Friday, April 25, 2014

የሴኬምን እንቅፋት ማስወገድ



 
 
ሴኬም በውስጧ ርኩሰትና አማልክት የሞላባት የአሕዛብ ከተማ ነች፡፡ ከእቅፋቶቿ ብዛት የተነሳ ለመንፈሳዊ ሕይወት ምቹነት የላትም ለዚህም ነበር እግዚአብሔር ያዕቆብን ‹‹ከሴኬም ተነስተህ ወደ ቤቴል ውጣ›› ያለው ዘፍ 35፡1፡፡ ቤቴል ማለት የእግዚአብሔር ቤት ማለት ነው ያዕቆብ ከልጆቹ ላይ ጌጣጌጥን አማልክትን ሳይቀር ተቀብሎ በጉድጓድ ውስጥ ቀበራቸው፡፡ የሴኬም እንቅፋት ናቸውና ለቤቴል ኑሮ አይገቡም፡፡ ይህን ይዞ ቤቴል ቢገዛ ኖሮ የቦታ ለውጥ እንጂ ትክክለኛ የሕይወት ለውጥ አይሆንለትም ነበር እንቅፋቶቹ ዛሬም አሉና፡፡


 








እንዲሁ ኃጢዓቱን (በውስጡ ያሉትን አማልክት) በንስሐ ጉድጓድ ውስጥ ሳይቀብር ቤተ ክርስቲያን እኖራለሁ የሚል ሰው የቦታ ለውጥ አደረገ እንጂ የሕይወት ለውጥ አላደረገም፡፡ እንቅፋቶችህን ካላስወገድካቸው ውስጣዊ ሰላምን አይሰጡም፡፡ ለምሳሌ ቁጣ ከሴኬም ያመጣኸው እንቅፋት ከሆነ ከክርስቲያኖች ጋር ያለህን ህብረት (ፍቅር) ያደፈርስብሃል፡፡ ሐሜት ከሴኬም ያሳደከው እርሾ ከሆነ የክርስቲያኖችን አንድነት ትበታትናለህ በዚህም እግዚአብሔርን በቤቱ ስታሳዝነው ትኖራለህ፡፡


 

እናም አሮጌውን እርሾ አስወግደው፡፡ ትንሽ ናት ብለን ከዓለም ይዘነው የምንመጣው ኃጢዓት መኖር የለበትም፡፡ ደግሞስ ‹‹ጥቃቅኑን ቀበሮዎች አጥምዳችሁ ያዙ›› መባሉስ ለምን ሆነና
! መኃ 3፡15 ደግሞም ‹‹ጥቂት እርሾ ሊጡን ሁሉ ታቦካዋለችና›› ተብሏል 1ቆሮ 5፡6 ለዚህ ነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ መቅደሱን ከሻጮች ሲያጠራ ትናንሽ ርግቦችን እንኳን ያላስቀረው፡፡ የአይሁድ መሸጫ ሆነዋልና ከዓለም ስንለይ መቅደስ በሆነ ልባችን ውስጥ ጥቃቅን ብለን የምንተዋቸው ነገሮች ነገ ለመንፈሳዊ ዕድገታችን ማነቆዎችና ችግር ፈጣሪዎች ስለሆኑ እንቅፋቶቻችንን ልናስወግድ ይገባል፡፡
(ምንጭ የመንፈሳዊ እድገት ማነቆዎች)

 

No comments:

Post a Comment