Wednesday, April 23, 2014

‹‹ገና ጨለማ ሳለ ማለዳ ወደ መቃብሩ መጣች›› (ዮሐ ፳፩፣፩)

ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን=>በዓቢይ ሃይል ወሥልጣን
ሮ ለሰይጣን => አግአዞ ለአዳም
ሰላም => እምእዘየሰ
ኮነ => ፍሰሃ ወሰላም።
+ ትረጉም +
--------------------
ክርስቶስ በታላቅ ሃይሉና ሥልጣኑ ከሙታን መካከል ተለይቶ ተነሳ፤
ሰይጠንን አሰረው፤ አዳምን ነፃ አወጣው፤
ከእንግዲህ ወዲህ ፍሰሃ፣ ሰላም፣ ደስታ ሆነ:: አሜን! 

መግደላዊት ማርያም መጌዶል በሚባለው የትውልድ አገሯ መግደላዊት ማርያም ትባላለች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብዙ ማርያሞች ስላሉ መግደላዊት ማርያም በመባል ተለይታ ተጠቅሳለች በውስጧ ታላቅ የፍቅር ትንታግ የሚቀጣጠልባት መግደላዊት ማርያም እስከዚህ ቀን ድረስ እንዴት ታግሳ ተቀመጠች? ስንል ጌታችን የተቀበረው ዓርብ ማታ ነው ቅዳሜ እንዳትመጣ የአይሁድ ሰንበት ነው በሰንበት ከተወሰነ ኪሎ ሜትር በላይ መጓዝ ስለማይቻል በሕግ ገደብ ተይዛ ቅዳሜን ከሌሎች ቅዱሳን አንዕስት ጋር በጭንቀት አሳለፈች፡፡
ሰንበት ካለፈ በኋላ ግን እሁድ ሌሊት ነጋ አልነጋ እያለች ስትጠባበቅ ገና ጨለማ ሳለ ወደ መቃብሩ ሥፍራ ገሰገሰች፡፡ አይሁዳውያን የሞተ ወዳጃቸውን በሦስተኛው ቀን መቃብሩ ላይ ሽቱ በማርከፍከፍ ለመጨረሻ ጊዜ ይሰናበቱታል ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በሕያውነቱ ሽቱን ተቀበለ የሙታን መሰናበቻ የሆነውን ሽቱ አልተቀበለም፡፡ መግደላዊት ማርያም የመጨረሻ ሀዘኗን ለመግለጥና ሽቱ ለመቀባት ገና ሳይነጋ ወደ መቃብሩ ሥፍራ ገሰገሰች፡፡
ገና ጨለማ ሳለና ማለዳ ወደ ክርስቶስ መገስገስ ለብዙዎች ጣር ነው ጨለማው እንዳለ ይሁን እኔ ግን ጌታዬን እፈልጋለሁ፣ ጌታዬ ያስፈልገኛል ከጨለማው በላይ ያለ እርሱ መኖር ይከብደኛል የሚሉ ጥቂቶች ናቸው፡፡ ጨለማው ከተወገደ በኋላ እንጂ ጨለማው እያለ ሊያመልኩት የተሰናዱ፣ ከጉዳያቸው ይልቅ የተሰቀለው ጌታ ራሱ ጉዳይ የሆነላቸው ጥቂቶች ናቸው፡፡ ብዙዎች በማለዳ ወደ ጌታ መምጣት አይፈልጉም፡፡

