እንደማይሰጥ ሰው ሰራሽ ሥርዓት አድርገው የሚመለከቱትም ብዙ ናቸው፡፡ አስተዋዮች ግን ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ቃለ እግዚአብሔር ጭምር እንጂ በእህል ውሃ ብቻ ሊኖር እንደማይችል ጠንቅቀው አውቀው እየጾሙ ይጠቀሙበታል አስፈላጊም በሆነ ቦታና ጊዜ ከማይፈለግ ጮማና ወይን ይልቅ ጥራጥሬ ተመግቦ መውዛት ማማር እንደሚኖር ከሶስቱ ወጣቶች (አናንያ፣ አዛርያና ሚሳኤል) ታሪክ መማር ይቻላል፡፡ (ዳን 1፡8-16)
4.   ምሳሌው ይደርስ ዘንድ (ለጊዜው)
ቀድሞ አባቶቹ ነቢያት አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾመዋል ከዚያ ቢያተርፍ አተረፈ ብለው ቢያጎድል አጎደለ ብለው አይሁድ ደገኛይቱን ሕግ ሕገ-ወንጌል ከመቀበል ይከላከሉ ነበር፡፡
‹‹እኔ ሕግና ነቢያትን ልፈጽም እንጂ ልሽር አልመጣሁም›› ብሏልና (ማቴ 5፡17) ሕግና ሥርዓትን እየፈጸመ ከሕግ በታች ሆኖ ተመላለሰ
ሀ/ ሙሴ በአርባ ዘመኑ ለዕብራዊው ወገኑ አግዞ ግብጻዊውን ገድሎ በአሸዋ ቀብሮታል (ዘጸ 2፡11) ሙሴ የወልድ እግዚአብሔር፣ ዕብራዊው ወገኑ የአዳም ፣ ግብጻዊው የዲያብሎስ፣ አሸዋው የመስቀል ምሳሌ ነው፡፡
ሙሴ ግብጻዊውን ገድሎ በአሸዋ እንደቀበረ ጌታችንም ጾሞ ጸልዮ ዲያብሎስንና ፈተናዎቹን ድል ነስቷል፡፡
ለ/ ሙሴ 40 ዘመን በምድያም ኖሮ እስራኤልን ከግብፅ የባርነት ቀንበር ነፃ አውጥቷል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም እንጂ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሞ ጸልዮ ነፍሳትን ከሲኦል ነጻ ያወጣልና
ሐ/ ሕዝበ እስራኤል የገዳም ምሳሌ በሆነው በቃዴስ በረሃ 40 ዘመን ኖረው ምድረ ርሥት ኢየሩሳሌም ገብተዋል፣ (ዘጸ 14፡19 ፣ 32፡34) እናንተም 40 ቀንና 40 ሌሊት ብትጾሙ ርስት መንግስተ ሰማያትን ትወርሳላችሁ (ዘጸ 16፡4-17)
መ/ ሙሴ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሞ ጸልዮ ለሕይወታችን መመሪያ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፉ አስርቱ ቃላት ያለባቸው ጽላቶች ተቀብሏል፡፡ ሕገ - ኦሪትን ሠርቷል (ዘጸ 34፡28)
ኢየሱስ ክርስቶስም እንጂ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሞ ጸሊዮ ሕገ-ኦሪትን አጽንቶ ደገኛይቱን ሕግ ህገ-ወንጌልን (ስድስቱን ቃላተ ወንጌል) ሠርቷል፡፡
ሠ/ ነቢዩ ኤልያስ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሞ በእሳት ሠረገላ በአውሎ ንፋስ ተነጥቆ ወደ ገነት (ብሔረ ሕያዋን) አርጓል፣ ገብቷል እናንተም 40 ቀንና 40 ሌሊት ብትጾሙ ገነት መንግስተ ሰማያት ትገባላችሁ፡፡ (1ኛ ነገ 19፡8 ፣ 2ኛ ነገ 2፡11)
ረ/ ነቢዩ ሕዝቅኤል በግራ ጎኑ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ተኝቶ ስድስት መቶ ሙታን አስነስቷል እናንተም አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ብትጾሙ ትንሣኤ ዘለ ክብር ትነሣላችሁ ለማለት ፣
ሰ/ ዕዝራ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ከምግብ ተከልክሎ የጥበብ ሕይወት መመሪያ መጻሕፍትን ጽፏል (ዕዝ 7፡6) እነዚያ ቀን ሲጽፉ እየዋሉ ማታ ይመገባሉ እርሱ ግን ቀን ሲያጽፈው የሚውለውን ማታ ሲያስበው ያድር ነበር፡፡
እናንተም 40 ቀንና 40 ሌሊት ብትጾሙ ምሥጢር ይገለጥላችኋል ለማለት፡፡
ሰ/ ነቢዩ ዳንኤል ከሀገሩ ከኢየሩሳሌም በምርኮ በተወሰደበት ሀገር በአንድ አምላክ ላይ ከነበረው ጽኑ እምነት ሳያወላውል በጾም በጸሎት ተወስኖ በመገኘቱ ከአንበሶች አፍ እንደ ዳነ ፣ ሕልምን የመተርጎም ዕውቀት ጥበብ እንደተሰጠው ሀገሩ ኢየሩሳሌም ነጻ የምትሆንበትን ወገኖች እስራኤል ከስደት የሚመለሱበት ከዚህም በላይ ረቂቅና ጠለቅ ያለ የክርስቶስ ሰው የመሆን ምስጢር እንደተገለጸለት በሱባዔው ፍጻሜ መላዕክት ተልከው እንዳረጋጉት የምስራች ዜና እንዳሰሙት ፈተናውን ሁሉ ድል እንዳደረገ (ዳን 9፡2-4 ፣ ዳን 10፡2-14)  
እኛም ጥበብ እውቀት እንዲገለጽልን በሀገርና በወገን ላይ የመጣው መዓትና መከራ እንዲወገድ ነውራችን እንዲከባለል ለኃጢዓታችን ስርየት እንድናገኝ፣ ከነፍሳችን ቁስል እንድንፈወስ ጾምን እንጹም፡፡
 

