Monday, April 7, 2014

ሁለተኛው ሻማህ ካልጠፋ ሌሎቹ ይበራሉ

 

 


(አባት ልጃቸውን ሲመክሩ)
ጥንት ነው አሉ አንድ ሰው ከሰማይ ወደዚህ ና ! ተመልከትም የሚል እንደ ውሃ የሚፈስ ድምጽ ሰማ፡፡ ሄደ! አየም እነሆ በአንድ እጅግ ጠባብ በሆነ መንገድ ላይ ሶስት ሻማዎች ይበሩ ነበር፡፡ የሚገርመው የመጀመሪያው ሻማ እምነት ሁለተኛው ተስፋ ሶስተኛውም ፍቅር የሚባሉ ስሞች ነበሯቸው፡፡


ድንገት ግን ታላቅ ነፋስ ከምዕራብ ነፍሶ እምነትና ፍቅር የተባሉትን ሻማዎች አጠፋቸው፡፡ ሁለተኛው ተስፋ የተባለው ሻማ ግን በብዙ ትግል ከመጥፋት ሲተርፍ ተመለከተ በዚህን ጊዜም በታላቅ ድምጽ ጮኸ ፡፡ እምነትና ፍቅር የተባሉት ሻማዎች ጠፍተዋል ወድቆ አለቀሰ፡፡ ወዲያውም ከምስራቅ በነጭ ደመና የተቀመጠ በዘመናት የሸመገለ ሰው መጥቶ ልጄ ሆይ አይዞህ አትዘን የእምነትና ፍቅር ሻማዎች ቢጠፉም የተስፋ ሻማ ስላለ እንደገና ሁለቱን ሻማዎች ማብራት ይቻላል አለው፡፡ ተስፋ የተባለውም ሻማ አንስቶ እምነትና ፍቅር የተባሉትን ሻማዎች ለኮሰና አበራቸው፡፡ ፍጹም ብርሃንም ሆነ ልቡም ተጽናንቷልና እንባውም ታብሷልና ደስ አለው አመሰገነም፡፡
ልጄ ሆይ ሁል ጊዜም እግዚአብሔርን ተስፋ አድርገው እምነትህ ቢደክም ፍቅር ሲቀዘቅዝ ብታይስንኳ ተስፋ ቆርጠህ ወደ ኋላ አትመለስ፡፡ ነገ መለመጥን ተስፋ አድርግ እንጂ ክርስትና ከሥጋና ደም ጋር የምትታገልበት ሕይወት ሳይሆን ትግሉ ከጨለማ ገዥዎች ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር መሆኑን አትዘንጋ፡፡ በሕይወትህ ውስጥ ጠላት ለማጥፋት የሚፈልገው ታላቅ የልብ ሻማ ተስፋ ነው፡፡ የልብህን ተስፋ አጥብቀህ ጠብቅ ተስፋ ካለ ሁሉን መልሰህ ማግኘት ትችላለህ፡፡ ተስፋ ከሌለህ ግን ልታምንም ልታፈቅርም ይከብዳል፡፡ ተስፋ የማታደርግ ከሆነ እንዴት ታምናለህ? ታፈቅራለህስ?
ስለዚህ ልጄ ሆይ ዛሬን ብትወድቅ ተስፋ አትቁረጥ ተነስ እንጂ ዛሬ እንደ ቃሉ በፍቅር መኖር ቢያቅትህ መፍትሔው ተስፋ መቁረጥ አይደለም፡፡ በእግዚአብሔር ተስፋ ማድረግ እንጂ ዛሬ በአገልግሎትህ ብትደክም ተስፋ ቆርጠህ ከቤቱ ከቶ አትውጣ፡፡ ከሐዋርያት ጋር ሆነህ ጌታ ሆይ ወደ ማን እሄዳለሁ?  አንተ የዘላለም ሕይወት ቃል አለህ በለው፡፡ ዮሐ 6፡68 ከዳዊት ጋርም ሆነህ አሁንስ ተስፋዬ ማነው አንተ እግዚአብሔር አይደለህምን በለው መዝ 38፡7 ፍሬ ለማፍራትም በእርሱ ተስፋ አድርግ፡፡ በተስፋ ለምትጠባበቀው ለምትሻውም ነፍስ ጌታ ቸር የሚራራም ነውና፡፡ ልጄ ሆይ አዳም ከገነት ቢሰደድ ይዞ የወጣው ሌላ አይደለም ተስፋን ነው፡፡ በጌታ ቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ እድሜ ልኩን በክፉ ስራ ቢኖርም ተስፋን ግን አልጣለም በመጨረሻ ትንፋሽ ላይ ሳለ ወደ ሕይወት ያደረሰችው ይህች ተስፋ አለመቁረጥ ናት፡፡ በግራ ያለውማ ተስፋ በመቁረጡ የእምነትና የፍቅር ሻማዎቹ ሊበሩለት አልቻሉም፡፡ እንግዲህ ልጄ ሆይ በጊዜውም ያለጊዜውም እርሱን ተስፋ አድርገህ ኑር፡፡ በፍጹም ተስፋ አትቁረጥ ቸር ያሰንብትህ፡፡
‹‹እግዚአብሔርን ተስፋ የሚያደርጉ ግን እነርሱ ምድርን ይወርሳሉ›› መዝ 36፡9
ለወደደን ከኃጢአታችንም በደሙ ላጠበን ለእርሱ ክብርና ኃይል ይሁን፡፡ አሜን!!
 

No comments:

Post a Comment