በወጣትነታቸው ጊዜ በጉብዝናቸው ወራት፣ ተናግረው ማሳመን፣ ጨብጠው ማቆም፣ ሮጠው መቅደም በሚችሉበት ዘመን ወደ እግዚአብሔር መቅረብ አይፈልጉም መጽሐፍ ግን ‹‹በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ›› (መክ 12፡1) ይለናል፡፡ ዕድሜያቸውን ከሰሩ በኋላ የዕድሜያቸውን እንጥፍጣፊ በእግዚአብሔር ቤት ለማሳለፍ የሚያስቡ ብዙዎች ናቸው፡፡ መስገድ፣ መፀለይ፣ መጾም በሚችሉበት ዘመን ዳንኪራ የሚረግጡ አስረሽ ምቺው የሚጨፍሩ ፣ ጠጥተው በመስከር የሚንዘላዘሉ በደባል ሱስ ተገዥ ሆነው በዓለም ሁካታ ተማርከው የሚኖሩ ነገር ግን ለእግዚአብሔር ጊዜ የሌላቸው ጥቂት አይደሉም ብዙ ሞክረው ሲደክማቸው እንጂ ገና በጠዋቱ ለእርዳታ ወደ እርሱ የሚመጡ በጣት የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ ክርስቶስ ለብዙዎች አማራጫቸው እንጂ ምርጫቸው አይደለም ስለዚህ በክብሩ አያዩትም፡፡
መግደላዊት ማርያም ወደ ክርስቶስ ስትገሰግስ ሴትነቷን የሚፈታተኑ ብዙ ነገሮች ነበሩባት ጨለማው፣ የመቃብሩ ሥፍራ ትልቅ ቋጥኝ ስጋቶቿ ነበሩ፡፡ ሴት ልጅ እንኳን በጨለማ በብርሃን አጥቂ ስለአለባት ትፈራለች የመቃብር ስፍራም እንኳን በጨለማ በቀንም የማይደፈር ነው ጌታን የከደነው ቋጥኝም በእርሷ ጉልበት የሚገፋ አይደለም የማትችለው ነገር ከፊት ለፊቷ ቢታያትም ‹‹ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላልና›› (1ዮሐ 4፡18) ፍቅር ፍርሃቷን አውጥቶ ጥሎላት ወደ ፊት ገሰገሰች፡፡ ወንጌላዊው ዮሐንስ ‹‹ድንጋዩ ከመቃብሩ ተፈንቅሎ አየች›› (ዮሐ 20፡1) በማለት ጽፎልናል፡፡ ወንጌላዊው ማርቆስ ደግሞ በመንገድ ሳለች ድንጋይ ትልቅ ስጋት እንደነበር ይገልጣል፡፡
‹‹እርስ በእርሳቸውም ድንጋዩን ከመቃብር ደጃፍ ማን ያንከባልልናል? ይባባሉ ነበር›› (ማር 16፡3) መግደላዊት ማርያም በእርሷና በክርስቶስ መካከል ጋሬጣ የሆነው ትልቅ ቋጥኝ በመንገዷ ሁሉ ያሳስባት ነበር ዛሬም ጌታችንን እንዳናገኝ ብዙ ቋጥኞች አስጨንቀውን ይሆናል፡፡ መግደላዊት ማርያም ግን ቋጥኙን ባትችለውም አለመቻሏ ጉዞዋን አላደናቀፈውም፡፡ ጥያቄና ስጋት የሆነባት ነገር ሕያው ቢሆንም ወደኋላ አልተመለሰችም ውጤቱ ግን ሕያው የሆነው ቋጥኝ ሳይሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ነበር፡፡ ‹‹ድንጋዩ ተፈንቅሎ አየች›› (ዮሐ 20፡1) በርግጥ ድንጋዩ የተፈነቀለው ጌታ እንዲነሳ አይደለም፡፡ መቃብሩ ባዶ መሆኑን ለማሳየት መልአኩ ፈንቅሎታል፡፡ ጌታ ግን መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል በኃይሉና በሥልጣኑ ነው የተነሳው፡፡