5.    ጌታችንና አምለካችን ኢየሱስ ክርስቶስ 40 ቀንና 40 ሌሊት የጾመበት ፍጻሜው ግን፡-
ሀ/ አዳም ልጅነት የተሰጠው በ40 ቀኑ ነበር በተፈጠረበት ምድር ኤልዳ በምትባል ቦታ ቆይቶ ገነት ገብቷል፡፡
በ40 ቀን ተሰጥቶት የነበረውን ልጅነት በመብል ምክንያት አጥቶት ስለነበረ
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾሞ ልጅነቱን (ለአዳም) ሊመልስ ፍጹም ካሣ እንደ ካሰ ለማጠየቅ (ኩፋ 4፡9)
ለ/ አንድም ፅንስ ሁሉ በእናቱ ማህፀን በ40ኛው ቀን ተሰዕሎተ መልክዕ ይይዛል (ይፈጸምለታል)
በመሆኑም በ40ኛው ቀን ተስዕሎተ መልክዕ ለተፈጸመለት ክቡር የሰው ዘር ሁሉ ፍጹም ካሳን ሊክስ እንደመጣ ለማጠየቅ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾመ፡፡
ሐ/ በሌላው ሰው የተሰራው ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋና ከአምስተኛ ባሕርያተ ነፍስ በመሆኑ ለአራቱ አስር አስሩን ለመካስ ወይም አራቱ ባሕርያተ ሥጋና አምስተኛ ባሕርያተ ነፍስን አድርጎ ለአምስቱ ስምንት ስምንት ለመካስ እንደመጣ ለማጠየቅ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾመ
                    4x10 = 40 ወይም 5x8= 40
ይቀጥላል…

1 comment:

  1. ሚስተር ቤንጃሚን የኢሜል ዝርዝሮችን እነሆ ፣ Lfdsloans@outlook.com ፡፡ / ወይም ደግሞ ንግዴን ለመጀመር በ 90,000.00 ዩሮ ብድር የረዳኝ WhatsApp + 1-989-394-3740 እና እኔ በጣም አመስጋኝ ነኝ ፣ እዚህ አንድ ነጠላ እናት ነገሮች እንዳላደረጉ መንገድ ለመፍጠር እየሞከርኩ ነው ፡፡ ከእኔ ጋር ቀላል ይሁኑ ግን ንግዴ እየጠነከረ ሲመጣ እና እያሰፋ ሲሄድ እያየሁ በሚስተር ሚስተር እርዳታ ፊቴ ላይ ፈገግታ አሳየኝ ፡፡ የገንዘብ ድጋፍን መፈለግ ወይም በዚያ ንግድ ውስጥ መከራን ማለፍ ወይም የመነሻ የንግድ ሥራ ፕሮጀክት መጀመር መፈለግ ይህንን ማየት እና ከችግራቸው ለመውጣት ተስፋ ሊኖረው ይችላል ... እናመሰግናለን ፡፡

    ReplyDelete