መግደላዊት ማርያም ሞቶም ትፈልገዋለች፣ ፈለገችው የገደሉትን የአይሁድ ካህናት ‹‹የዓርብ ገዳይ ነን›› ብለው ለራሳቸው የሚፎክሩትን ሳይሆን ስለ ፍቅር የሞተውን ኢየሱስ ክርስቶስን ነው፡፡ ሞቱን እንደመረታት አልቆጠረችውም ስለ ፍቅር የሚሞት ከገዳዮች ይልቅ እርሱ ጀግና ነውና፡፡ ሞቱ እንድትረሳው አላደረጋትም ፍቅሯን እንድትገልጥለት ውለታው አስገደዳት ሞቱ የቅርብ ደቀመዛሙርቱን ሳይቀር ያስደነገጠ ቢሆንም እርሷ ግን ከጊዜ ጋር አልተለወጠችም ከራሷ ይልቅ ስለ ክርስቶስ ፍቅር አሰበች ፍፁሙ ፍቅር ራስን በመርሳት ስለ ክርስቶስ ማሰብ መሆኑን አሳየች ሞቶም ፈለገችው ፍቅሯን ልዩ ያደረገውም የፈለገችው ተአምር እንዲደረግላት ከደዌ እንዲፈውሳት አበርክቶ እንዲመግባት አልነበረም፡፡
ስለ ራሱ ስለ ጌታ፣ ስለ ፍቅሩ ስለማንነቱ ፈለገችው የምታመልከውን እርሱን እንጂ ጥቅሟን አልነበረም ከጉድለት በላይ ኢየሱስ ክርስቶስን ማጣት ትልቅ ጉዳት ሆኖ ተሰማት፡፡ የክርስቶስ የሆነውን መውደድና ክርስቶስን መውደድ የተለያየ እንደሆነ ይህች ሴት ትመሰክራለች የዚች ሴት ፍቅር ፍቅራችንን ይታዘበዋል፡፡ ሁላችንም አምላካችን ገዳይ እንጂ ሟች እንዲሆን አንፈልግም ጠላቶቻችንን የሚበቀል በተነሱብን ላይ ፈጥኖ የሚፈርድ እንዲሆን እንፈልጋለን፡፡ እኛን አስከብሮ ራሱን ተፈሪ ያሚያደርግ አምላክ እንሻለን በድካም የሞተውን ወይም ዝም ያለውን ክርስቶስ እንደዚች ሴት ለመፈለግ ፍቅራችን ምን ያህል የፀና ይሆን?
ዛሬ ክርስቶስን ለማየት የሚከለክሉ ብዙ ቋጥኞች አሉ እግዚአብሔርን ለሚፈልግ ለዛሬው ትውልድ እነዚህ ቋጥኞች ሥጋት ቢሆኑም እግዚአብሔርን ፈላጊ ትውልድ በስጋቶች አይቆምምና ወደ ክርስቶስ መገስገስ ያስፈልጋል ያን ጊዜ ቋጥኙ አንከባሎ የተነሣውን ጌታ የምስራች እንሰማን፡፡
እኛስ ክርስቶስን እንዳናይ ጋሬጣ የሆነብን ነገር ምንድን ነው? ኃጢዓትና ሱስ ይሆን? በእምነት ከተጓዝን ቋጥኙ ይንከባለላል ክርስቶስን ለምትፈልግ ነፍስ ትልቅ ሆኖ የሚያስፈራት ችግር የለም ከትልቅ ችግራችን ይልቅ ክርስቶስ ትልቅ ነው፡፡ ከፍ ካለው ነገር በላይ ከፍ ያለው የሞት መድኀኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ የምንፈልጋቸውና እንዲሆኑልን የምንመኛቸው ብዙ መልካም ነገሮች ቢኖሩም ‹‹ድንጋዩን ማን ያንከባልልናል?›› የሚል ስጋት ግን አለብን ራዕያችን፣ ትዳራችን፣ ወዳጅነታችን የራሱ የሆነ የፈተና ቋጥኝ አለው የማይቀር ሆኖብን ብንጀምረው እንኳ ልባችን ግን ይፈራል፡፡
በእምነት ብንጓዝ ግን ድንጋዩ ተፈንቅሎ እናይ ነበር የእስራኤል ልጆች ባሕር የተከፈተላቸው በመጓዛቸው ነው እግዚአብሔር በእምነት ወደፊት ለመጓዝ ባሕር መክፈል፣ ቋጥኝ ማንከባለል ደስታው ነው ሕይወት በእኛ መቻል ላይ የተመሰረተች አይደለችም እኛ ምንም የማንችል ደካሞች ነን ነገር ግን ኃይልን በሚሰጠን በክርስቶስ እየታገዝን ወደ ፊት መጓዝ አለብን እንጂ ፍርሃታችንን ከቃሉ ይልቅ አምነን መቆም አይገባም፡፡
ለማንም ሰው መቃብር ቋጥኝ አይገጠምም የኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ግን ቋጥኝ ተደርጎበታል ዓለም ገድላም የፈራችው ቢኖር ኢየሱስ ክርስቶስን ነው፡፡ አስቸጋሪ የተባሉ ሰዎች ሁሉ ከሞቱ በኋላ አስጊነታቸው ያበቃል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ሞቶም ያስፈራል ሕያው ነውና በእርሱ ላይ እንደሆነው በተከታዮቹ ላይም ይሆናል ሞተንም የምናስፈራበት ጊዜ ብዙ ነው ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ ‹‹… አሳቾች ስንባል እውነተኞች ነን ያልታወቁ ስንባል የታወቅን ነን የምንሞት ስንመስል እነሆ ሕያዋን ነን የተቀጣን ሳንሆን አንገደልም ኃዘንተኞች ስንሆን ዘወትር ደስ ይለናል ድሆች ስንሆን ብዙዎችን ባለጠጎች እናደርጋለን አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የእኛ ነው›› (2ቆሮ 6፡9-10) በማለት የጻፈው፡፡

ደክሞኛል ብዙ ማገልገል አቅም የለኝም እያልን ጠላት ግን ከባድ ሥራ ሊሠራ አድፍጧል እያለ መከራ ያውጅብናል በብርታታችን ዘመን ያልነበሩ ሰዎችንም በድካማችን ዘመን ሲወለዱ እናያለን፡፡ ‹‹ምንም እንኳ ቢደክሙ ያሳድዱ ነበር (መሳ 8፡4) ተብሎ እንደተጻፈ ጠላት ምን ጊዜም ከማሳደድ አርፎ አያውቅም፡፡
አይሁዳውያን ጌታ እንደሚነሳ እርግጠኞች ነበሩ፡፡ ጠላቶቹ ያመኑትን ትንሳኤ ግን ደቀመዛሙርቱ አያምኑም ነበረ የምናመልከውን አምላክ ኃያልነት ጠላቶች የተባሉት ዲያብሎስና ሰራዊቱ አንድም አሕዛብ የሚያዉቁትን ያህል እኛ ብናውቅ ምንኛ በበረታን ነበር ጠላት አምላካችንን አይደለም እኛን እንኳ አይንቀንም የሚያሳድደን ስለፈራን እንጂ ስለናቀን አይደለም፡፡ እነዚህ ጠላቶች ትንሳኤውን ስለፈሩ ተከታታይ የሆኑ ሦስት ጥንቃቄዎችን አደረጉ፡፡
·         በትልቅ ቋጥኝ መቃብሩን ዘግተው በሮማ መንግስት ማህተም አተሙ
·         ይህንን ቢያልፍ ብለው የሚይዙ ልዩ ወታደሮችን ዘብ አድርገው አቆሙ
·         ይህንን ሁለት አጥር ቢያልፍ ትንሣኤውን የሚያስተባብሉ ወሬኞችን በገንዘብ ደልለው አሰናዱ አይሁድ በጣም ተሞኙ፣ ሞትን ያሸነፈ እርሱ ቋጥኝ ይከብደዋል ብለው ማሰባቸው ደካማነት ነው፡፡
እርሱ ባዶ መቃብር በቋጥኝ ከድነው ሲጠብቁ ኤልሻዳይ ንጉስ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በገሊላ ቀድሞ ከተማውን አዳረሰ በየሰው ሁሉ ቤት ሞላ በገንዘብ የተገዙ የሐሰት ምስክሮችን ቢያሰናዱም በፍቅሩ የተገዙ ደቀመዛሙርት ለመስዋዕትነት ጨክነው ለምስክርነት ወጡ፡፡  



No comments:

Post a Comment